ሕግና ኅብረተሰብ ጠንካራ ቁርኝት አላቸው፡፡ ኅብረተሰብ በሌለበት ሕግን ማሰብ፣ ሕግ በሌለበት በሥርዓት የሚኖር ኅብረተሰብን ማሰብ አስቸጋሪ ነው፡፡ ይህ ግንኙነት አንዳንድ ጊዜ በመቀዳደም ሊፈጸም ይችላል፡፡ ሕግ ኅብረተሰብን ዘመናዊ ለማድረግና ለመለወጥ እንደ መሳሪያነት ሊያገለግል ይችላል፡፡ በእንዲህ ዓይነት ጊዜ የሕጉ ዓላማ ኅብረተሰቡ ያልደረሰበትን ለውጥ ማስገኘት ነው፡፡ በተቃራኒው ከኅብረተሰቡ የሚወጡ እሴቶችና ባህሎችን ወደ ሕግ ደረጃ በማሳደግም የኅብረተሰቡን ሕልውና ማስቀጠል ይቻላል፡፡ እነዚህ የተሳሰሩ ግንኙነቶች ኅብረተሰቡ ከሕግ መጠቀም የሚቻልበትን ሁኔታ የሚያሰፋ ነው፡፡ ከዚህ ውጭ በሆነ መልኩ ሕጉ ከኅብረተሰቡ ዕድገት ወደ ጓላ ከቀረ ሕጉ ከወረቀት ያለፈ ተፈጻሚነት አይኖረውም፡፡ ይህን ችግር በአገራችን የተወሰኑ ሕግጋት እናስተውለዋለን፡፡
መንግሥት ገቢ ከሚሰበሰብባቸው ምንጮች መካከል የቴምብር ቀረጥ አንዱ ነው፡፡ የቴምብር ቀረጥ ቀጥተኛ ያልሆነ ታክስ ሲሆን፣ የሚሰበሰበውም በተወሰኑ ሰነዶች ላይ እንዲለጠፍ ወይም እንዲከፈል በማድረግ ነው፡፡
በአገራችን የቴምብር ቀረጥ የተጣለው ስለ ቴምብር ቀረጥ አከፋፈል በወጣው አዋጅ ቁጥር 110/90 መሠረት ነው፡፡ የዚህ አዋጅ አፈጻጸም በተለያዩ ባለድርሻ አካላት መካከል ያለው አሠራር ተመሳሳይ አይደለም፡፡ በተግባር በሰነዶች የተለያዩ ግብይቶች (Transactions) የሚፈጸሙ ሰዎች፣ የአገር ውስጥ ገቢ ሠራተኞች፣ ባንኮች፣ ፍርድ ቤቶች ወዘተ የየራሳቸው የአዋጁ አረዳድ አላቸው፡፡ የልዩነቱ ምንጭ አዋጁን ካለማወቅ፣ ከአዋጁ ድንጋጌዎች ይልቅ በልማድ መሥራት፣ እንዲሁም የአዋጁን ክፍተት የሚሟሉ መመርያዎችን አለማወቅ እንደሆነ የተለያዩ ጥናቶች አመልክተዋል፡፡ እነዚህን ችግሮች በመቅረፍ የአዋጁ አፈጻጸም የሕግ አውጪውን መንፈስ እንዲከተል ማስቻል የዚህ ጽሑፍ ዓላማ ነው፡፡
የቴምብር ቀረጥ የሚከፈልባቸው ሰነዶች
የቴምብር ቀረጥ በሰነዶች ላይ የሚጣል ታክስ ቢሆንም፣ ሁሉም ሰነዶች ላይ የሚጣል አይደለም፡፡ አዋጁ በአንቀጽ 3/12 የተለያዩ ሰነዶችን በመዘርዘር የሚከፈሉበትን ጊዜ፣ ሁኔታና መጠን በግልጽ አመልክቷል፡፡ የአዋጁ ዝርዝር ምሉዕ (Exhaustive) በመሆኑ በማመሳሰል ሌሎች ያልተጠቀሱ (ያልተዘረዘሩ) ሰነዶች ላይ የቴምብር ቀረጥ እንዲለጠፍ ወይም እንዲከፈል መጠየቅ አይቻልም፡፡ የቀረጥ ቴምብር የሚከፈለው በመመሥረቻና መተዳደሪያ ደንብ፣ የግልግል ሰነድ፣ ማገቻ፣ የዕቃ ማከማቻ ማረጋገጫ ሰነድ፣ ውል፣ ስምምነትና የእነዚህ መግለጫ፣ የመያዣ ሰነዶች፣ የኅብረት ስምምነት፣ የሥራ (ቅጥር) ውል፣ የኪራይ፣ የተከራይ አከራይና መሰል መብት የማስተላለፊያ ሰነዶች፣ ማረጋገጫ፣ የውክልና ሥልጣንና የንብረት ባለቤትነትን ማስመዝገቢያ ሰነድ ላይ ነው፡፡ ከእነዚህ ሰነዶች ውጭ ባሉ ሰነዶች ላይ የቴምብር ቀረጥ አይከፈልም፡፡
ፍርድ ቤቶች ሐምሌ 30 ሥራቸውን ካጠናቀቁ አንድ ሳምንት ሆናቸው፡፡ በየዓመቱ በክረምቱ አጋማሽ ተዘግቶ በመስከረም መጨረሻ የሚከፈተው ፍርድ ቤት ክረምት ጭር ይላል፡፡ የተወሰኑ የወንጀል ችሎቶችና ተረኛ ችሎቶች ካልሆኑ በቀር ፍርድ ቤቱ ከመደበኛው ሥራ ይቀዘቅዛል፡፡ አዲስ ፋይል መክፈት፣ አስቸኳይ የፍርድ ቤት ትዕዛዝ (ለምሳሌ እግድ) መስጠት፣ ከበድ ያሉ የወንጀል ጉዳዮች ከመመልከት ውጭ መደበኛ ቀጠሮ አይስተናገድም፡፡ በዚህ በክረምት ወቅት ችሎቶቹ አይሠሩም ማለት እንጂ አስተዳዳሪዎቹ፣ ስለ ፍርድ ቤቶቹ የተሻለ አሠራር፣ የዳኞች አቅም የማጎልበት ሥራ፣ ስለ ሥራቸውና አገልግሎት አሰጣጣቸው የሚቀርቡ ቅሬታዎችን የማስተካከል ሥራ ላይ ይጠመዳሉ ተብሎ ይታሰባል፡፡ ፍርድ ቤቱ ልማዳዊ የፍርድ ቤት አሠራሮችን በማስቀረት፣ የዳኞችን ሥነ ምግባር በመቆጣጠር እንዲሁም ለተገልጋዮች ምቹ የሚሆንበትን ሥራ የሚያስብበት ወቅት በመሆኑ፣ በዚህ ጽሑፍ በፍርድ ቤቶች የተዘነጉ ግን ተገልጋዮችን እየጎዱ ባለ ልማዶችና አሠራሮች ላይ የተወሰነ ምልከታ ለማድረግ እንሞክር፡፡
የመፀዳጃ ቤቱ ነገር
መፀዳጃና ፍርድ ቤት ምን አገናኛቸው እንዳልይባል ከገጠመኝ ልጅምር፡፡ በልደታ ፍርድ ቤት የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የተገልጋዮች መግቢያ በቀኝ በኩል ባሉት የድሮ ሕንፃዎች ጀርባ ሰዎች ተጣድፈው ሲገቡ ቀልቤን ሳቡኝ፡፡ ገንዘብ ቤት ወይም ኮፒ ቤት የሚሄዱ ቢመስልም ፍጥነታቸው የሚያሯሩጥ ሰው ያለ ነው የሚመስለው፡፡ ቀረብ ብዬ አንድ ወዳጄን ‹‹ሰዎቹ የት እየሄዱ ነው?›› ብዬ ስጠይቀው፣ ‹‹የተፈጥሮ ግዴታ ወጥሯቸው›› በማለት ሰዎቹ የሽንት ወረፋ ለመያዝ እንደሚቻኮሉ ነገረኝ፡፡ ከፍርድ ቤት ቅጥር ውጭም ባለጉዳዮችና ጠበቆች ሳይቀሩ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ፊት ለፊት ካለው ኒያላ ሆቴል ጀርባ ለሽንት ማዘውተራቸው የተለመደ ነው፡፡ ድንገት ተራቸው ደርሶ ከተጠሩ ‹‹ኒያላ ሆቴል ለሽንት ሄደው ነው›› ቢባል የሚረዳ ይኖር ይሆን? ፍርድ ቤቶቻችን በጤና መሥፈርት አንፃር ቢገመገሙ ኖሮ አሁን ካሉበት ደረጃ የባሱኑ ዝቅ ሊሉ እንደሚችሉ መገመት ይቻላል፡፡ በርካታ ባለጉዳይ የሚስተናገድበት ፍርድ ቤት ለባለጉዳዮች፣ ለጠበቆች፣ ለነገረ ፈጆች የሚሆኑ መታጠቢያ ቤቶችና የመፀዳጃ ቤቶች የላቸውም፡፡ አዲስ በተሠራው የልደታው ፍርድ ቤት ሕንፃ ሳይቀር ሽንት ቤት ባለመኖሩ ጠበቆችና ባለጉዳዮች ከፍርድ ቤት ውጭ በየካፌውና ሬስቶራንቱ ሲዞሩ ይውላሉ፡፡ በዚህ ዘመን ዘመናዊ ሕንፃዎች አይደሉም የገጠሩ ማኅበረሰብ እንኳን የመፀዳጃ ቤት እንዲያዘጋጅ በሚመከርበት ወቅት፣ ትናንሽ ግሮሰሪዎችና ካፌዎች እንኳን መፀዳጃ ቤት ለደንበኞቻቸው በሚያቀርቡበት ጊዜ ፍርድ ቤቶች ረዥም ሰዓት ለሚያስቆሙዋቸው ባለጉዳዮቻቸው የተፈጥሮ ግዴታቸውን የሚወጡበት ቦታ አለማዘጋጀታቸው ደንበኛ ተኮር እንዳይሆኑ አድርጓቸዋል፡፡ በሰኔ ወር በጠቅላይ ፍርድ ቤቱ በተዘጋጀ ጉባዔና የኢትዮጵያ የሕግ ባለሙያዎች ማኅበር በሐምሌ አጋማሽ በፍትሕ ሚኒስቴር ባዘጋጀው የውይይት መድረክ ላይ ጠበቆች ‹‹ኧረ የመፀዳጃ ቤቱን ነገር አደራ!!›› የሚል መልዕክት ለፍርድ ቤቶቹ አመራሮች አሰምተዋል፡፡ አንዳንድ ጠበቆች ከልምዳቸው እንደሚናገሩት ከፍተኛ ታዋቂነት ያላቸውና የውጭ ዜጎች ሳይቀሩ የመፀዳጃ ቤት ጥያቄ ባቀረቡ ጊዜ አለማስተናገዳቸው የፍርድ ቤቱን ገጽታ እንደሚያጎድፈው ይናገራሉ፡፡ ሕፃናትና ነፍሰ ጡሮች፣ አረጋውያንና የታመሙ ሰዎች በሚገኙበት ፍርድ ቤት ለአስቸጋሪ ሁኔታ የሚጠቅም መታጠቢያ ቤትና መፀዳጃ ቤት አለመኖሩ አንገብጋቢ ጉዳይ ነው፡፡ የድሮዎቹ ፍርድ ቤት ለዳኞች መፀዳጃ ቤቶችን ሲያዘጋጁ ባለጉዳዮቹንም አይዘነጉም ነበር፡፡ ለዚህ ነው በአዲስ ባልተተኩት የድሮ ሕንፃዎች ንጽህናቸው አጠያያቂ ቢሆንም፣ ለባለጉዳዮች ሽንት ቤቶች አዘጋጅተው የምናስተውለው፡፡ የሽንት ቤት ነገር የፍርድ ቤቶች አስተዳዳሪ አካል የክረምት የቤት ሥራ ይሆናል ብለን ተስፋ እናድርግ፤ ካልሆነ ጤና ጥበቃ የሽንት ቤቱን ጥያቄ በይግባኝ እንዳይመለከተው፡፡
ጊዜ ዋጋ የሚያገኘው መቼ ነው?
በማንኛውም አገር የመንግሥት አስተዳደር ከሕግ አውጪውና ከሕግ አስፈጻሚው እኩል የዳኝነት አካሉ አደረጃጀት፣ አወቃቀርና ጥንካሬ የሥርዓቱን ዴሞክራሲያዊነት ይወስናል፡፡ የዳኝነት አካሉ ገለልተኛና ነፃ ባልሆነ መጠን የሥርዓቱ ዴሞክራሲያዊነት ዋጋ ያጣል፡፡ የዳኝነት አካሉ መሠረታዊ ሕገ መንግሥታዊ መርሆችን ለማስፈጸም፣ የዜጎች የሰብዓዊ መብቶች እንዲጠበቁና የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን ገለልተኛ፣ ግልጽ አሠራርን የሚከተልና ጠንካራ እንዲሆን ያስፈልጋል፡፡ በ1987 ዓ.ም. የወጣው ሕገ መንግሥታችን በአንቀጽ 78 እና 79 እነዚህ መሠረታዊ የዳኝነት አካሉ መገለጫዎችን ደንግጓል፡፡ ይሁን እንጂ ሕገ መንግሥቱ ከወጣ ከ25 ዓመታት በኋላም የዳኝነት አካሉ የአሠራር ግልጽነትና ተጠያቂነት አመርቂ እንዳልሆነ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ይስማማሉ፡፡ ለዚህ ነው የፌዴራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት በ2015 ዓ.ም በሕዝብ ታማኝነት ያለው የዳኝነት አካል ለመሆን ራዕይ ይዞ የሚንቀሳቀሰው፡፡ ከ15 ቀናት በፊት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከፀደቀው የዳኝነት ሹመት ጋር በተያያዘ በሕግ ባለሙያዎች በየዐውዱ የሚደረገው ክርክር የዚህ አንዱ መገለጫ ነው፡፡ ኃይለ ገብርኤል መሐሪ የተባሉ ጸሐፊ ሰኔ 26 ቀን 2008 ዓ.ም. በሪፖርተር ጋዜጣ የአስተያየት አምድ ‹‹ግልጽነት የጎደለው የዳኞች ምልመላ›› በሚል በጻፉት ጽሑፍ የተሾሙት ዳኞች ምልመላ በአጭር ጊዜ የተፈጸመ፣ በቂ ፈተናና ግምገማ ያልተደረገበት፣ የሕዝብ አስተያየት በአግባቡ ያልተወሰደበትና ግልጽነት የጎደለው እንደነበር ይገልጻሉ፡፡ ጸሐፊውን ጨምሮ በፍርድ ቤቶች አካባቢ የሚታዩ ጠበቆችም የዳኞቹ አመላመልና ሹመት ጋር በተያያዘ ሊታዩ የሚገቡ ነጥቦች እንዳሉ ያምናሉ፡፡
የዳኞች አመላመልና አሿሿም የዳኝነት አካሉን ነፃነት ከሚያረጋግጡ ቅድመ ሁኔታዎች ዋናው ነው፡፡ ዳኞችም ከማንኛውም ቀጥተኛም ሆነ ተዘዋዋሪ ተፅዕኖ ነፃ በመሆን ፍትሕ እንዲሰፍን የሚሠሩት ምልመላውና አሿሿሙ ግልጽና ተጠያቂነት ሲኖረው ነው፡፡ የዳኞች አሿሿም የዳኝነት አካሉን ነፃነት ከሚያስገኙ የገለልተኝነት፣ የብቃት፣ የሃቀኝነትና የነፃነት እሴቶች ጋር እጅጉን ይቆራኛል፡፡ የዳኝነት አካሉ በኅብረተሰብ ውስጥ ተገቢውን ቦታ እንዲያገኝ በግልጽነት የዳኞችን የመሾም ሥርዓት ሊያከናውን ይገባል፡፡ ይህ የሚሳካው ደግሞ የዳኞች የአመራረጥና የአሿሿም ዘዴ፣ የሚመረጡ ዳኞች ዕውቀትና ልምድ በጥንቃቄና በኃላፊነት ሲከናወን ነው፡፡ በዚህ ጽሑፍ ከዳኝነት አሿሿም ጋር በተያያዘ ጥንቃቄ የሚፈልጉ አንዳንድ ነጥቦችን ለመመልከት እንሞክራለን፡፡
የዳኝነት አሿሿም ዘዴዎች
የዳኝነት አሿሿም እንደ አገሮቹ የፖለቲካ ባህልና ማኅበራዊ እሴት ይለያያል፡፡ አንድ ወጥ የአሿሿም ሥርዓት የለም፡፡ ማንኛውንም የአሿሿም ሥርዓት የሚከተል አንድ አገር የዳኝነት አካሉ ነፃ እንዲሆን የአሿሿም ሒደቱ ግልጽና ኅብረተሰቡን ያሳተፈ ሊሆን ይገባዋል፡፡ ግልጽነትና የሕዝብ ተሳትፎ በአሿሿም ካለ ጥራትና ብቃት ያላቸው የሕግ ባለሙያዎች ዳኛ ይሆናሉ፡፡ ኅብረተሰቡ በዳኝነት አካሉ ላይ ያለው መተማመን ይጨምራል፡፡
በተለያዩ አገሮች ተፈጻሚ የሚሆኑ የዳኝነት አሿሿም በደምሳሳው በሁለት ሊከፈል ይችላል፡፡ አንዱ በምርጫ የሚከናወን ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ በመሾም ሥርዓት የሚከናወን ነው፡፡
መኳንንት ከሕግ ትምህርት ቤት ተመርቆ ሲወጣ ግር ያለው ነገር የትምህርቱና የአተገባበሩ ልዩነት ነው፡፡ በአብዛኛው በንድፈ ሐሳብ አስተምህሮና ትንተና ላይ የሚተኮረው ትምህርቱ በተግባር ከሚታየው የፍርድ ቤት ነባራዊ ሁኔታ ጋር አልታረቅ ብሎት ተቸግሯል፡፡ ይህን ችግሩን ያባባሰው ደግሞ ከቤተሰቡ አንዱ የወራሽነት የምስክር ወረቀት ከፍርድ ቤት እንዲሰጠው በማሰብ አቤቱታውን እንዲያዘጋጅለት ሲጠይቀው ነው፡፡ አቤቱታውን አዘጋጅቶ ለቤተሰቡ አባል ቢሰጠውም በአንዱ ክልል ከሚገኘው የወረዳ ፍርድ ቤት የገጠመው ነገር ሌላ ነው፡፡ ቤተ ዘመዱ በፍርድ ቤቱ አቤቱታው በትክክል አለመጻፉ ተነግሮት በፍርድ ቤቱ ደጃፍ ከሚገኙት ራፖር ጸሐፊ ተጽፎ እንዲመጣ ተመከረ፡፡ ሰውየውም የተባለውን ፈጽሞ አቤቱታው ተቀባይነት አግኝቶ የወራሽነት የምስክር ወረቀት አገኘ፡፡ የመኳንንትና የራፖር ጸሐፊው አቤቱታ ልዩነት ቀላል ነበር፡፡
ጸሐፊው በሚከታተለው አንድ የንግድ ችሎት ጉዳይ ጠበቃው የችሎቱን ዳኛ ያማርራል፡፡ የዳኛውን የችሎት አካሄድ እየተቸ በዕለቱ በሰጠው ፍርድ ጠበቃው ለጉዳዩ ጠቃሚ የሆነውን የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ የሕግ ትርጉም የችሎቱ ዳኛ በፍርዱ አለማካተቱ፣ ለጉዳዩ አግባብነት ያለው መሆኑንና ይዘቱንም በፍርዱ ለማንፀባረቅ ፈቃደኛ አለመሆኑ እጅጉን አንገብግቦታል፡፡ እንደ ጠበቃው አነጋገር ‹‹ከሳሾች ባቀረቡት ክስ ለጉዳዩ አግባብነት ያለውን የሰበር ችሎት ቅጹን፣ የመዝገብ ቁጥሩንና ቀኑን አመልክተን አቀረብን፣ በቃል ክርክርም ይህንኑ በአጽንአት እንዲመዘገብልን አመለከትን፤›› ይላል፡፡ ውጤቱን ሲገልጽ ደግሞ ዳኛው በፍርዱ ሀተታውም ሆነ ትንታኔ የሰበር ችሎቱን ፍርድ አልገለጸም፣ የሰጠውም ፍርድ ሰበር ችሎቱ ከሰጠው አስገዳጅ ትርጓሜ ጋር የሚጋጭ በመሆኑ በይግባኝ ከማሳረም ውጭ አማራጭ እንደሌለው ተናገረ፡፡
ከሰኔ 1997 ዓ.ም. ጀምሮ በአገራችን የሰበር ችሎት የሚሰጠው ትርጉም በሥር ፍርድ ቤቶች ላይ አስገዳጅ መሆኑ በሁሉም የሕግ ባለሙያዎች ዳኞችን ጨምሮ የታወቀ ነው፡፡ በተግባር ግን ጠበቃው የገጠመውን ዓይነት የፍርድ ቤቶች ልማድ ማስተዋል የተለመደ ነው፡፡ አፈጻጸሙን በተመለከተ ግን አሁንም ያልጠሩ ወይም የማይፈጸሙ አሠራሮች መኖራቸውን የጠበቃው ተሞክሮ ያሳያል፡፡ ለመሆኑ የሥር ፍርድ ቤት ዳኞች የሰበር ሰሚ ችሎት የሰጣቸውን አስገዳጅ ፍርዶች ማወቅ (Judical notice መውሰድ) ይጠበቅባቸዋልን? የሰበር ሰሚ ችሎት አስገዳጅ ፍርዶች ባልታተሙበት ሁኔታ አስገዳጅነት አላቸውን? አንድ የሥር ፍርድ ቤት ዳኛ የሰበር አስገዳጅ ፍርድ ተጠቅሶላት የማይቀበልበት ሁኔታ ይኖራልን? አስገዳጅ የሰበር ትርጉምን ወደ ጎን ማድረግ፣ አለመቀበል ወይም ከተሰጠው ትርጉም ተቃራኒ የሆነ ፍርድ መስጠት ዳኞችን በሥነ ምግባር አያስጠይቃቸውምን? የሚሉት ነጥቦች ምላሽ የሚፈልጉ ናቸው፡፡ በዚህ ጽሑፍ እነዚህን ነጥቦችና ከሰበር ችሎት ፍርድ አስገዳጅነት ጋር የተያያዙ አንዳንድ ነጥቦችን ለማንሳት እንሞክራለን፡፡
አዋጅ ቁጥር 454/97 ዓላማውና ይዘቱ
ይህ አዋጅ በአንቀጽ 4 ላይ ‹‹የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከአምስት ያላነሱ ዳኞች በተሰየሙበት የሰበር ችሎት የሚሰጠው የሕግ ትርጉም በየትኛውም ደረጃ ላይ በሚገኝ የፌዴራል ወይም የክልል ፍርድ ቤት ላይ አስገዳጅነት ይኖረዋል፡፡ ሆኖም የሰበር ችሎቱ በሌላ ጊዜ በተመሳሳይ ጭብጥ የተለየ ትርጉም ሊሰጥ ይችላል፤›› ሲል ይደነግጋል፡፡ በዚህ ድንጋጌ መሠረት የሥር ፍርድ ቤቶች ሰበር ችሎቱ የሰጠውን የሕግ ትርጉም የመከተል፣ የመተግበር ግዴታ አለባቸው፡፡
ዶ/ር ትዝታ በፌዴራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ጉዳዩዋን ለመከታተል በችሎት ታድማለች፡፡ በሥር ፍርድ ቤት በቤቷ ላይ ያለአግባብ ፍርድ ተሰጥቷል ብላ ስላመነች የተማረ ጠበቃ የይግባኝ አቤቱታ ጽፎላት ጉዳይዋን በራሷ ትከታተላለች፡፡ እንደ እርሷ አስተሳሰብ ጉዳይዋን ከእርሷ ይልቅ የሚረዳው የለም በሚል ከዳኛ ፊት ቀርባ ለማስረዳት ጓጉታለች፡፡ በዛሬው ቀጠሮ ይህ ሐሳቧ እንደሚሳካላት በውጭ የሚያማክራት ጠበቃ ነግሯታል፡፡
መዝገቡ ለዛሬ በቀጠሮ ያደረው ቀደም ሲል ረዳት ዳኛ ፊት ቀርባ ስለጉዳዩ ካሳሰበች በኋላ የይግባኝ አቤቱታውን ለመስማት በሚል ነው፡፡ ችሎት ተቀምጣ የምትሰማው የዳኛው ድምፅ ‹‹አያስቀርብም ብለናል!›› ‹‹አያስቀርብም›› የሚሉ አጭርና መርዶ ነጋሪ ቃላት ናቸው፡፡ የእሷ ጉዳይ ገና ያልተሰማ በመሆኑ እንዲህ ያለውን ፍርድ ዛሬ እንደማትሰማው አምናለች፡፡ የሕግ አማካሪዋም ልቧን አጽንቶላታል፡፡ ተራዬ እስኪደርስ በሥር ፍርድ ቤት ተፈጸመ የተባለውን ስህተት ለማስረዳት ከማስታወሻዬ ላይ ነጥቦቹን ተራ በተራ በወፍ በረር ልቃን ብላ ጀምራለች፡፡ ከተመሰጠችበት ንባብ ያናጠባት በዳኛው የተጠራው ስሟ ነበር፡፡
‹‹ዶ/ር ትዝታ በረደድ›› ብለው ዳኛው ሲጠሩ ከመቅጽበት ከዳኛው ፊት ተገተረች፡፡ ዳኛው ማንነቷን ካረጋገጡ በኋላ ‹‹ይግባኙ አያስቀርብም ብለናል፤›› ሲሏት በደንብ አልሰማቻቸውም፡፡ ‹‹እህ እህ ምን አሉ?›› ብላ ስትጠይቅ ‹‹አያስቀርብም ተዘግቷል፣ ጨርሰናል፤›› አሏት፡፡ ‹‹ይግባኜ አልተሰማም፣ ረዳቱ ነው ያናገረኝ፣ እርስዎን ዛሬ ማየቴ ነው… ለውሳኔ አልተቀጠረም… መዝገቡ የሌላ እንዳይሆን …›› ብዙ ለማለት ብታስብም ባህላዊው የፍርድ ቤት ፍርኃት አላስችላት አለ፡፡ ከእሷ በፊት የተስተናገዱት አቀርቅረው እንደወጡ እሷም በቁሟ አቀረቀረች፡፡ ከዳኛው ፊት እንደቆመች ዳኛው ሌላ ባለጉዳይ ማስተናገድ ቀጠሉ፡፡
በዚህ መነሻ ነበር ከችሎት ስትወጣ ጨዋታ የጀመርነው፡፡ ‹‹አያስቀርብም›› ማለት ምንድነው? በምን ምክንያት ነው? የማያስቀርበውስ እንዴት ነው? ዳኛው ይግባኜን አይሰሙም እንዴ? የሚሉትንና እኔ መልስ ልሰጣት የማልችላቸውን ጥያቄዎች ያዥጎደጎደችው፡፡ ሕጉ የሚለውን፣ ዳኛው ሊፈጽሙት ይገባ የነበረውን ሥርዓት ብነግራት ይባሱኑ ትበሳጫለች በማለት በቀልድ ነገሯን ለማጣጣል ጥረት አደረግኩ፡፡
እናንተ ሐኪሞችስ በማይነበብ ጽሑፍ ለበሽታህ መድኃኒቱ ይሄ ነው ብላችሁ ብጣቂ ወረቀት ትሰጡ የለም እንዴ? አልኳት፡፡ ዶ/ር ትዝታም መለሰች ‹‹እንዴ እኛ እኮ ደማችሁን ለክተን፣ ሙቀታችሁን አይተን፣ የሚሰማችሁን በዝርዝር ሰምተን፣ ደምና ሰገራ፣ ኤክስሬይና ራጅ ተመልክተን ነው፤ ከጻፍነውም በኋላ የመድሃኒት ባለሙያ የማይነበበውን አንብቦ ተገቢውን መድሃኒት ይሰጣችኋል አለች›› በልቤ ‹‹ልክ ነሽ›› አልኩ፡፡ እንዲያውም የመደመጥ መብት በሐኪሞች የተሻለ ይተገበራል፡፡ በእኛ አገር ሐኪሞች ከዳኞች ይልቅ ደንበኛቸውን ይሰማሉ፣ ጊዜ ይሰጣሉ፣ ሰፊ ምርመራም ያከናውናሉ አልኩ፡፡ እርሷንም እንድትጽናና ነግሬያት የነጋሪት ጋዜጣ ወደ መግዣው ሱቅ በመሔድ ከእሷና ከሐሳቧ ሸሸሁ፡፡
የ‹‹ያስቀርባል - አያስቀርብም›› ነገር ግን የሕግ ዕውቀቱ የሌላቸውን ቀርቶ ለሕግ ባለሙያዎችም በአግባቡ የሚገባ ወይም የተረዳ አይመስለኝም፡፡ ፀሐፊው በፍርድ ቤቶች አካባቢ ከገጠሙት ጉዳዮችና በችሎት ከሚያስተውለው ተግባር አንፃር ‘አያስቀርብም እንቆቅልሽ፣ ያስቀርባል ሎተሪ’ እየሆነ መምጣቱን አስተውሏል፡፡ የ‹‹አያስቀርብም›› ልማድ በሰበር ችሎት ሳይቀር የሚስተዋል ቢሆንም፣ በዚህ ጽሑፍ በከፍተኛ ፍርድ ቤቶች የታዘብኩትን አጠር አድርጌ ለመቃኘት እሞክራለሁ፡፡ ተሞክሮው በጎ የተሠራውን፣ ጊዜ ወስዶ መዝገብ መርምሮ በምክንያት ወይም ያለምክንያት አያስቀርብም የሚሉትን ተሞክሮዎች ስለማይመለከት የአሠራር ክፍተት ባለባቸው ላይ ማተኮሩ ተገቢ ሳይሆን አይቀርም፡፡ አያስቀርብም በሕጉ ያለውን ቦታ፣ ከዳኛው የሚጠበቀውን ሥርዓት፣ በተግባር የሚታዩ ክፍተቶችን፣ የክፍተቶቹን አንድምታ በመቃኘት የሚስተካከልበትን መፍትሔ ለመጠቆም እሞክራለሁ፡፡
ስለ ይግባኝ መብትነት
የአዲስ አበባ ፍርድ ቤት ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ ሥልጣናቸውን የተመለከቱ የተለያዩ ክርክሮች ተነስተዋል፡፡ ዋናው ክርክር በተቋቋመበት ወቅት የተነሳው የሕገ መንግሥታዊነት ጭብጥ ነው፡፡ ሕገ መንግሥቱ በአንቀጽ 78 እስከ 80 የዳኝነት አካሉን ሲያዋቅር በተለያዩ ደረጃዎች ያሉት የፌዴራልና የክልል ፍርድ ቤቶች እንደሚቋቋሙ በመግለጽ የፍርድ ቤት ሥልጣን ከመደበኛ ፍርድ ቤቶች የሚወሰዱ ጊዜያዊና ልዩ ፍርድ ቤቶች እንደማይቋቋሙ ደንግጓል፡፡
ይህን መሠረት አድርገው አንዳንዶች በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሥር የተቋቋመው የከተማ ነክ ፍርድ ቤት (አሁን የከተማ ፍርድ ቤት) ሕገ መንግሥታዊ አይደለም ሲሉ ሞግተዋል፡፡ የፍርድ ቤቱን ሕገ መንግሥታዊነት የሚደግፉ ወገኖች ደግሞ ሕገ መንግሥቱ በአንቀጽ 49 በአዲስ አበባ የራስ አስተዳደር ስለፈቀደ አዲስ አበባ እንቅስቃሴዎቿን ለመከታተል የሕግ አውጭ፣ የሕግ አስፈጻሚ እንዲሁም የሕግ ተርጓሚ አካላትን ማቋቋም ትችላለች ብለዋል፡፡ የግራ ቀኙን የሕገ መንግሥታዊነት ለመደገፍ ሌሎችም ምክንያቶች ተጠቅሰዋል፡፡ ያም ሆኖ የአዲስ አበባ ከተማ ፍርድ ቤት በአዋጅ ተቋቁሞ መደበኛ የፍርድ ቤት ሥራዎችን መሥራት ከጀመረ ሁለት አሠርት ዓመታትን አስቆጥሯል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ ፍርድ ቤት በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ ሥልጣኖች ተሰጥተውታል፡፡ በተቋቋመበት ወቅት በዋናነት የከተማ አስተዳደሩ የሚያከናውናቸው ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ የአስተዳደርና የቁጥጥር ሥልጣኖችን ከማስፈጸም ጋር የተያያዙ ክርክሮችን ይመለከት ነበር፡፡ ሁከት ይወገድልኝ፣ ደንብ መተላለፍ፣ ከቀበሌ ቤቶች ጋር የተያያዙ ክርክሮች፣ ከመሬት ጋር የተያያዙ ክርክሮችን ተቀብሎ እንዲያስተናግድ ተፈቀደለት፡፡ ከተወሰኑ ጊዜያት በኋላ ደግሞ ከመሬት ጋር የተያያዙት ጉዳዮች በአስተዳደሩ ስም ለተቋቋመ ቦርድ የተሰጠ ሲሆን፣ በምትኩ ጊዜ ቀጠሮ፣ እስከ አምስት ሺሕ ብር የሚደርሱ የፍትሐ ብሔር ክርክሮች፣ የስም ለውጥ፣ የወራሽነት የምስክር ወረቀት፣ የመጥፋት ውሳኔ፣ የባልና የሚስትነት፣ የሞግዚትነት የምስክር ወረቀት የመስጠት ሥልጣን በተሻሻሉ አዋጆች እንዲሠራ ተደርጓል፡፡
ለፍርድ ቤቱ በተለያዩ ጊዜያት ከተሰጡት ሥልጣኖች ለመረዳት የሚቻለው ፍርድ ቤቱ እንዲሠራቸው የተፈለጉት ክርክሮች ውስብስብነት የሌላቸው፣ በአጭር ጊዜ ሊጠናቀቁ የሚገባቸው፣ የገንዘብ መጠናቸው አነስተኛና ከከተማ አስተዳደሩ ጋር የተያያዙ ሥራዎችን (Municipality activities) መሠረት አድርገው የሚነሱ ክርክሮችን ነው፡፡
በአንጌሳ ኢቲቻ የተጻፈውን ‹‹ችሎት መድፈር፡- ሕጉና የአሠራር ግድፈቶች›› የሚለውን ሳነብ እ.አ.አ በታኅሣስ 2013 በተመሳሳይ ርዕስ የጻፍኩትን ለአንባብያን ለማካፈል ወደድኩ፡፡ በዚህ ጽሑፌ ፍርድ ቤት መድፈር ምን ማለት ነው? የኢትዮጵያ ሕግ ስለ ፍርድ ቤት መድፈር ምን ይላል? የሕጉ ዓለማስ ምንድነው፣ የወንጀሉ አወሳሰን ልዩ ባህርይስ እንዴት ይታያል፣ በአፈጻጸም የሚታዩ ችግሮች ምንድናቸው የመሚለውን እዳስሳለሁ፡፡
በወቅቱ የሪፖርተር ጋዜጣ ይዞት የወጣው ከፍርድ ቤት ጋር የተያያዙ ሁለት ዜናዎች አንባቢውን በተለይም የሕግ ባለሙያዎችን የሚያስገርም ነበር፡፡ የመጀመሪያው ዜና አንድ የፖሊስ አባል የፌዴራል ፍርድ ቤት ዳኛን በማመናጨቅና ፍርድ ቤት በመድፈር ወንጀል ጥፋተኛ ተብለው መታሠራቸውና ሌሎቹ ፖሊሶች ጉዳይ በቀጠሮ ላይ መሆኑ ነው፡፡ በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ሁለተኛ ፍትሐብሔር የቤተሰብ ችሎት ውስጥ የተፈጸመው ይህ ወንጀል ለየት የሚያደርገው ሕግን ለማስከበር አስፈጻሚውን በሚወክለው በፖሊስ መፈጸሙ ብቻ አይደለም፡፡ ፖሊሶቹ ያሳዩት ባህርይና ኃላፊዎቹ የሰጡት መልስ የበለጠ አስገራሚ ነበር፡፡ ፖሊሶቹ በጊዜው የዳኝነት ሥራ ስታከናውን የነበረችይቱን ዳኛ ‹‹አንመጣም››፣ ‹‹አንቀርብም››፣ ‹‹ስቀርብ ትፈትሽኛለሽ››፣ ‹‹ነገርኩሽ እኮ›› ወዘተ. በማለት ፍርድ ቤቱን ዝቅ የሚያደርግ፣ በኅብረተሰቡ ውስጥ ያለውን መተማመን የሚያሳጣና ሌሎች ዳኞችን የሚያሳቅቅ ነው፡፡ የፍርድ ቤት መድፈር በአብዛኛው በተከራካሪ ወገኖች፣ በቤተ ዘመዶቻቸው፣ በጋዜጠኞች ወዘተ. ተፈጸመ ተብሎ መስማት የተለመደ ነው፡፡ ችሎቱን ለማስከበር በተሰማሩት የፖሊስ አባላት መፈጸሙ ግን የበለጠ ግርምት ይፈጥራል፡፡ በጊዜው የፖሊስ ኃላፊው ‹‹ልጆቹ ጥፋት ያጠፉት ልጆች ስለሆኑ ነውና ይቅርታ ይደረግላቸው›› የሚለው ደግሞ፣ የፖሊስ ተቋሙ በፍትሕ አደባባይ፣ የሚበሳጭና የሚናደድ ተከራካሪ በሚኖርበት፣ ኅብረተሰቡ በብዛት አንዱን ነቅፎ ለሌላው ወግኖ በሚቆምበት ቦታ የሚመድባቸውን ፖሊሶች የትምህርትና የልምድ ሁኔታ ጥያቄ ውስጥ የማያስገባ ነው፡፡ ሁለተኛው ዜና የከፍተኛው ፍርድ ቤት ትዕዛዝ በአዲስ ክፍለ ከተማ መሬት ልማት ማኔጅመንት የመጣሱ ዜና ነው፡፡ በፍርድ ቤት በተያዘ አንድ ጉዳይ ፍርድ ቤቱ እንዳይፈርስ የእግድ ትዕዛዝ የሰጠበትን የንግድ ቤት የእግድ ትዕዛዙ ደርሶት ክፍለ ከተማው ቤቱን የማፍረሱ ዜና እጅጉን አስደንጋጭ ነው፡፡
እነዚህ ሁለት ዜናዎች በፍትሕ ሥርዓቱ ላይ የተጋረጡትን ፈተናዎች አመላካች ናቸው፡፡ ፍርድ ቤቶች ከሦስቱ የመንግሥት አካላት አንዱ እንደመሆናቸው ሕገ መንግሥታዊ ጥበቃና ኃላፊነት ተሰጥቷአቸዋል፡፡ ፍርድ ቤቶች አስፈጻሚውን የመቆጣጠር ሕገ መንግሥታዊ ግዴታ ያለባቸው ሲሆን አስፈጻሚውን ለመቆጣጠር ባልቻሉ መጠን ህልውናቸው ላይ አደጋ ይፈጥራል፡፡ በሁለቱ ዜናዎች ፍርድ ቤቱ የተደፈረው በአስፈጻሚው አካል እንደመሆኑ መጠን የፍትሕ ተቋሙ ተመሳሳይ ጥሰቶች እንዳይኖሩ ተግቶ ሊሥራ እንደሚገባው አመላካች ነው፡፡ በአስፈጻሚው አካል ክብር ያልተሰጠው ፍርድ ቤት በተራ ዜጋው ክብር ይሰጠዋል ማለት አስቸጋሪ ነው፡፡ ተመሳሳይ ድርጊቶች በፍርድ ቤቶች ወይም በዳኞች ላይ የሚፈጸሙ ከሆነ ፍርድ ቤቶች በኅብረተሰቡ ውስጥ ያላቸውን ክብርና መተማመን ማጣታቸው አይቀርም፡፡ የራሱን መብት የማያስከብር ፍርድ ቤት የሌላውን ዜጋ መብት እንዲያስከብር መጠበቅ ሞኝነት መሆኑ ነጋሪ አይፈልግም፡፡
መያዣ ለአንድ ግዴታ አፈፃፀም ማረጋገጫ የሚሰጥ የንብረት ዋስትና ነው፡፡ ዋና ግዴታ በሌለበት መያዣ ስለማይኖር መያዣ በንብረት ላይ የሚፈፀም ደባል ግዴታ (accessory obligation) ነው፡፡ መያዣ በሚንቀሳቀስ ወይም በማይንቀሳቀስ ንብረት ላይ የሚመሠረት ሲሆን በዚህ ጽሑፍ ምልከታ የሚደረግበት የአክሲዮን መያዣ የሚንቀሳቀስ ንብረት መያዣ /pledge/ በመሆኑ ከማይንቀሳቀስ ንብረት መያዣ ጋር በተገናኘ በንጽጽር ካልሆነ በቀር የሚነሱ ነጥቦች አይኖሩም፡፡ የፍትሐብሔር ሕጋችን ፕሌጅ ከውል የሚመሠረት ግዴታ እንደሆነ ይደነግጋል፡፡ የሕጉ አንቀጽ 2825 የመያዣ ውል ማለት አንድ ባለዕዳ በባለገንዘቡ በኩል የገባውን ግዴታ ለመፈፀም መቻሉን በማረጋገጥ መያዣ ተብሎ የሚጠራውን ዕቃ ለመስጠት የሚገደድበት ውል ማለት ነው ሲል ግልጽ ትርጉም ይሰጣዋል፡፡ በመያዣ ሊሰጥ የሚችለውን ነገር በመወሰን ረገድ የፍትሐብሔር ሕጉ የሚታይም ሆነ የማይታይ ተንቀሳቃሽ ንብረትን ሊያካትት እንደሚችል ይደነግጋል፡፡ ሕጉ በቁጥር 2829 በመያዣነት የሚሰጠው አንድ ተንቀሳቃሽ ንብረት (a chattel) ወይም በጠቅላላው ዕቃ ተብለው ከሚጠሩ ተንቀሳቃሽ ንብረቶች አንዱ (a totality of effects) ወይም አንድ የገንዘብ መጠየቂያ መብት ሰነድ (a claim) ወይም በአንድ ተንቀሳቃሽ ንብረት ላይ ያለ የመብት መጠየቂያ ሰነድ ለመሆን እንደሚችል ይደነግጋል፡፡ አክሲዮን የአንድ የንግድ ማኅበር (የአክሲዮን ማኅበር ወይም ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር) የአባልነት ማስረጃና በካፒታሉ ውስጥ ያለ ድርሻ (ጥቅም) ማረጋገጫ ነው፡፡ አክሲዮን የገንዘብ መጠየቂያ ሰነዶች (claims) ውስጥ የሚወድቅ ግዙፍነት የሌለው ተንቀሳቃሽ ንብረት (incorporeal Movable) ነው፡፡ የፍትሐብሔር ሕጉን አንቀጽ 1125 ይመለከቷል፡፡ አክሲዮን በመያዣ የሚሰጥበት የሕግ ማዕቀፍ በፍትሐብሔር ሕጉ ቁጥር 2863-2874 እንዲሁም በንግድ ሕጉ ቁጥር 329 ላይ የተካተተ ሲሆን በዚህ ጽሑፍ የአክሲዮን መያዣ የሚቋቋምበትን ሁኔታ እና አክሲዮን በመያዣ የተቀበለ ባለገንዘብ ያሉትን መብቶች የተመለከቱ ነጥቦችን ለማየት ሙከራ ይደረጋል፡፡
የሚንቀሳቀስ ንብረት መያዣ (ፕሌጅ) አመሠራረት