የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ያስፋፋው የማንነት ስርቆት (identity theft)

መቸም አሁን ለእናንተ ላወጋችሁ ያሰብኩትን ነገር በድሮ በዚያ በጥንት ጊዚያት ለነበሩ ሰዎች ብተርክላቸው ጉድ ሳይሰማ መስከረም አይጠባም ይሉኝ እንደነበረ አምናለሁ፡፡ ይህንን ጽሁፍ በተለያየ መልኩ አግኝታችሁ ወይም ያነበቡት አጋርተዋችሁ ስለዚህ ጉዳይ በደንብ የምታውቁ መኖራችሁ እንደተጠበቀ ሆኖ አንድ አንዶቻችሁ ግን ወቼ ጉድ! አሁን የሰዎችን ማንነት መሰረቅም ተጀምርዋል ነው የምትለን;! የምትሉ አትጠፉም ብየ እገምታለሁ፡፡ ለዚህም ምላሼ አዎ! የሰውን ማንነት መሰረቅ ተጀምርዋልና ማንነታችሁ እንዳይሰረቅ ጠንቀቅ በሉ ነው የምላችሁ፡፡ እንዴት ሆኖ ይሰረቃል በልስቲ አውጋን የሚል ከሆነ ቀጣዩ ጥያቄያችሁ በደስታ ይሄው እላለሁ፡፡


በቅድሚያ እንዴት ይሰረቃል ለምን አላማ ሲባል ይሰረቃል የሚለውን ከመመልከታችን በፊት ለመሆኑ ማንነት ስንል ምን ማለታችን ነው የሚለውን እንመልከት፡፡ አንድ ሰው ለመተዋወቅ ወይም ደግሞ ከእኛ የሚፈልገው አገልግሎት ኑሮት እኔ እገሌ እባላለሁ! በማለት ራሱን ሊያስተዋውቀን ይችል ይሆናል፡፡ እኛም እንደነገሩ አስፈላጊነትና ግዴታ የተባለው ሰው ስለመሆኑ በተለያየ መልኩ እንዲያስረዳን ልንጠይቀው እንችላለን፡፡ በሌላ አነጋገር እገሌ ስለመሆንህ ማስረጃ አቅርብልን ልንለው እንችላለን፡፡ ይሄው ብሎ ማንነቱን የሚገልጽ ወረቀት መታወቂያ ወይም ከዚህ ተመሳሳይነት ያለው ማስረጃ ሊያቀርብልን ይችላል፡፡ እኛም አሁንም እንደነገሩ አስፈላጊነት የተባለው ሰው ነው ወይስ አይደለም የሚለውን ለማረጋገጥ የተቀበልነውን ማስረጃ አገላብጠን ልንመለከተው እንችል ይሆናል፡፡ ታዲያ እርሱ ማን እንደሆነ ምን እንደሚሰራ የት እንደሚኖር ጾታውን እድሜውን የቤተሰቡን ሁኔታ ዜግነቱ እናም የመሳሰሉትን መረጃዎች ከተቀበልነው ሰነድ ልናይ እንችላለን፡፡ ከዚህ በህዋላ ግለሰቡ እርሱ ራሱን መሆን አለመሆኑን ካረጋገጥን በህዋላ ከእኛ የሚጠበቅ ነገር ሲኖር ተፈላጊውን አገልግሎት ወይም ትብብር ልናደርግለት እንችላለን፡፡ ስለዚህ ምን እያልን ነው ያለነው አንድን ሰው ማንነቱን እንድንለይ ሊያደርጉን የሚችሉ መስፈርቶች ከሀገር ሀገር የሚለያዩ ቢሆኑም በአብዛኛው የሚከተሉት መስፈርቶች የአንድ ግለሰብ ማንነቱ ሊያስረዱን የሚችሉ መታወቂያዎች ናቸው፡፡ ለምሳሌ የግለሰቡን ስም፣ የስራ ወይም የመኖሪያ አድራሻው፣ ዜግነቱ የመታወቂያ ወይም የፓስፖርት ቁጥሩ፣ የማህበራዊ ዋስትና ቁጥሩ፣ የባንክ አካውንት ቁጥሩ፣ የመንጃ ፈቃዱን የትምህርት ደረጃው፣ የተሰማራበትን የስራ መስክ፣ እድሜው፣ የትውልድ ቀንና ቦታውን ጥቂቶቹ ናቸው፡፡


ስለሆነም አንድ የማንነት ስርቆት ወንጀል ፈጻሚ እነዚህንና ሌሎች የራሱን ማንነት ደብቆ የሌላ ሰውን ማንነት ለመላበስ/ለመምሰል የሚያስፈልጉ ከላይ የተመለከትናቸውን የማንነት መገለጫዎችን ልቅም አድርጎ በመውሰድ/በመስረቅና ለዚህ አጋዥ የሚሆነውን ሀሰተኛ ሰነድ በማዘጋጀት ወይም እንዲዘጋጅለት በማድረግ ማንነቱን ሙሉ በሙሉ ወይም በከፊል በመቀየር በሰረቀው ሰው ስምና ማንነት ወንጀል መስራት ይጀምራል፡፡ ይህም ማለት የማንነት ስርቆት ማለት የአንድ ግለሰብ መለያ መስፈርቶች ሊሆኑ የሚችሉትን መስፈርቶችን በመጠቀም የወንጀሉ ሰለባውን ተመሳስሎ ህገወጥ ድርጊት የመፈጸም ወንጀል ነው፡፡ የዚህ አይነት የወንጀል ድርጊት ቀደም ብሎ የነበረና የቆየ ወንጀል ድርጊት ቢሆንም የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ መስፋፋትንና ስራዎች በአብዛኛው በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ መከናወናቸውን ተከትሎ በከፍተኛ ደረጃ የወንጀል ድርጊቱ ሊስፋፋ ችልዋል፡፡


በማንነት ስርቆት የተሰማሩ ሰዎች የሚከተሉት ዘዴዎችን በመጠቀም የግለሰቦችን ይሁን የተቅዋማት መረጃዎችን ይወስዳሉ/ይሰርቃሉ፡፡ የመጀመሪያው ማህበራዊ ምህንድስና (social engineering) የሚባለው ዘዴ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ውጤት የሆኑ እንደ ቫይረስና አሳሳች ሶፍትዌሮችን በመጠቀም መረጃዎችን የመሰብሰብ ተግባራት ያከናውናሉ፡፡ ማህበራዊ ምህንድስና (social engineering) የሚባለው በአካል ከግለሰቡ ከራሱ ወይም እርሱን ከሚያውቁ ሌሎች ግለሰቦች ጋር በመተዋወቅ ስለ ግለሰቡ ማንነት አስፈላጊ መረጃዎችን የመሰብሰብ ሂደት ነው፡፡ በዚህም ግለሰቡ ማን እንደሆነ ምን እንደሚሰራ የት እንደሚኖር እና ለወንጀል ድርጊታቸው ያስፈልጉናል የሚልዋቸውን ሌሎች መረጃዎችና ማስረጃዎችን በማሰባሰብ ወደ ወንጀል ድርጊታቸው ይገባሉ፡፡


ቫይረስንና አሳሳች ሶፍትዌሮችን በተመለከተ በዚህ የወንጀል ድርጊት የተሰማሩ ሰዎች ለወንጀል ድርጊታቸው የሚያግዝዋቸውን ልዩ ልዩ የኮምፒውተር ቫይረስ አይነቶችን ሊጠቀሙ ይችላሉ፡፡ እነዚህ የኮምፒውተር ቫይረሶች በተለያዩ መንገዶች እንዲሰራጩ ተደርገው የግለሰቦችንና ተቅዋማትን መረጃ ለእነዚህ ህገ ወጥ ግለሰቦች እንዲደርሳቸው ያደርጋሉ፡፡ ከዚህ ጋር የሚቀራረብም ሌላ ዘዴም አለ፤ ይሄውም፣ በኢሌትሮንክስ መልእክት አመካኝነት ይሁን ወይም ደግሞ ግለሰቡ የሚጠቀምባቸውን ድህረ-ገጾችን በማስመሰል፡፡ አዳዲስ ድህረገጾችን በትግበራ ላይ እንዲውሉ በማድረግ አሳስቶ እንዲጠቀም ማድረግ ነው ይህም በእንግሊዘኛው አጠራር “fishing” የሚባለው ዘዴ ነው፡፡ በዚህም የወንጀል ሰለባው ስለራሱ ማንነት የሚመለከቱ መረጃዎችን በተዘጋጀለት የሀሰት ቅጽ ላይ እንዲሞላ በማድረግ በተለይም ደግሞ የመጠቀሚያ ስሙንና የይለፍ ቃሉን በቀላሉ ለመሰብሰብ ያስችላችዋል፡፡ ወይም ደግሞ ከግለሰቡ ይሁን ተቅዋሙ ጋር ግንኙነት ካለው የኢለትሮንክስ መልእክት የተላለፈ በማስመሰል፡፡ እርሱ ብቻ የሚያውቃቸውን እንደ የይለፍ ቃልና የመጠቀሚያ ስሙን እንዲሞላ ቅጽ በመላክና እንዲሞላ በማድረግ አስፈላጊ የሆኑትን መረጃዎችን ይወስዳሉ፡፡ አላማው የግለሰቡን የይለፍ ቃልና ሌሎች መረጃዎችን ለመውሰድ ነው፡፡ 

Continue reading
  9794 Hits

የሳይበር ክልልና ሀገሮች ለአላዊነታቸውን ለማስከበር የሚከተልዋቸው መርህዎች

ሰላም እንዴት ናችሁ፡፡ በባለፈው ጽሁፌ የሳይበር ክልልና የሀገሮች የለአላዊነት ስልጣን እስከ ምን ድረስ? በሚል ርእስ አንድ ጽሁፍ አስፍሬ እንደነበር ይታወሳል፡፡ ለዛሬ ደግሞ የሳይበር ክልል ለመቆጣጠር ሀገሮች በመከተል ላይ ያሉት መርህዎች ምን ይመስላል? የሚለውን ለማየት እሞክራለሁ፡፡ በዚህ አጋጣሚ ሀለፎም ሃይሉ ለሰጡኝ ምላሽ አመሰግናለሁ፡፡


የአንድ ሀገር የለአላዊነት ስልጣን መገለጫ ከሆኑት ውስጥ አንዱ ስልጣን ባለው ሀገር የተሰጠውን ውሳኔ በሌላ አካል (ሀገር/ድርጅት) ሊከለስ ወይም ደግሞ ሊቀለበስ የማይችል ሲሆን ነው ከዚህ አንጻር ሀገሮች አንድን ጉዳይ የለአላዊነት ስልጣን አለን ወይም የለንም ብለው ለመወሰን የሚያስችልዋቸው ልዩ ልዩ መርህዎች አሉ፡፡ ለምሳሌ እንደ ግዛትን፣ ዜግነትን፣ ብሄራዊ ጥቅምን የአለም አቀፍ ስልጣንና የመሳሰሉትን መርሆዎችን በተናጠል ወይም አጣምረው በተግባር ላይ በማዋል የሀገሮቻቸውን ለአላዊነት ተጠብቆ እንዲኖር ያደርጋሉ፡፡ እነዚህን መርህዎች በሳይበር ክልል እንዴት ይተገበራሉ የሚለውን እንደሚከተለው ለመመልከት እንሞክራለን፡፡


ግዛትን መሰረት ያደረገ መርህ


አንድ አንድ ሀገሮች በሳይበር ክልል ውስጥ ለሚነሱ ግጭቶች ይሁን አለመግባባት ግዛትን መሰረት በማድረግ ለጉዳዩ መፍትሄ ማግኘት አለበት ብለው ያምናሉ፡፡ ይህም የሚሆነው ለጉዳዩ መነሻ የሆነው ጉዳይ የተፈጠረው በአንድ ሀገር ግዛት እስከሆነ ድረስ ምንም እንኳን ሌሎች ሀገሮች በድርጊቱ ጉዳት ደርሶባቸው ሊሆን ቢችልም ነገር ግን ግዛትዋ ላይ በመሆን የተፈጸመ እንደመሆኑ መጠን ለጉዳዩ መነሻ የሆነው ሀገር ህግንና ደንብ ተፈጻሚ መሆን አለበት፡፡ የሚል አስተሳሰብ አላቸው፤

ሆኖም፣ ይህ መርህ ለሳይበር ወንጀል ብቻ ሳይሆን በማንኛውም የወንጀል ድርጊት ተፈጻሚ መሆን ያለበት የህግ መርህ ቢሆንም ነገር ግን ከሳይበር ወንጀል ባህሪ አንጻር ሲታይ አንድ ወንጀል ሲፈጸም የበርካታ ሀገሮችን ቴክኖሎጂን በመጠቀም የወንጀል ድርጊቱ የሚፈጸምበት አጋጣሚ ያለ በመሆኑ ለወንጀሉ መፈጸም ግዛታቸውን ከተጠቀመባቸው ሀገሮች ውስጥ የየትኛው ሀገር ህግና ደንብ ተፈጻሚ ይሁን የሚለውን ጥያቄ በአግባቡ የሚመልስ አይደለም፡፡ ስለሆነም መርሁ ከሳይበር ጋር ተያይዞ ለሚነሱ ጥያቄዎች የግዛት መርህ አግባብነት የለውም ብለው የሚተቹት ቢኖሩም ነገር ግን የግዛት ህግ መፈጸም አለበት ብለው የሚከራከሩ መርሁን ተፈጻሚ እንዲሆን የሚያግዙ ሁለት ንድፈ-ሀሳቦችን ያስቀምጣሉ፡፡ እነዚህም ንድፈ-ሀሳቦች የአውራጅና ጫኝ ንድፈ-ሀሳብና የሰርቨር ህግ ንድፈ-ሀሳብ ናቸው፡፡

Continue reading
  8680 Hits
Tags:

የሳይበር ክልልና የሀገሮች የለአላዊነት ስልጣን እስከ ምን ድረስ

የሳይበር ክልል ሲባል የኮምፒውተር ፕሮግራሞች፣ ዳታዎች፣ የኮምፒውተርና የቴሌኮምንኬሽን ግንኙነት፣ የኮምፒውተር ስርአትና በአጠቃላይ እነዚህ መሰረተ ልማት ዝርጋታ፣ እንዲሁም ተጠቃሚዎችን የሚያካትት ክልል ነው በማለት በአጭሩ መግለጽ ይቻላል፡፡ ታዲያ ይህ ክልል የሀገሮች የፖለቲካ ይሁን የመልክአ-ምድር አቀማመጥ የማይገድበው እንዲሁም በሀገሮችና በህዝቦች መካከል ያለው የባህል፣ የቋንቋና የአኗኗር ዘዴ ጫና የማያሳድርበት ከመሆኑ አንጻር ክልሉን የሚመለከቱ ገና ምላሽ ያላገኙ በሀገሮች መካከል ለውዝግብና ያለመግባባት መንስኤ ሊሆኑ የሚችሉ በርካታ ነጥቦች መከሰታቸው አልቀረም፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ይህን ዘርፍ እንዴትና በማን ይተዳደር፣ ዘርፉንስ ከህገወጦች እንዴት እንከላከል እንዲሁም በሀገሮችና ዜጎቻቸው ላይ ደህንነትና ጥቅሞች በህገ ወጦች ይሁን በአንድ አንድ የሀገር መንግስታት አመካኝነት አደጋ ሲቃጣ የሀገሮች ምላሽ ምን ሊሆን ይገባል ህገወጦችንስ ለፍርድ የማቅረብ ስልጣን የማን ሊሆን ይገባል በአጠቃላይ የሀገሮች ሉአላዊነት እንዴት ማስከበር ይቻላል እና የመሳሰሉትን ጉዳዮች ላይ ገና ምላሽ ያላገኙ ጥያቄዎች ይነሳሉ፡፡


ከዚህም ብዙም ሳንርቅ ለሳይበር ክልል መፈጠርና ማደግ በዋናነት ቁልፍ ሚና በመጫወት ላይ ካሉት የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ መሳሪያዎች ውስጥ የኮምፒውተሮች ግንኙነት ወይም ደግሞ በይነ-መረብ በዋናነት ከሚጠቀሱ የቴክኖሎጂ ውጤቶች አንደኛው ነው፡ ይህ ዘርፍ ከሚሰጣቸው በርካታ አገልግሎቶችና ከተጠቃሚዎች ብዛት አንጻር በተጠቃሚዎች መካከል ልዩ ልዩ አለመግባባቶች ማጋጠማቸው አይቀርም፡፡ ለምሳሌ ከውል አፈጻጸም፣ የካሳ ጥያቄና አከፋፈል የዳኝነት ስልጣንና የመሳሰሉት አለመግባባትና ግጭቶች ያጋጥማሉ፡፡ ታዲያ እንደእነዚህ አይነት ግጭቶችና ያለመግባባት እንዴት ይፈቱ፡ በተለይም ደግሞ ሀገሮች ዘርፉን በመቆጣጠርና ማስተዳደር እንዲሁም የራሳቸውን ሉአላዊነት ከማስከበር ጋር ተያይዞ ያለባቸውን ክፍተት በመሙላት ረገድ ገና ምላሽ የሚያስፈልጋቸው ልዩ ልዩ ጥያቄዎች ይነሳሉ፡፡


እንደሚታወቀው ማንኛውም ለአላዊ መንግስት በአለም አቀፍ ደረጃ እውቅና የሚሰጣቸው የሉአላዊነቱ መገለጫ የሆኑ ስልጣኖች አሉት፡፡ ይሄውም፣ አንድ ነጻ የሆነ የሀገር መንግስት እነዚህን የሉአላዊነቱን መገለጫ የሆኑትን ተግባራት በግዛቱ ውስጥ በሚገኙ ሰዎች፣ የሚንቀሳቀሱ ይሁን የማይንቀሳቀሱ ነገሮች እንዲሁም ክንውኖች ላይ ህግ የማውጣት፣ የወጣውን ህግ ተግባር ላይ እንዲውል የማድረግና ያወጣቸውን ህጎች ተጥሰው ሲገኙ ያለማንም ጣልቃ ገብነት ህግን የማስከበርና እንደነገሩ ሁኔታ አጥፊዎችንም ለፍርድ በማቅረብ የማስቀጣት ሙሉ የለአላዊነት ስልጣን አለው፡፡ በመሆኑም ሀገሮች አለም አቀፍ የሳይበር ክልል መፈጠርን ተከትሎ ይህንን የለአላዊነታቸው መገለጫቸው የሆኑትን ስልጣኖች በዚሁ ክልል ላይም ለመተግበር እንዲችሉ ልዩ ልዩ ጥረቶችን በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡


ይሁን እንጂ የአንድ ሀገር ለአላዊነት ስልጣን እስከምን ድረስ ሊሆን ይገባል በሚለው ላይ አንድ መደምደሚያ ላይ ለመድረስ አልተቻለም፡፡ ስለሆነም፣ በዚህ ጉዳይ ላይ የተለያዩ ሙህራን የተለያዩ አስተያየቶች ይሰጣሉ፡ ለምሳሌ ይህ ዘርፍ በየትኛው ህግ ሊመራ ይገባል በሚለው ጉዳይ ላይ አንድ አንዶች እንተርኔት ሳይበር ክልል በለአላዊ ግዛቶች መካከል የቴክኖሎጂ፣ የህግና ስርአት ትስስር እንዲፈጠር የሚያደርግ ዘርፍ እንደመሆኑ መጠን ዘርፉ በየትኛው ህግ ሊተዳደር ይገበዋል ያልን እንደሆነ በነጻ ለኣላዊ ሀገሮች መካከል ያለውን ግንኙነት የሚመለከተው የህግ ክፍል አለም አቀፍ ህግ ነው፡፡ ስለሆነም፣ እንተርኔትም በዚሁ የህግ ማእቀፍ ሊተዳደር ይገባል የሚሉ ሙሁራን የመኖራቸው ያክል ሌሎች ደግሞ ልክ ነው በሀገሮች መካከል ላለው ግንኙነት በተመለከተ ግንኙነታቸው የሚመራው በአለም አቀፍ ህግና ስምምነቶች ነው ነገር ግን እንተርኔት የሀገሮች ግንኙነት ጉዳይ ብቻ አይደለም ዘርፉ ከሀገሮች ጋር ያለውን ግንኙነት ቁርኝት እንዲፈጠር በማድረግ አለም አቀፋዊነቱ እንደተጠበቀ ሆኖ ይህ ጉዳይ የሀገር ውስጥ ጉዳይም ጭምር ነው በቀጥታ በሀገር ደህንነት፣ ሰላም፣ ልማት፣ ዲሞክራሲ እድገትና ውድቀት ላይ ትልቅ ሚና ያለው ዘርፍ ነው፡፡


ስለሆነም ይህ ለአለም አቀፍ ግንኙነት ብቻ የሚተው ጉዳይ አይገባም፡፡ በሌላ በኩል ይህ ጉዳይ የሀገር ውስጥ ጉዳይ ነው ስለሆነም የሀገሪቱ ህግ ሙሉ በሙሉ ተፈጻሚ ይሁን ሊባልም የሚችል ጉዳይ አይደለም ምክኒያቱም የሳይበር ክልል በአንድ ሀገር ድንበር የታጠረ አይደለምና ነው፡፡ ለምሳሌ ከተጠቃሚዎች አንጻር ብንመለከተው የየትኛው ሀገር ተጠቃሚ የትኛውም ሀገር ካለው ተጠቃሚ ጋር ግንኙነት በመፍጠር መረጃ ይለዋወጣሉ ሀሳባቸውን ይገልጻሉ የንግድ እንቅስቃሴ ያካሂዳሉ ሌላው ቀርቶ ግንኙነታቸውን በማጠናከር ማህበራዊና ቤተሰባዊ ትስስር እስከመፍጠር ይደርሳሉ፡፡ ስለዚህም በአንድ ሀገር ህግና ደንብ መመራት አለበት የሚለውም በተወሰነ ደረጃ ልክ ሊሆን ቢችልም፣ ነገር ግን ዘርፉ የሀገር ውስጥና አለም አቀፍ ጉዳዮችን አጣምሮ የሚይዝ እንደመሆኑ መጠን፣ በሀገር ውስት ህግ ብቻ መተዳደር ይኖርበታል የሚለውም አግባብነቱ አጠያያቂ እንዲሆን ያደርገዋል፡፡ 

Continue reading
  8302 Hits
Tags: