መግቢያ
የፌደራል ፍርድ ቤቶች አዋጅ 1234/2013 በፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ስር የተቋቋመ 15 ከፍተኛ የሕግ ባለሙያዎችን በአባልነት ያካተተ የዳኝነት ሥርዓት አማካሪ ጉባኤ ረቂቁ ተዘጋጅቶ በፌደራል ፍርድ ቤቶች አመራሮች፣ በሕግ ባለሙያዎች እና በሕዝብ ተሳትፎ ዳብሮ ከሁለት አመታት ቆይታ በኋላ ጥር 13 ቀን/ 2013 ዓ.ም በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጸድቋል።
ይህ አዲሱ የፌደራል ፍርድ ቤቶች አዋጅ 1234/2013 ከነባሩ የፌደራል ፍርድ ቤቶች አዋጅ ቁጥር 25/88 እና ይህን አዋጅ ካሻሻሉት ሌሎች አዋጆች ቁጥራቸው 138/1991፣ 254/1993፣ 321/1995 እና 454/1997 ከሆኑት አዋጆች ምን የተለየ አዲስ ነገር ይዞ መጥቷል? እንዲሁም ለአዳዲሶቹ ሕጎች መነሻ ዋና ዋና ምክንያቶቹስ ምን ምን ናቸዉ የሚለዉን በወፍ በረር እንመልከት።