የፌዴሬሽኑ አባል ክልሎች የፌዴራሉን መንግሥት ሕጎች አልፈፅምም ማለት ይችሉ ይሆን?

መግቢያ

የፌዴራል የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 53 መሠረት በተቋቋመ ወዲህ ላለፉት 24 ዓመታት በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ከ1100 በላይ አዋጆችን ያወጣ ሲሆን ከእነዚህም አዋጆች ውስጥ በምክር ቤቱ በሚገኙ የገዢው ፓርቲ አባላት መካከል ሞቅ ያሉ ክርክሮችና የልዩነት ሃሳቦች ያስተናገዱ በጣት የሚቆጠሩ አዋጆች መሆናቸው የሚታወቅ ነው፡፡ ሞቅ ያሉ ንትርክ አዘልና የልዩነት ሃሳቦች ከተንፀባረቁባቸው ሕጎች መካከል ለአብነት ያህል በሚንስትሮች ምክር ቤት ከየካቲት 06 ቀን 2010 ዓ.ም ጀምሮ ተፈፃሚነት የነበረውንና ለሁለተኛ ጊዜ በሚኒስትሮች ምክር ቤት አዋጅ ቁጥር 2/2010 የታወጀውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተቀባይነት እንዲያገኝ በቀረበ ወቅት የተደረገው እልህ አስጨራሽ ክርክር የቅርብ ጊዜ ትውስታ ነው፡፡

በተመሳሳይ መልኩ የአስተዳደር ወሰን እና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 1101/2011 የፀደቀባት ሁኔታ የጋለ ክርክርን ያስተናገደ ነበር፡፡ የፌዴራሉ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ታህሳስ 11 ቀን 2011 ዓ.ም ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ የኮሚሽኑን ማቋቋሚያ አዋጅን በ33 ተቃውሞ በ4 ድምፅ ተዓቅቦ በአብላጫ ድምፅ አፅድቋል፡፡ በዚህ አዋጅ ላይ የተደረገው ክርክርና የሰላ ሂስ በምክር ቤቱ ባሉአባላት ብቻ ሳይወሰን ከምክር ቤቱ ውጪ ባሉ የፖለቲካና የሕግ ሊሂቃን መካከል የከረረ ክርክርና ትችት ሲያስተናግድ ሰንብቷል፡፡

የኮሚሽኑን ማቋቋሚያ አዋጅ ሕገ-መንግሥታዊነቱንና ሥልጣኑን በተመለከተ የሚቀርበው ድጋፍና ትችት በግለሰቦች ደረጃ ብቻ የቀረ ሳይሆን የትግራይ ክልል ምክር ቤት በጥር 18 ቀን 2011 ዓ.ም ባካሄደው 5ኛ ዓመት 14ኛ መደበኛ ጉባዔ ላይም የመከራከሪያ አድማስ ሆኖ በአዋጅ አፈፃፀም ላይ የክልል ምክር ቤቱን የውሳኔ ሃሳብ እስከማሰጠት ደርሷል፡፡

የዚህ ጽሑፍ መነሻ ሃሳብም የትግራይ ክልል ምክር ቤት በኮሚሽኑ ማቋቋሚያ አዋጅ ላይ በሰጠው የውሳኔ ሃሳብ ላይ ሲሆን በዚህም አግባብ የክልሉ ምክር ቤት የፌዴራሉን መንግሥት ሕጎች አልተገብርም ማለቱን ከኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ-መንግሥት አንፃር ያለውን ውጤት እና የአስተዳደር ወሰን እና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን ሥልጣንና ተግባርን አጠቃላይ እንድምታ የምንዳስስ ይሆናል፡፡

Continue reading
  11063 Hits