“ለእግረኛ ቅድሚያ በመከልከል…” ከሕግ አንጻር ሲታይ


በሀገራችን እጅግ አሳሳቢ እና አነጋጋሪ ከሆኑት የወንጀል ድርጊቶች መካከል በአሽከርካሪዎች የሚፈጸመው ወንጀል ቀዳሚውን ሥፍራ ይይዛል ለማለት ይቻላል፡፡ ከትራፊክ ፖሊስ ዕለታዊ ሪፖርት በየዕለቱ እንደምንሰማው በአዲስ አበባ ከተማ ብቻ እንኳን ያለበትን ሁኔታ ብንመለከት በንብረትና በሰው ላይ፣ ቢያንስ በአንደኛው ላይ አደጋ ሳይደርስ የዋለበት ቀን የለም ለማለት ይቻላል፡፡ የአደጋ ዜናው በ24 ሰዓት፣ በወርና በዓመት ስሌት ሲነገር ስንሰማው እጅግ አሳሳቢ ነገር ነው፡፡ በትርፊክ ፖሊስ የዘወትር ሪፖርት እንደምንሰማውም ብዙውን ጊዜ አደጋው የደረሰው ለእግረኛ ቅድሚያ መከልከል በአሽከርካሪ ጥፋት መሆኑን መዘገቡ የተለመደ ነው፡፡


በዚህ ጽሁፍ ፍተሻ የምናደርግባቸው ነጥቦች አሽከርካሪ አጥፍቷል ወይም በቸልተኝነት ወንጀል ፈጽሟል የሚባለው መቼ ነው; የወንጀል ድርጊቱን ለመከላከል/ለመቀነስ እግረኞችስ ምን ዓይነት ግዴታ አለባቸው; አደጋውን እያባባሱ ያሉት ዋና ዋና ሁኔታዎች ምንድን ናቸው; የሕግ ስርዓታችንና በፍርድ ቤቶች የተሰጠው ቦታስ ምን ይመስላል; የሚሉትንና ተያያዥነት ያላቸውን ነጥቦች ናቸው፡፡


ወደ ዝርዝር ነጥቦች ከመግባታችን በፊት ጭብጡን በፍርድ ቤቶች በታዩና ፍርድ በተሰጠባቸው ጉዳዮች ለመደገፍ ይቻል ዘንድ በቅድሚያ ሶስት ዐቃቤ ህግ የወንጀል ክስ ያቀረበባቸውንና ፍርድ ቤት ፍርድ የሠጠባቸውን ናሙና ጉዳዮችን በአጭሩ እንመልከት፡፡


ጉዳይ አንድ፡ ጊዜው ነሐሴ ወር 2002 ዓ.ም ነው፡፡ በ70ዎቹ የዕድሜ ክልል የሚገኙት አዛውንት ከኦሮሚያ ክልል አርሲ ዞን ለሥራ ጉዳይ በማለት ወደ አዲስ አበባ ይመጣሉ፡፡ አዛውንቱ ሥራ ያሉትም በመንገድ ላይ ገንዘብ ለምኖና አጠራቅሞ ወደመጡበት መመለስ ነበር፡፡ ሥራቸውንም በተክለሃይማኖት አካባቢ ባለው አስፋልት ላይ ቀኑን እንደ ሸማኔ መወርወሪያ ከግራ ወደቀኝ በመመላለስ በትጋት ሲያከናውኑ መዋል ጀመሩ፡፡ የልመና ገንዘቡም በዋናነት ከአሽከርካሪዎች እየተሰበሰበና እየተጠራቀመ ነው፡፡ ይሁንና በአንዲቷ ጎደሎ ቀን ከአንዱ አሽከርካሪ ሳንቲም ተቀብለው በሌላኛው ተሽከርካሪ ተከልለው መንገዱን ከቀኝ ወደ ግራ ሲያቋርጡ ከአንድ የጭነት ተሽከርካሪ አይሱዙ ጋር ይጋጩና ከአስፋልቱ ላይ ይወድቃሉ፡፡ አዛውንቱም የሰበሰቡትን ገንዘብ የት እንዳስቀመጡት ሳይናገሩና እንዳሰቡትም ወደ መጡበት ሳይመለሱ እንደወጡ ቀሩ፡፡ የትራፊክ ፖሊስ የአዛውንቱ ሞት በአሽከርካሪ ጥፋት ለእግረኛ ቅድሚያ መከልከል የተፈጸመ መሆኑን በመግለጽ ፕላኑን አዘጋጅቶና ሪፖርቱን ጽፎ ጉዳዩን ለዐቃቤ ህግ አስተላለፈ፡፡ ዐቃቤ ህግም በሪፖርቱ መሠረት ክሱን በ1996 ዓ.ም የወጣውን የወንጀል ህግ አንቀጽ 543/2/ ተላልፎ በቸልተኝነት ሰው መግደል የወንጀል ክስ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቀረበ፡፡


ጉዳይ ሁለት፡ ጊዜው በስድስተኛው ወር በ2002 ሲሆን አሽከርካሪዋ ሴት ነች፡፡ አሽከርካሪዋ ባለቤቷ ከዚህ ዓለም በሞት ሲለይ የነበራቸውን ጅምር ቤት በመሸጥ ሁለት ህጻናት ልጆቿን ለማሳደጊያ ይሆናት ዘንድ በማሰብ አንድ ትንሽ ላዳ ታክሴ በመግዛት ሹፌር ቀጥራ ገቢ ማግኘት ጀመረች፡፡ ሴትዮዋ ያላት የመንጃ ፈቃድ 2ኛ ሆኖባት እንጅ 3ኛ ቢሆን ኖሮ ታክሲዋን ራሷ በማሽከርከር ገቢዋን የተሻለ የማድረግ ሀሳቡ ነበራት፡፡ ሀሳቧን ከግብ ለማድረስም 3ኛ ደረጃ አሽከርካሪነት የሙያ ፈቃድ ለማግኘት ልምምድ ጀመረች፡፡ ነገር ግን ልምምዱ በተፈቀደላቸው አሰልጣኞችና የመለማመጃ ተሸከርካሪዎች ብቻ የተወሰነ አልነበረም፡፡ ከዚህ አልፎ በራሷ ታክሲ እና በሹፌሯ አለማማጅነት ልምምዷን በኮተቤ አስፋልት ቀጠለች፡፡ ይሁንና እንኳን በ3ኛ ደረጃ መንጃ ፈቃድ የሚነዳውን ተሸከርካሪ ማሽከርከር ይቅርና ችሎታዋ በ2ኛ ደረጃ ለሚሽከረከረውም አጥጋቢ አልነበረምና ከኋላ በተከተላትና ድምጹን በሰማቸው ከባድ ተሸከርካሪ ምክንያት በድንጋጤ ከመንገዱ በመውጣት በከባድ ቸልተኝነት የመንገዳቸውን ቀኝ ጠርዝ ይዘው ይጓዙ ከነበሩት ሴት ህጻናት ተማሪዎች መካከል በአንዷ ላይ የሞት አደጋ፣ በሁለቱ ላይ የአካል ጉዳት አደጋ በማድረስ ግቢ ጥሳ በመግባት በንብረትም ላይ ጉዳት የማድረስ ድረጊት ይፈጸማል፡፡ የትርፊክ ፖሊስም አደጋው የደረሰው ከመንጃ ፈቃድ ደረጃ ውጭ ደንብ በመተላለፍ፣ በአሽከርካሪ ጥፋት ለእግረኛ ቅድሚያ መከልከል የተፈጸመ መሆኑን በመግለጽ ፕላኑን አዘጋጅቶና ሪፖርቱን ጽፎ፣ አለማማጁንም ከምስክሮች መካከል አድርጎ (እያለማመደ የነበረ መሆኑን ክዷል) ጉዳዩን ለዐቃቤ ህግ አስተላለፈ፡፡ ዐቃቤ ህግም በሪፖርቱ መሠረት ክሱን በ1996 ዓ.ም የወጣውን የወንጀል ህግ አንቀጽ 543/2/ እና 559/2/ ተላልፎ በቸልተኝነት ሰው መግደል እና የአካል ጉዳት ማድረስ እንዲሁም በመንጃ ፈቃዱ ደንብ በመተላለፍ ሦስት የወንጀል ክሶችን በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቀረበ፡፡ 

Continue reading
  10272 Hits

የንግድ ፈቃድን ማከራየት በወንጀል ያስቀጣል?


በሀገራችን የንግድ ሕግ ሥርዓት መሠረት ነጋዴነት ምን መብቶችና ግዴታዎች አሉበት? ለመሆኑ አንድ ነጋዴ በሥሙ ያወጣውን የንግድ ፈቃድ ለሌላ ሰው ማከራየትና በኪራይ ውል ማስተላለፍ ይችላል? አከራይቶ ቢገኝስ በወንጀል ሊያስከስሰውና ሊያስቀጣው ይችላልን? የነጋዴነት መብቶችና ግዴታዎች በየትኞቹ ህግጋት ይገዛል? የነጋዴዎችን መብትና ግዴታዎች በዋናነት የሚመለከቱት ሕግጋት በአዋጅ ቁጥር 166/1952 የወጣውና ከመስከረም 1 ቀን 1953 ዓ.ም ጀምሮ በሥራ ላይ የዋለው የንግድ ሕግ፣ የንግድ ምዝገባና ፈቃድ አዋጅና ደንብ እና ግብርን የሚመለከቱ ሕጎች ሲሆኑ ሌሎች ህግጋትም እንደ የውል ሕግ፣ የኪራይ ሕግ፣ የአሠሪና ሠራተኛ ሕግ፣ የወንጀል ሕግ.... በነጋዴዎች ላይ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የሚያስከትሉት መብትና ግዴታዎች ይኖራሉ፡፡ በዚህ አጭር ጽሁፍ ስለ ነጋዴዎች መብትና ግዴታዎች በዝርዝር ለመጻፍ የማይቻል በመሆኑ ጽሁፉ ለመዳሰስ የሚሞክረው በነጋዴነት የተመዘገበ የንግድ ፈቃድ የተሰጠው ሰው የንግድ ፈቃዱን ለሦስተኛ ወገን በኪራይ ውል ማስተላለፍ ህጋዊ መብት አለው ወይስ የለውም? የሚለውን ጭብጥ ነው፡፡


ጽሁፉን በተጨባጭ የፍርድ ቤት ጉዳይ ለመደገፍ ይቻል ዘንድ የሚከተለውን አንድ ጉዳይ እንመልከት፡-
አቶ ተፈራ… (ስሙ ለጽሑፉ ሲባል የተቀየረ) ባለትዳርና የልጆች አባት ሲሆን በባለቤቱ ሥም በቅድመ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት አገልግሎት በሚል ዘርፍ በአፀደ ሕጻናት አገልግሎት የንግድ ፈቃድ የወጣበትን ድርጅት ለማስተዳደር የውክልና ስልጣን የተሰጠው በመሆኑ በራሱ እየሠራበት እያለ በጤና እና በሌሎች ምክንያቶች ድርጅቱን የማስተማር ልምድ ካለው ሰው ጋር በኪራይ ለማሠራት ተስማምተው በጽሑፍ የኪራይ ውል አስተላለፈው፡፡ ይሁንና ተከራይው ግለሰብ ድርጅቱን እንደ ባለቤቱ/ወኪሉ ሆኖ ለመምራት ባለመቻሉ የተማሪዎች ቁጥር እየቀሰነበትና ኪሣራ እየደረሰበት በመምጣቱ በመሐከላቸው አለመግባባት በመፈጠሩ በፍትሐብሔሩ አለመግባባት ጉዳዩ ወደ ፍ/ቤት ደረሰ፡፡ ተከራይው ግለሰብ የንግድ ፈቃዱን ተከራይቶ መሥራቱን ለተቆጣጣሪ አካላት መረጃ በመስጠቱ አቶ ተፈራ በፖሊስ ለምርመራ እንደሚፈለግ ጥሪ ደርሶት የወንጀል ምርመራ ተደረገበት፡፡ ጉዳዩ በምርመራ ብቻ ሳያበቃ በፌዴራል ዐቃቤ ሕግ የንግድ ምዝገባና ፈቃድ አዋጅ ቁጥር 686/2002 ድንጋጌዎችን በመተላለፍ የንግድ ፈቃድን ማከራየት ወንጀል ፈጽመሃል በማለት በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ክስ ቀርቦበት በወንጀል ተከሳሽ ሳጥን ለመቆም በቃ፡፡ ተከሳሽ ክሱ ደርሶት ስለ ድርጊቱ በፍርድ ቤቱ ሲጠየቅ ድርጅቱን ማከራየቱን ሳይክድ፣ ያከራየሁት መብቴን ተጠቅሜ የድርጅቱን መልካም ዝና እንጅ የንግድ ፈቃዱን ብቻ ነጥዬ ለሌላ ሰው ያላከራየሁ በመሆኑ ጥፋተኛ አይደለሁም በማለት ክርክሩን አቅርቧል፡፡ ከንግድ ሕጉና ከንግድ ምዝገባና ፈቃድ አዋጁ አንጻር ተከሳሽ በወንጀል ጥፋተኛ ሊሆን ይችል ይሆን? በህጉ መሠረት የንግድ ፈቃድን ማከራየት የንግድ መደብርን ከማከራየት ተለይቶ የሚታይ ነውን? በተከሳሽ ላይ የቀረበውን ክስና የክርክሩን ውጤት ወደኋላ እናቆየውና በቅድሚያ ለጉዳዩ አግባብነት ያላቸውን የህጉን ድንጋጌዎች እንመልከት፡፡


በንግድ ሕጉ ስለ ነጋዴዎችና ስለ ንግድ መደብሮች በሚለው ክፍል በአንቀጽ 5 ሥር ስለ ነጋዴነት ትርጉም ሲገልጽ “ነጋዴዎች” የሚባሉት ሰዎች የሞያ ሥራቸው አድርገው ጥቅም ለማግኘት ሲሉ በህጉ የንግድ ሥራዎች ተብለው የተቆጠሩትን ሥራዎች የሚሠሩ ሰዎች መሆናቸውን ተደንግጓል፡፡ በንግድ ሕጉና በንግድ ምዝገባና ፈቃድ አዋጁ መሠረት የንግድ ሥራዎች ተብለው ከተዘረዘሩት ሥራዎች መካከል ለምሳሌ፡- ጥሬ ዕቃዎችን ወይም ምርቶችን ገዝተው/አምርተው የሚሸጡ፣ ህንጻዎችን/ዕቃዎችን የሚያከራዩ፣ የሆቴል፣ የምግብ ቤት፣የቡና ቤት፣ የመጠጥ ቤት፣የመኝታ ቤት… አገልግሎት የሚሰጡ፣ የትምህርት አገልግሎት የሚሰጡ፣ የላኪነትና አስመጭነት፣ የጉምሩክ አስተላላፊነት…ወ.ዘ.ተ ሥራ በንግድ መዝገብ ተመዝገበውና የንግድ ፈቃድ አውጥተው የሚሠሩ ሰዎች ናቸው፡፡ ሰዎች የሚለው እንደአግባብነቱ የተፈጥሮ ወይም የሕግ ሰውነት የተሰጣቸውን ሁሉ የሚወክል ነው፡፡ 
በንግድ ህጉ አንቀጽ 100 በኢትዮጵያ ግዛት ውስጥ የንግድ ሥራ የሚሠራ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ወይም የውጭ አገር ሰው ወይም የንግድ ማህበር በመዝገብ መግባት እንዳለበት በአስገዳጅነት ተደንግጓል፡፡ በአንቀጽ 105 እንደተደነገገው አንድ ነጋዴ ለመመዝገብ ማመልከቻ ሲያቀርብ ከሚገልጻቸው መረጃዎች መካከልም የቤተዘመድ ስሙ፣ የተወለደበት ቀንና ቦታ፣ ዜግነቱ፣ የግል አድራሻው፣ የጋብቻ ሁኔታ፣ የንግዱ ዓላማ፣ የንግዱ ሥም፣ ሥራ አስኪያጅ ካለው ስሙንና ሥልጣኑን ይገኙበታል፡፡ እነዚህ ሁኔታዎች በንግድ መዝገብ የመግባታቸው አስፈላጊነት የንግድ ሥራ ፈቃድ በግለሰቡ ማንነት የተወሰነ እንዲሆን ታስቦ ይሆን? የሚል ጥያቄ ያስነሳል፡፡ በንግድ ህጉ አንቀጽ 112 መነገድን ስለመተው በተደነገገው መሠረት ደግሞ ማንኛውም የተመዘገበ ነጋዴ የተመዘገበውን የንግድ ሥራውን በማናቸውም ምክንያት በተወ ጊዜ ወይም የንግዱን መደብር በአከራየ ጊዜ በሁለት ወር ውስጥ ከመዝገቡ እንዲሰረዝ ማመልከቻ ማቅረብ እንደሚገባው ተደንግጓል፡፡


የነጋዴነት ሥራ የቫት(የተጨማሪ እሴት ታክስን ጨምሮ) ከግብር ክፍያና በሽያጭ መመዝገቢያ ማሽን ደረሰኝ ግብይት የማከናወን ግዴታ ፣ ከሦስተኛ ወገኖች ወይም የብድርና ሌላ ውል ተዋዋዮች መብት፣ ከወንጀል ኃላፊነት፣ ከሠራተኞች መብት እና ከሌሎች ጉዳዮች ጋር ዘርፈ ብዙ የመብትና ግዴታ ግንኙነት ያለው መሆኑ ይታወቃል፡፡ ከዚህ አንጻርም የንግድ ፈቃድን በማከራየት የንግዱ ሥራ ቢሠራ በአገልግሎቱ ጥራት፣ በተገልጋይው መብት፣ በንግዱ ቁጥጥር፣ በግብር ክፍያ፣ በተጠያቂነትና በሌሎች ሁኔታዎች ላይ የሚያመጣው አሉታዊ ውጤት ይኖረዋልን? የሚለውን ሥጋቶች ለመከላከል የንግድ ፈቃዱን ላልተፈቀደለት ሰው በኪራይ እንዳይተላለፍ በሕግ መከልከሉ መፍትሔ ይሆናል የሚል ሃሳብ ያጭራል፡፡


በአሁኑ ወቅት በሥራ ላይ ያለው የንግድ ምዝገባና ፈቃድ አዋጅ ቁጥር 686/2002 ከመውጣቱ በፊት ከ13 ዓመታት በላይ በሥራ ላይ በነበረው አዋጅ ቁጥር 67/1989 ማንኛውም ሰው በንግድ መዝገብ ሳይመዘገብ የንግድ ሥራ መሥራት እንደማይችል፣ የንግድ ድርጅት ለሌላ ሰው በሚተላለፍበት ጊዜ የቀድሞው ፈቃድ ተመላሽ ተደርጎ ድርጅቱ የተላለፈለት ሰው በስሙ ፈቃድ ማውጣት እንዳለበት የተደነገገ ሲሆን በአዋጁ መሠረት በወጣው ደንብ ቁጥር 13/1989 መሰረትም ከአዋጁ በተመሳሳይ ሁኔታ ነጋዴው የቅርብ ጊዜ ፎቶ ግራፉንና ሌሎች ዝርዝር ሁኔታዎችን አሟልቶ መመዝገብ እንዳለበት በአስገዳጅነት ተደንግጓል፡፡ 

Continue reading
  13231 Hits

ስለ “የታሰሩ ሰዎች መብቶች” አንዳንድ ነጥቦች

 

በማያ ጋዜጣ ሐምሌ የታተመ በሰሞኑ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የችሎት ውሎዎች በፌዴራል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ እና በፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን የጋራ የወንጀል ሕጉን የማስፈጸም ተግባር ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎች፣ የተለያዩ መንግስታዊ መሥሪያ ቤቶች ዳይሬክተሮችን ጨምሮ በሙስና ወንጀል ተጠርጣሪነት ተይዘው የጊዜ ቀጠሮ እየተጠየቀባቸው የሚገኙት እስከ ሣምንቱ አጋማሽ ድረስ ቁራቸው 45 የደረሱ ተጠርጣሪዎች በእሥር ላይ የሚገኙ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ የሕግ እርምጃው ቀጣይነት ያለው መሆኑንም በመንግስት መገናኛ ብዙሃን በኢቢሲ መግለጫ ተነግሯል፡፡ የተጠርጣሪዎችን በእሥር ላይ መዋል ተከትሎ በመንግስትም ሆነ በግል መገናኛ ብዙሃን ተጠርጣሪዎቹ ፈጽመውታል ተብሎ ስለተጠረጠሩበት ወንጀል ዝርዝር የገንዘቡን መጠን ጨምሮ በስፋት ሲዘገብ እየተመለከትንና በጋዜጦች እያነበብን ነው፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ ተጠርጣሪዎቹን በሕግ መሠረት በቁጥጥር ሥር አውሎ፣ ክስ አቅርቦ ጥፋተኝነታቸው በማስረጃ የተረጋገጠባቸውን በህጉ መሠረት እንዲቀጡ ማድረግ መሰረታዊ የህግ ዓላማ እንዲሁም አንደኛው የሕግ አስፈጻሚዎች ሥልጣንና ተግባር ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ በእሥር ላይ የሚገኙት ተጠርጣሪ እሥረኞችን ሕገመንግሥታዊ መብቶችን የማክበሩ ጉዳይም ከተጠያቂነቱና የወንጀል ህጉን ከማስፈጸሙ እኩል ጎን ለጎን ትኩረትን የሚሻ ነው፡፡ የሰዎች መብቶችና ግዴታዎች ሁል ጊዜ ጎን ለጎን በትይዩ የሚፈጸሙ መሆናቸው መሠረታዊ የህግ መርህ ነው፡፡ 


ከላይ የተጠቀሱትን ተጠርጣሪዎችን ጨምሮ ካሁን በፊት በሙስናም ሆነ በሌሎች ወንጀሎች ተጠርጥረው በእሥር ቤት/ በማረሚያ ቤት በሚገኙ ተከሳሾች የፍርድ ቤት ችሎት ውሎዎች የታሰሩ ሰዎችን መብቶች በተመለከተ የሚነሱ ዘርፈ ብዙ የመብት ጥያቄዎች፣ የመብት ጥሰት አቤቱታዎችና ክርክሮች ተደጋግመው ሲነሱ ይስተዋላል፡፡ የዛሬው የጽሁፋችን ርእስና ጭብጥ ሆኖ የተመረጠው ይህንኑ የእስረኞችን መብት ጉዳይ የሚመለከት ነው፡፡ በኢፌዲሪ ሕገመንግስት ከአንቀጽ 13 እስከ 44 ስለ ሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ከተደነገጉት መካከል በአንቀጽ 21 ሥር በጥበቃ ሥር ያሉና በፍርድ የታሰሩ ሰዎች መብት ከሰብአዊ መብቶች መካከል አንደኛው ሕገመንግስታዊ መብት መሆኑን ተደንግጓል፡፡ 
የሕገመንግስቱ አንቀጽ 21 ሁለት ንዑሳን ድንጋጌዎች እንደሚከተለው ይነበባሉ፡- 
(1) በጥበቃ ሥር ያሉና በፍርድ የታሰሩ ሰዎች ሰብዓዊ ክብራቸውን በሚጠብቁ ሁኔታዎች የመያዝ መብት አላቸው፡፡

(2) ከትዳር ጓደኞቻቸው፣ ከቅርብ ዘመዶቻቸው፣ ከጓደኞቻቸው፣ ከሃይማኖት አማካሪዎቻቸው፣ ከሐኪሞቻቸው እና ከሕግ አማካሪዎቻቸው ጋር ለመገናኘትና እንዲጎበኟቸውም ዕድል የማግኘት መብት አላቸው፡፡

ለመሆኑ የታሰሩ ሰዎች ምን መብት አላቸው? መብቶቻቸውስ በየትኞቹ የሀገራችን ህግጋት ጥበቃ ተደርጎላቸዋል? የመብት ጥበቃውስ ከማን ነው? ጠባቂውስ ማን ነው? የት፣ መቼና እንዴትስ ይጠበቃል? ጽሁፉ እንዚህንና ተያያዥ ጭብጦችን ይዳስሳል፡፡

Continue reading
  13360 Hits