በወንጀል ጉዳይ የመጨረሻ ውሳኔን እንደገና ስለማየትና በኢትዮጵያ ያለው ሁኔታ

በወንጀል ጉዳይ  የፍርድ ውሳኔ የሰጠው ፍርድ ቤት በድጋሜ ጉዳዩን ማየት ማለት ፍርድ ቤቱ የመጨረሻ የፍርድ ውሳኔ ከሰጠ በኋላ የግዜ ገደብ ሳይኖረው ጉዳዩን በድጋሜ በተለያዩ ምክንያቶች ማየትና በድጋሜ ውሳኔ መስጠት ማለት ነው፡፡ በተለይም በዚህ ዘመን የሐሰት ሰነዶች የመቅረባቸው ጉዳይ እራስ ምታት በሆነበት፣ ሐሰተኛ ምስክርነትን መሠረት በማድረግ በተቃራኒ ተከራካሪ ወገንም ሆነ በፍርድ ቤቱ ሊደረስበት ባለመቻሉ የተሳሳተና የተዛባ የፍርድ ውሳኔ በሚሰጥበት ዘመን የእነዚህን ሐሰተኛ ማስረጃዎች ግዜ ሳይገድበው የሚያገኝ የወንጀል ጉዳይ ተከራካሪ ወደዛው ፍርድ ቤት በመሄድ የተገኘውን አዲስ ማስረጃ መሠረት በማድረግ ክርክር በድጋሜ አድርጎ ውሳኔው እንዲሰተካከል ለማድረግ የሚያስችል የሕግ አካሔድ መኖሩን አስፈላጊነት ሁሉም የሚስማማበት ነው፡፡ አንዳዴም እንደሚሰማው በህይወት ያለን ግለሰብ ገድለኃል ተብሎ ጥፋተኛ የተባለን ግለሰብ ሞተ የተባለው ግለሰብ በህይወት መኖሩ ቢታወቅ እንኳን ጥፋተኛ የተባለውን ግለሰብ ነፃ የሚያወጣ የሕግ አካሔድ ሊኖር የሚገባ ስለመሆኑም የሚያስማማ ነው፡፡ በቅርብ ግዜ በተላለፈ የቴሌቭዥን ፕሮግራም ላይ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞች ከሚያጋጥማቸው ጉዳዮች በመነሳት የሐሰት ሰነዶች እና የሐሰት ምስክርነት ጉዳይ ከግዜ ወደ ግዜ እየተበራከተ መምጣቱን ሲናገሩ መስማቴ ትዝ ይለኛል፡፡ ይህን መሰል የፍትሕ ጠር የሆነ ተግባር ሙሉ ለሙሉ ማጥፋት ባይቻል እንኳን ይህ ሁኔታ በታወቀ ግዜ ግን ጉዳዩን ውሳኔውን የሰጠው ፍርድ ቤት በድጋሜ እንዲያይ የሚያስችልና ሐሰተኛውን ማስረጃ እና የተሳሳተውን ውሳኔ ለማስተካከል የሕግ መሠረት ሊኖረን ይገባል፡፡

  13726 Hits