ባለንበት ዘመን ሕገ መንግሥት ወይም ስለመንግሥት አሠራርና አመራር የሚደነግግ ሕግ የሌሎው ሀገር ለማግኘት ያስቸግራል፡፡ ሳስበው ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓት መደንገግና በዛው ልክ መቆጣጠር ያስፈለገበት መሠረታዊ ምክንያት የሰው ልጅ ካለፈባቸው የችግርና የጦርነት ውጤት የቀሰመው አብይ መፍትሔ እንደሆነ ይሰማኛል፡፡ አብዛኞቹ ሀገራት በሕገ መንግሥታቸው ውስጥ ከሚያካትቱት መሠረታዊና ጥቅል ድንጋጌዎች መካከል የመንግሥት ሥልጣንና ተግባር፣ የዜጎች መሠረታዊ መብትና ግዴታ፣ የመንግሥት አስተዳደርና የሥልጣን ክፍፍል እንዲሁም የአሠራር ሁኔታ ይገኙበታል፡፡
በሕዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም የአስተዳደር ጥፋት የሚመለከት ምርመራ ለማካሔድ ስለአስተዳደር በደል በሚቀርብ አቤቱታ ሊጀመር ይችላል፡፡ ማለትም ተቋሙ በራሱ አነሳሽነት ከሚያደርገው ምርመራ በስተቀር ሁሉም በእንባ ጠባቂ በኩል የሚደረጉ ምርመራዎች ሥረ መሠረቱ ለተቋሙ የሚቀርብ አቤቱታ ነው፡፡
ስለአቤቱታ አቅራቢ
ለእንባ ጠባቂ ተቋም አቤቱታ የሚቀርበው መብቴ ተጥሶብኛል በሚል ሰው፣ ወይም በሚስት ወይም በባል ወይም በቤተዘመድ ወይም በወኪል ወይም በሦስተኛ ወገን ሊሆን ይችላል፡፡ በዚህ ዓረፍተ ነገር ከግል ተበዳይ ውጭ ያሉ አቤቱታ ለማቅረብ የሚችሉ ሰዎች ማንነት የሚሸፈነውና የሚወሰነው በሌሎች አግባብነት ባላቸው ሕጐች ነው፡፡ ባል፣ ሚስትና ቤተዘመድ ተብሎ የተጠቀሰው በቤተሰብ ሕግ በተመለከተው መሠረት የሚወሰን ሲሆን ወኪል በፍትሐብሔር ሕግና በፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ውክልና በሚመለከቱ ድንጋጌዎች የሚሸፈን ነው፡፡ በአዋጅ ቁጥር 211/1992 አንቀጽ 22 ሥር አቤቱታ ለማቅረብ ከሚችሉ ሰዎች መካከል የተዘረዘረው “ሦስተኛ ወገን” የሚለው ሀረግ ምን ያመለክታል? ይህ ሦስተኛ ወገን ለአቤቱታ መነሻ በሆነው ነገር ላይ ጥቅም ወይም መብት ያለው ሰው ነው? ወይስ ማንም የፈለገ ሰው ስለአንድ የአስተዳደር በደል ለእንባ ጠባቂ ተቋም አቤቱታ ማቅረብ ይችላል? የሕጉ መንፈስ ምንድ ነው? ለምሳሌ በስኮትላንድ የእንባ ጠባቂ ሕግ መሠረት የኅብረተሰቡ አካል በሆነው ሰው ላይ ደርሷል ስለተባለው የአስተዳደር በደል የኅብረተሰቡ አባል የሆነ ሌላ ሰው ስለበደሉ ለእንባ ጠባቂ ተቋም አቤቱታ ለማቅረብ ይችላል፡፡ ነገር ግን በአዋጁ “ሦስተኛ ወገን” ተብሎ የተመለከተው በአገሪቱ ውስጥ በአድቮኬሲ ሥራ ላይ የተሰማሩ መንግሥታዊ ያልሆኑ ምግባረ ሰናይ ድርጅቶችን ያጠቃልላል?