የአስተዳደር ወሰን እና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን ሕገ-መንግሥታዊነት

ባለፈው ሳምንት መጨረሻ መንግሥት የአስተዳደር ወሰን እና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽንን የሚያቋቁም አዋጅ ማፅደቁ ይታወቃል፡፡ አዋጁ በተወካዮች ምክር ቤት ውስጥ የጦፈ ክርክርን አስነስቶ በ33 ተቃውሞ እና በ4 ድምፀ ተዓቅቦ በአብላጫ ድምፅ ቢፀድቅም በፓርላማ ውስጥ ለአዋጁ ድምፅ ከነፈጉ የሕዝብ ተወካዮች ጀምሮ እስከ ክልል መንግሥታት ድረስ ሰፊ ተቃውሞን አስተናግዷል፡፡ ለተቃውሞው መነሻ የሆነው ዋነው ጉዳይ የማንነትም ሆነ በክልሎች መካከል የሚነሱ አለመግባባቶችን መፍታት የፌዴሬሽን ምክር ቤት እና የክልሎች ሥልጣን ሆኖ ሳለ ሌላ ተቋም የማቋቋም አስፈላጊነት እና ሕገ መንግሥታዊነት ጥያቄ ነው፡፡

ለእነዚህ ጉዳዮች በሕግ አግባብ መልስ ለመስጠት ሁለት ጉዳዮችን በጥልቀት ማገናዘብ ይጠይቃል፡፡ አንደኛው እና መሠረታዊው ጉዳይ በሕገመንግሥቱ እና በሥራ ላይ በነበሩ ሕጎች  መሠረት የማንነት እና ራስን የማስተዳደር ጥያቄዎች እንዲሁም በክልሎች መካከል የሚነሱ አለመግባባቶች የሚፈቱበት ሥርዓት ምን እንደሆነ መፈተሸ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ለኮሚሽኑ የተሰጠውን ሥልጣን እና ተግባር ከሕገ-መንግሥቱ ጋር በንፅፅር አይቶ ሕገ መንግሥታዊነቱን መመርመር ነው፡፡

የማንነት እና ራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄዎች

በሕገ መንግሥቱ መሠረት የማንነት እና ራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄዎችን የመፍታተት ሥልጣን በመሰረታዊነት የተሰጠው ለክልሎች (ምክር ቤት) ነው፡፡ ነገር ግን የመጨረሻ ውሳኔ የመስጠት ሥልጣን የፌዴሬሽን ምክር ቤት መሆኑ በሕገ መንግሥቱ ከመደንገጉም በላይ በአዋጅ ቁጥር 251/1993 እንደተቀመጠው ክልሎች ለቀረበላቸው ጥያቄ በአንድ ዓመት ውስጥ አጥጋቢ መልስ ካልሰጡ ጥያቄው በይግባኝ መልክ ለፌዴሬሽ ምክር ቤት ቀርቦ የመጨረሻ ውሳኔ ማግኘት ይችላል፡፡

በመሠረቱ በማንነት እና ራስን በራስ በማስተዳደር ጥያቄዎች መሀል ምን ልዩነት እና አንድነት እንዳለ በግልፅ ያስቀመጠ ሕግ የለም፡፡ በሕገ መንግሥቱና በሌሎች ሕጎችም ራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄ እንጂ ‹የማንነት ጥያቄ› በሚል አገላለፅ የተቀመጠ መብትም ሆነ ሥርዓት የለም፡፡ ከዚህ ባለፈም በአንዳንዶች ዘንድ በክልሎች መካከል የሚነሱ የወሰን አለመግባባቶች እና በማንነት ጥያቄዎች መካከል ያለውን ልዩነት ያለመረዳት ስህተት ይስተዋላል፡፡ በዚህ ላይ የሚነሱ ክፍተቶች እና አከራካሪ ጉዳዮች በሌላ ሰፊ ጽሑፍ ቢታዩ ተመራጭ ስለሆነ ዝርዝሩን በመተው ወደ ቀጣዩ ጉዳይ እናልፋለን፡፡

Continue reading
  10120 Hits