“ለእግረኛ ቅድሚያ በመከልከል…” ከሕግ አንጻር ሲታይ


በሀገራችን እጅግ አሳሳቢ እና አነጋጋሪ ከሆኑት የወንጀል ድርጊቶች መካከል በአሽከርካሪዎች የሚፈጸመው ወንጀል ቀዳሚውን ሥፍራ ይይዛል ለማለት ይቻላል፡፡ ከትራፊክ ፖሊስ ዕለታዊ ሪፖርት በየዕለቱ እንደምንሰማው በአዲስ አበባ ከተማ ብቻ እንኳን ያለበትን ሁኔታ ብንመለከት በንብረትና በሰው ላይ፣ ቢያንስ በአንደኛው ላይ አደጋ ሳይደርስ የዋለበት ቀን የለም ለማለት ይቻላል፡፡ የአደጋ ዜናው በ24 ሰዓት፣ በወርና በዓመት ስሌት ሲነገር ስንሰማው እጅግ አሳሳቢ ነገር ነው፡፡ በትርፊክ ፖሊስ የዘወትር ሪፖርት እንደምንሰማውም ብዙውን ጊዜ አደጋው የደረሰው ለእግረኛ ቅድሚያ መከልከል በአሽከርካሪ ጥፋት መሆኑን መዘገቡ የተለመደ ነው፡፡


በዚህ ጽሁፍ ፍተሻ የምናደርግባቸው ነጥቦች አሽከርካሪ አጥፍቷል ወይም በቸልተኝነት ወንጀል ፈጽሟል የሚባለው መቼ ነው; የወንጀል ድርጊቱን ለመከላከል/ለመቀነስ እግረኞችስ ምን ዓይነት ግዴታ አለባቸው; አደጋውን እያባባሱ ያሉት ዋና ዋና ሁኔታዎች ምንድን ናቸው; የሕግ ስርዓታችንና በፍርድ ቤቶች የተሰጠው ቦታስ ምን ይመስላል; የሚሉትንና ተያያዥነት ያላቸውን ነጥቦች ናቸው፡፡


ወደ ዝርዝር ነጥቦች ከመግባታችን በፊት ጭብጡን በፍርድ ቤቶች በታዩና ፍርድ በተሰጠባቸው ጉዳዮች ለመደገፍ ይቻል ዘንድ በቅድሚያ ሶስት ዐቃቤ ህግ የወንጀል ክስ ያቀረበባቸውንና ፍርድ ቤት ፍርድ የሠጠባቸውን ናሙና ጉዳዮችን በአጭሩ እንመልከት፡፡


ጉዳይ አንድ፡ ጊዜው ነሐሴ ወር 2002 ዓ.ም ነው፡፡ በ70ዎቹ የዕድሜ ክልል የሚገኙት አዛውንት ከኦሮሚያ ክልል አርሲ ዞን ለሥራ ጉዳይ በማለት ወደ አዲስ አበባ ይመጣሉ፡፡ አዛውንቱ ሥራ ያሉትም በመንገድ ላይ ገንዘብ ለምኖና አጠራቅሞ ወደመጡበት መመለስ ነበር፡፡ ሥራቸውንም በተክለሃይማኖት አካባቢ ባለው አስፋልት ላይ ቀኑን እንደ ሸማኔ መወርወሪያ ከግራ ወደቀኝ በመመላለስ በትጋት ሲያከናውኑ መዋል ጀመሩ፡፡ የልመና ገንዘቡም በዋናነት ከአሽከርካሪዎች እየተሰበሰበና እየተጠራቀመ ነው፡፡ ይሁንና በአንዲቷ ጎደሎ ቀን ከአንዱ አሽከርካሪ ሳንቲም ተቀብለው በሌላኛው ተሽከርካሪ ተከልለው መንገዱን ከቀኝ ወደ ግራ ሲያቋርጡ ከአንድ የጭነት ተሽከርካሪ አይሱዙ ጋር ይጋጩና ከአስፋልቱ ላይ ይወድቃሉ፡፡ አዛውንቱም የሰበሰቡትን ገንዘብ የት እንዳስቀመጡት ሳይናገሩና እንዳሰቡትም ወደ መጡበት ሳይመለሱ እንደወጡ ቀሩ፡፡ የትራፊክ ፖሊስ የአዛውንቱ ሞት በአሽከርካሪ ጥፋት ለእግረኛ ቅድሚያ መከልከል የተፈጸመ መሆኑን በመግለጽ ፕላኑን አዘጋጅቶና ሪፖርቱን ጽፎ ጉዳዩን ለዐቃቤ ህግ አስተላለፈ፡፡ ዐቃቤ ህግም በሪፖርቱ መሠረት ክሱን በ1996 ዓ.ም የወጣውን የወንጀል ህግ አንቀጽ 543/2/ ተላልፎ በቸልተኝነት ሰው መግደል የወንጀል ክስ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቀረበ፡፡


ጉዳይ ሁለት፡ ጊዜው በስድስተኛው ወር በ2002 ሲሆን አሽከርካሪዋ ሴት ነች፡፡ አሽከርካሪዋ ባለቤቷ ከዚህ ዓለም በሞት ሲለይ የነበራቸውን ጅምር ቤት በመሸጥ ሁለት ህጻናት ልጆቿን ለማሳደጊያ ይሆናት ዘንድ በማሰብ አንድ ትንሽ ላዳ ታክሴ በመግዛት ሹፌር ቀጥራ ገቢ ማግኘት ጀመረች፡፡ ሴትዮዋ ያላት የመንጃ ፈቃድ 2ኛ ሆኖባት እንጅ 3ኛ ቢሆን ኖሮ ታክሲዋን ራሷ በማሽከርከር ገቢዋን የተሻለ የማድረግ ሀሳቡ ነበራት፡፡ ሀሳቧን ከግብ ለማድረስም 3ኛ ደረጃ አሽከርካሪነት የሙያ ፈቃድ ለማግኘት ልምምድ ጀመረች፡፡ ነገር ግን ልምምዱ በተፈቀደላቸው አሰልጣኞችና የመለማመጃ ተሸከርካሪዎች ብቻ የተወሰነ አልነበረም፡፡ ከዚህ አልፎ በራሷ ታክሲ እና በሹፌሯ አለማማጅነት ልምምዷን በኮተቤ አስፋልት ቀጠለች፡፡ ይሁንና እንኳን በ3ኛ ደረጃ መንጃ ፈቃድ የሚነዳውን ተሸከርካሪ ማሽከርከር ይቅርና ችሎታዋ በ2ኛ ደረጃ ለሚሽከረከረውም አጥጋቢ አልነበረምና ከኋላ በተከተላትና ድምጹን በሰማቸው ከባድ ተሸከርካሪ ምክንያት በድንጋጤ ከመንገዱ በመውጣት በከባድ ቸልተኝነት የመንገዳቸውን ቀኝ ጠርዝ ይዘው ይጓዙ ከነበሩት ሴት ህጻናት ተማሪዎች መካከል በአንዷ ላይ የሞት አደጋ፣ በሁለቱ ላይ የአካል ጉዳት አደጋ በማድረስ ግቢ ጥሳ በመግባት በንብረትም ላይ ጉዳት የማድረስ ድረጊት ይፈጸማል፡፡ የትርፊክ ፖሊስም አደጋው የደረሰው ከመንጃ ፈቃድ ደረጃ ውጭ ደንብ በመተላለፍ፣ በአሽከርካሪ ጥፋት ለእግረኛ ቅድሚያ መከልከል የተፈጸመ መሆኑን በመግለጽ ፕላኑን አዘጋጅቶና ሪፖርቱን ጽፎ፣ አለማማጁንም ከምስክሮች መካከል አድርጎ (እያለማመደ የነበረ መሆኑን ክዷል) ጉዳዩን ለዐቃቤ ህግ አስተላለፈ፡፡ ዐቃቤ ህግም በሪፖርቱ መሠረት ክሱን በ1996 ዓ.ም የወጣውን የወንጀል ህግ አንቀጽ 543/2/ እና 559/2/ ተላልፎ በቸልተኝነት ሰው መግደል እና የአካል ጉዳት ማድረስ እንዲሁም በመንጃ ፈቃዱ ደንብ በመተላለፍ ሦስት የወንጀል ክሶችን በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቀረበ፡፡ 

Continue reading
  9232 Hits

አንዳንድ ነጥቦች ስለአዲሱ የመንገድ ትራፊክ መቆጣጠሪያ ማሻሻያ ደንብ ቁጥር 395/2009

 

በየካቲት ወር 2008 ዓ/ም መዲናችን አዲስ አበባ ላይ የመንገድ ትራንስፖርት ትራፊክ መቆጣጠሪያ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 208/2003 ዓ/ም የሪከርድ አያያዝ ትግበራ መጀመሩን ተከትሎ የታክሲ የአሽከርካሪዎች ስራ የማቆም አድማ ነበረ፡፡ በዚህም መሰረት ተግባራዊ መደረግ ተጀምሮ የነበረው የሪከርድ አያያዝ ተግባራዊነቱ እንዲቋረጥ ተደርጎ ከአሽከርካሪዎች እና ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት ከተደረገ በኋላ የደንቡ መሻሻል አስፈላጊነት ታምኖበት ደንቡ እንዲሻሻል ተደርጓል፡፡ በወቅቱ በአሽከርካሪዎች በኩል ሀገሪቱ ባላት የትራፊክ ተቆጣጣሪዎች ብቃት ደረጃ፣ የመንገድ መሰረተ ልማት ችግሮች፣ ልል የሆነ የትራፊክ ተቆጣጣሪዎች ተጠያቂነት፣ የተቆጣጣሪዎች ስነምግባር ችግር እንዲሁም ከብዙ ተያያዥ ጉዳዮች ጋር በተገናኘ በደንብ ቁጥር 208/2003 ዓ/ም ላይ ሪከርድን የሚመለከተው ክፍል ወደ ተግባር የሚገባ ከሆነ አስቸጋሪ ሁኔታዎች እንደሚፈጠርባቸው ለስራ ማቆም አድማው የተሰጡት ምክንያቶች ነበሩ፡፡ ደንቡ በ2003 ዓ/ም እንደመውጣቱ እሪከርድን የሚመለከተው ክፍል ተግባራዊ መደረግ የጀመረው በ2008 ዓ/ም መሆኑ በራሱ የህግ አስፈጻሚውን ቸልተኝነት የሚያሳይ ሲሆን ደንቡን በመተግበር ረገድ ቀድመው የጀመሩ እንደ አማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ያሉትን ደግሞ በክልላቸው የሚንቀሳቀሱትን አሽከርካሪዎች በሀገሪቷ ውስጥ ካሉ ሌሎች አሽከርካሪዎች በተለየ ሁኔታ ተጎጂ ሲያደርጋቸው ነበር፡፡ ይህ ጽሁፍ ደንቡ የተሻሻለበትን ምክንያቶች አግባብነት፣ ማሻሻያው ውስጥ የተጨመሩ እና ማስተካከያ የተደረገባቸውን አንቀጾች እንዲሁም የማሻሻያውን አንድምታ በተወሰነ መልኩ ለመዳሰስ ይሞክራል፡፡

የደንብ ቁጥር 208/2003 መሻሻል አስፈላጊነት

የመንገድ ትራንስፖርት ትራፊክ መቆጣጠሪያ የሚንስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 208/2003 ዓ/ም / ከዚህ በኋላ "ደንቡ" እያለ ይቀጥላል / በርከት ያሉ ድንጋጌዎች ከያዙ እና የመንገድ ትራፊክ ፍሰትን ለማሳለጥ ከሚያስችሉ መሰረታዊ ህጎች ውስጥ አንዱ ነው፡፡ ለዚህ ደንብ መሻሻል ገፊ ምክንያት የሆነው ከደንቡ የሪከርድ ክፍል ጋር በተያያዘ የተነሳው ተቃውሞ ቢሆንም ከጊዜ ቆይታ እና የሁኔታዎች ተለዋዋጭነት አንጻር እንዲሁም ደንቡ ቀድሞውንም ሲወጣ ከነበሩበት የህግ አወጣጥ ችግሮች ጋር በተያያዘ መሻሻል የነበረበት በመሆኑ የመንገድ ትራንስፖርት ትራፊክ መቆጣጠሪያ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ማሻሻያ ደንብ ቁጥር 395/2009 ዓ/ም /ከዚህ በኋላ "ማሻሻያው" እያለ ይቀጥላል /መውጣቱ ተገቢነት ያለው ነው፡፡ ይህ ደንብ ሲሻሻል ከግምት ውስጥ ሊያስገባ የሚገባው መሰረታዊ ነጥብ ቢኖር ሀገሪቷ በአሁኑ ሰአት ከየትኛውም አደጋ በላይ በአመት ከ5000 /አምስት ሺ/ የሚበልጥ የሰው ሂወት እየቀጠፈ እና ከባድ የሆነ የንብረት ውድመት እያስከተለ ያለውን የትራፊክ አደጋን መቀነስ ነው፡፡ ከዚህ አንጻር አብዛኞቹ የትራፊክ አደጋዎች የሚደርሱት በአሽከርካሪዎች ጥፋት መሆኑ እየታወቀ ሪከርድን የሚመለከተው የህጉ ክፍል የተሻሻለበት መንገድ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ከግምት ከማስገባት ይልቅ በነበረው ተቃውሞ ተጽእኖ ስር ሆኖ የተሻሻለ ነው፡፡ ይህንን ከታች በዝርዝር እንመለከተዋለን፡፡ ሪከርድን ከሚመለከተው ክፍል ውጪ የተሻሻለው የደንቡ ክፍል ከነ ክፍተቶቹም ቢሆን ከዚህ ቀደም በደንቡ ላይ ግልጽነት የጎደላቸውን ድንጋጌዎች ለማስተካከል ከመሞከሩም በላይ አዳዲስ አንቀጾችን በመጨመር የደንቡን ክፍተቶች ጥሩ በሚባል መልኩ አስተካክሏል፡፡

መሰረታዊ ማሻሻያ የተደረገባቸው እና አዲስ የተጨመሩ ድንጋጌዎች በከፊል

Continue reading
  20554 Hits