በክፍል 1 ላይ ጸሐፊው ስለ አጠቃላይ የዋስትና የሕግ ማዕቀፍ በአጭሩ ለማቅረብ ሞክሯል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ ስለ ኮንስትራክሽን ዋስትና ምንነት፣ ዓይነቶች እንዲሁም በተግባር የሚታዩ ክፍተቶች ይዳስሳል፡፡
1. የኮንስትራክሽን ዋስትና (Construction security)
በኮንስትራክሽን ውል አፈጻጸም ወቅት በርካታ የዋስትና ዓይነቶች ሲተገበሩ ይታያል፡፡ ከቅድመ ግንባታ ጀምሮ በግንባታ ወቅት አንዳንዴም ከግንባታ በኋላ ለሚከሰቱ ችግሮች ዋስትና ጥቅም ላይ ሲውል ይሰተዋላል፡፡ በተለይም የህንጻ አሰሪዎች (Clients) ግንባታው በፈለጉት ጊዜና ዕቅድ መሰረት እንዲካናወንላቸው ካላቸው ጽኑ ፍላጎት የተነሳ ውሉ እንዲፈጸምላቸው አሰፈላጊ ከለላ እንዲኖራቸው ይሻሉ፡፡
በኢትዮጵያም አብዛኛው የኮንስትራክሽን ውሎች መንግስት አሰሪ በመሆን የሚቀርብባቸው ናቸው፡፡ ለማሳያ ያህል የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች ግንባታ፣ የኢንዲስትሪ ፓርኮች ግንባታ፣ የባቡር ዝርጋታ፣ የመንገድ ግንባታዎች ወዘተ ተጠቃሽ ናቸው፡፡ በተለምዶው የመንግስት ኪስ እርጥብ (solvent) ነው ቢባልም በውል አስተዳደር ወቅት በተለያዩ ምክንያቶች የክፍያ መዘግየት ይስተዋላል፡፡ በዚህ ጊዜም ሥራ ተቋራጩ ልክ እንደ አሰሪው ሁሉ ግዴታ አለተፈጸመልኝም ብሎ ጥያቄ ማቅረብ ይችላል፡፡ በመርህ ደረጃ አሰሪ ሆኖ የቀረበው የመንግስት መስሪያ ቤት ውል ባለመፈጸሙ ምክንያት ሥራ ተቋራጩ ውል አልተፈጸም በሚል መከራከሪያ ሊያቀርብ እንደማይችል ከፍትሐብሔር ሕጉ አንቀጽ 3177 ድንጋጌ እና ከተለመደው የላቲን አባባል፡- ‘Exceptio non adimpleti contractus’ (ግዴታ አለተፈጸመልኝምን እንደ መከራከሪያ አለማቅረብ) መረዳት ይቻላል፡፡