የአስተዳደር ወሰን እና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን ሕገ-መንግሥታዊነት

ባለፈው ሳምንት መጨረሻ መንግሥት የአስተዳደር ወሰን እና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽንን የሚያቋቁም አዋጅ ማፅደቁ ይታወቃል፡፡ አዋጁ በተወካዮች ምክር ቤት ውስጥ የጦፈ ክርክርን አስነስቶ በ33 ተቃውሞ እና በ4 ድምፀ ተዓቅቦ በአብላጫ ድምፅ ቢፀድቅም በፓርላማ ውስጥ ለአዋጁ ድምፅ ከነፈጉ የሕዝብ ተወካዮች ጀምሮ እስከ ክልል መንግሥታት ድረስ ሰፊ ተቃውሞን አስተናግዷል፡፡ ለተቃውሞው መነሻ የሆነው ዋነው ጉዳይ የማንነትም ሆነ በክልሎች መካከል የሚነሱ አለመግባባቶችን መፍታት የፌዴሬሽን ምክር ቤት እና የክልሎች ሥልጣን ሆኖ ሳለ ሌላ ተቋም የማቋቋም አስፈላጊነት እና ሕገ መንግሥታዊነት ጥያቄ ነው፡፡

ለእነዚህ ጉዳዮች በሕግ አግባብ መልስ ለመስጠት ሁለት ጉዳዮችን በጥልቀት ማገናዘብ ይጠይቃል፡፡ አንደኛው እና መሠረታዊው ጉዳይ በሕገመንግሥቱ እና በሥራ ላይ በነበሩ ሕጎች  መሠረት የማንነት እና ራስን የማስተዳደር ጥያቄዎች እንዲሁም በክልሎች መካከል የሚነሱ አለመግባባቶች የሚፈቱበት ሥርዓት ምን እንደሆነ መፈተሸ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ለኮሚሽኑ የተሰጠውን ሥልጣን እና ተግባር ከሕገ-መንግሥቱ ጋር በንፅፅር አይቶ ሕገ መንግሥታዊነቱን መመርመር ነው፡፡

የማንነት እና ራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄዎች

በሕገ መንግሥቱ መሠረት የማንነት እና ራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄዎችን የመፍታተት ሥልጣን በመሰረታዊነት የተሰጠው ለክልሎች (ምክር ቤት) ነው፡፡ ነገር ግን የመጨረሻ ውሳኔ የመስጠት ሥልጣን የፌዴሬሽን ምክር ቤት መሆኑ በሕገ መንግሥቱ ከመደንገጉም በላይ በአዋጅ ቁጥር 251/1993 እንደተቀመጠው ክልሎች ለቀረበላቸው ጥያቄ በአንድ ዓመት ውስጥ አጥጋቢ መልስ ካልሰጡ ጥያቄው በይግባኝ መልክ ለፌዴሬሽ ምክር ቤት ቀርቦ የመጨረሻ ውሳኔ ማግኘት ይችላል፡፡

በመሠረቱ በማንነት እና ራስን በራስ በማስተዳደር ጥያቄዎች መሀል ምን ልዩነት እና አንድነት እንዳለ በግልፅ ያስቀመጠ ሕግ የለም፡፡ በሕገ መንግሥቱና በሌሎች ሕጎችም ራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄ እንጂ ‹የማንነት ጥያቄ› በሚል አገላለፅ የተቀመጠ መብትም ሆነ ሥርዓት የለም፡፡ ከዚህ ባለፈም በአንዳንዶች ዘንድ በክልሎች መካከል የሚነሱ የወሰን አለመግባባቶች እና በማንነት ጥያቄዎች መካከል ያለውን ልዩነት ያለመረዳት ስህተት ይስተዋላል፡፡ በዚህ ላይ የሚነሱ ክፍተቶች እና አከራካሪ ጉዳዮች በሌላ ሰፊ ጽሑፍ ቢታዩ ተመራጭ ስለሆነ ዝርዝሩን በመተው ወደ ቀጣዩ ጉዳይ እናልፋለን፡፡

Continue reading
  10120 Hits

የፌዴሬሽኑ አባል ክልሎች የፌዴራሉን መንግሥት ሕጎች አልፈፅምም ማለት ይችሉ ይሆን?

መግቢያ

የፌዴራል የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 53 መሠረት በተቋቋመ ወዲህ ላለፉት 24 ዓመታት በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ከ1100 በላይ አዋጆችን ያወጣ ሲሆን ከእነዚህም አዋጆች ውስጥ በምክር ቤቱ በሚገኙ የገዢው ፓርቲ አባላት መካከል ሞቅ ያሉ ክርክሮችና የልዩነት ሃሳቦች ያስተናገዱ በጣት የሚቆጠሩ አዋጆች መሆናቸው የሚታወቅ ነው፡፡ ሞቅ ያሉ ንትርክ አዘልና የልዩነት ሃሳቦች ከተንፀባረቁባቸው ሕጎች መካከል ለአብነት ያህል በሚንስትሮች ምክር ቤት ከየካቲት 06 ቀን 2010 ዓ.ም ጀምሮ ተፈፃሚነት የነበረውንና ለሁለተኛ ጊዜ በሚኒስትሮች ምክር ቤት አዋጅ ቁጥር 2/2010 የታወጀውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተቀባይነት እንዲያገኝ በቀረበ ወቅት የተደረገው እልህ አስጨራሽ ክርክር የቅርብ ጊዜ ትውስታ ነው፡፡

በተመሳሳይ መልኩ የአስተዳደር ወሰን እና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 1101/2011 የፀደቀባት ሁኔታ የጋለ ክርክርን ያስተናገደ ነበር፡፡ የፌዴራሉ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ታህሳስ 11 ቀን 2011 ዓ.ም ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ የኮሚሽኑን ማቋቋሚያ አዋጅን በ33 ተቃውሞ በ4 ድምፅ ተዓቅቦ በአብላጫ ድምፅ አፅድቋል፡፡ በዚህ አዋጅ ላይ የተደረገው ክርክርና የሰላ ሂስ በምክር ቤቱ ባሉአባላት ብቻ ሳይወሰን ከምክር ቤቱ ውጪ ባሉ የፖለቲካና የሕግ ሊሂቃን መካከል የከረረ ክርክርና ትችት ሲያስተናግድ ሰንብቷል፡፡

የኮሚሽኑን ማቋቋሚያ አዋጅ ሕገ-መንግሥታዊነቱንና ሥልጣኑን በተመለከተ የሚቀርበው ድጋፍና ትችት በግለሰቦች ደረጃ ብቻ የቀረ ሳይሆን የትግራይ ክልል ምክር ቤት በጥር 18 ቀን 2011 ዓ.ም ባካሄደው 5ኛ ዓመት 14ኛ መደበኛ ጉባዔ ላይም የመከራከሪያ አድማስ ሆኖ በአዋጅ አፈፃፀም ላይ የክልል ምክር ቤቱን የውሳኔ ሃሳብ እስከማሰጠት ደርሷል፡፡

የዚህ ጽሑፍ መነሻ ሃሳብም የትግራይ ክልል ምክር ቤት በኮሚሽኑ ማቋቋሚያ አዋጅ ላይ በሰጠው የውሳኔ ሃሳብ ላይ ሲሆን በዚህም አግባብ የክልሉ ምክር ቤት የፌዴራሉን መንግሥት ሕጎች አልተገብርም ማለቱን ከኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ-መንግሥት አንፃር ያለውን ውጤት እና የአስተዳደር ወሰን እና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን ሥልጣንና ተግባርን አጠቃላይ እንድምታ የምንዳስስ ይሆናል፡፡

Continue reading
  11064 Hits