ሕግ ጭራሽ ካለመከበሩ በከፋ ተመርጦ ሲከበር የበለጠ አልተከበረም፡፡ አሁን ባለን መረጃ ሀገሪቱ ከቻይና ጋር ስለገባነው የብድር ስምምነት የሚያትትውን 1000ኛውን አዋጅ ካወጀች ብኋላ እንኳ ከመቶ በላይ አዋጆች ወጥተዋል፡፡ ኑሮው፣ ፖለቲካው፣ ኢኮኖሚውና ማህበራዊ ጉዳያችን ብዙ ነው እና ሕጎቹ በዙ አይደለም ጉዳዩ፡፡ ስንቱ በርግጥ ወጥቶ ሥራ ላይ ዋለ ነው ጥያቄው፡፡ የማናከብረውን እና የማንተገብረውን ሕግ ማውጣት ከሕግ አልባነት አይሻልም፡፡
ይህ ጽሑፍ ስለ መረጃ ነፃነት ነው፡፡ ሰብአዊና አለማቀፋዊ የሆነው የመረጃ ነፃነት መብት ተጥሷል፡፡ በአጭር ቋንቋ ህገ መንግስቱ ተጥሷል፡፡ የተጣሰው ደግሞ ህጉ በወጣለት ህዝብም ፤ ህጉ በወጣበት መንግስትም ፤ ህጉ በወጣላቸው ሚዲያዎችም ጭምር ነው፡፡
ሁሉን ብፅፍ ቀለም አይበቃም እንዲል ሊቁ እኔ ግን እናተን በረጅም ጽሑፍ ላለማሰልቸት እንደሚከተለው አሳጥሬዋለሁ፡፡ በሕገ መንግሥቱ የተከበረው እና የታፈረው የዜጎች መረጃ የማግኘት መብት በሚዲያዎች እና በመንግስት ተቋማት በአደባባይ እየተሻረ ነው፡፡ ግልፅ ነው ዜጎች ስለማናቸውም ጉዳይ እጅግ ውስን ከሆኑ በስተቀሮች በቀር መረጃ የማግኘት መብት አላቸው፡፡ ዴሞክራሲ ጎዞ ጀምሯል የሚባለው ጠያቂ ሚዲያ ፣ መለሽ መንግስትና አድማጭ ህዝብ ሲኖርም ጭምር ነው፡፡ ያለ መረጃ ነፃነት ዴሞክራሲ የለም አይኖርምም፡፡ ካልተማሩ እንዴት ያውቃሉ ካላወቁ እንዴት ይጠይቃሉ እንዲል መጽሐፍ የመረጃ ነፃነት ወይም መረጃ የማግኘት መብት የዴሞክራሲ አምድ ነው፡፡
ሚዲያዎች መንግስት ሃላፊዎችን እና የመንግስት ተቋማትን የሚያጋልጡ መረጃዎችን ጨምሮ ማናቸውንም የህዝብ መረጃ የመጠየቅ ጠይቆ የማግኘት መብትም ግዴታም አለባቸው፡፡ መንግስት እጅግ ጥቂት ከሆኑ እንደ ሃገር ደህንነት የሚመለከቱ ጉዳዮች በቀር ምን? ለምን? እንደሚሰራ ዜጎች የማወቅ እና በጉዳዩ ላይ በሻቸው መንገድ ሃሳባቸውን የመግለፅ መብትና አቋም የመያዝ መብት አላቸው፡፡ ጉዳዩ አዋጃዊ አይደለም ህገመንግስታዊ ጭምር ነው፡፡ ስለዚህ ይህን መብት አለማክበር ህገ- መንግስትን አለማክበር ነው፡፡ ህገ-መግስት አልተከበረም የሚባለው የየግል ቁስላችን ሲናካና ትላንት ድንጋይ ወደ መንግስት ሲወረወር ዛሬ የፌደራል ስረአቱ ሲነካ ብቻ አይደለም ፡፡ በህገ-መግስቱ በግልፅ እና በቅድሚያ የተደነገጉት የግለሰብ እና የህዝብ መብቶች ሲጣሱም ጭምር ነው፡፡ የህገ-መንግስቱን መጣስ ሁሌ ከፌደራል ስረአት መከበር አለመከብር ጋር ማያያዝ ህገመግስቱ ለግለሰቦች የሰጣቸውን በረጅም የህዝቦች ትግልና መሰዋትነት አለማቀፋዊነት ደረጃ ያገኙ መብቶችን መጣስ ነው፡፡ መቼስ ስረአቱ የተዘረጋው ለህዝቦች መብት ሰላም እና ደህንነት ከሆነ የግለሶችን እና የህዝቦች መብት እየጣሱ ስረአቱን መጠበቅ ውሃውን እያፈሰሱ ቧንቧውን እንደመንከባከብ ያለ አባካኝነት ነው፡፡