መግቢያ
የፍትሐ ብሔር ሕግ ቁጥር 1724 እንዲህ ይነበባል፤ መንግስት ወይም ለሕዝብ አገልግሎት የቆሙ መስሪያ ቤቶች ግዴታ የሚዋዋሉባቸዉ ዉሎች ሁሉ በጽሁፍና በሚገባ አኳኋን በፍርድ ቤት መዝገብ ወይም ባንድ ባስተዳደር ክፍል መስሪያ ቤት መዝገብ ወይም ዉል ለማዋዋል ስልጣን በተሰጠዉ ሰዉ ፊት መሰራት አለባቸዉ፡፡ እንግሊዘኛዉ ደግሞ እንዲህ ይነበባል፤ Any contract binding the Government or a public administration shall be in writing and registered with a court, public administration or notary. የኪራይ ቤቶች አስተዳደር ድርጅት የሚዋዋላቸዉ ዉሎች በዚህ የፍ/ብ/ሕ/ቁ.1724 የሚወድቁ ናቸዉ ወይ የሚለዉን ጥያቄ ለመመለስ እሞክራለሁ፡፡ ለዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆነዉ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ችሎት በሰ/መ/ቁ.14285 በመጋቢት 15 1997 የሰጠዉ ዉሳኔ ነዉ፡፡
ጉዳዩ የተጀመረዉ የኪራይ ቤቶች አስተዳደር ድርጅት በፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በአንድ ግለሰብ ላይ በመሰረተዉ ክስ ዉዝፍ የቤት ኪራይ ባለመክፈላቸዉ እንዲከፍሉ ይወሰንልኝ በማለት ነዉ፡፡ ግለሰቡም ዉሉ ላይ የኪራይ ቤቶች አስተዳደር ድርጅት ሃላፊ ሆነ እራሱ አልፈረሙበትም፤፤ ኪራይ ክፈልበት በተባልኩበት ቤት ዉስጥም አልኖርኩም፤ የተከራየዉ ሌላ ቤት ሲሆን በዚያም የሚጠበቅበትን ክፍያ እንደፈጸመ በመግለጽ ተከራክሯል፡፡
የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት
የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በዉሳኔዉ ኪቤአድ የመንግስት መስሪያ ቤት ነዉ፡፡ በፍ/ብ/ሕ/ቁ. 1724 መሰረት ደግሞ የመንግስት መስሪያ ቤቶች ዉል በጽሁፍ መሆን አለበት፡፡ በፍ/ብ/ሕ/ቁ. 1727(1) እና (2) መሰረት ደግሞ በጽሁፍ የሚደረገዉ ዉል በሁለት ምስክሮች መረጋገጥ አለበት፤ ይህ ካልሆነ ዉሉ አይጸናም፡፡ ለጉዳዩ መነሻ የሆነዉ ዉል በሁለት ምስክሮች ያልተረጋገጠ በመሆኑ አይጸናም በሚል ወስኗል፡፡ ይህም ዉሳኔ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመጽናቱ የሰበር አቤቱታ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ቀርቧል፡፡