Abyssinia Law Abyssinia Law
  • Home
  • Laws
    • Search Federal Laws
    • Regional Laws
    • Constitutions
    • Audio Legal Resources
  • Decisions
    • Cassation Decisions by Volume
    • Cassation Decisions Database
    • FFI Court Commercial Bench Decisions
  • Blog
  • Resources
    • Researches Papers
    • Policies and Strategies
    • Codes, Commentaries and Explanatory notes
    • Legal Forms
    • Bench Books
    • Human Right Documents
    • Modules and Materials
    • About Our Laws
    • Quick links
  • Study On-line
  • know your rights
  • Lawyers
  • About Us
    • Who Are We
    • Our Partners
    • Advertise with Us
    • Privacy Policy
    • Contact us
    • Professional Advice?
    • How to submit a blog post
  • login
Abyssinia Law Abyssinia Law
  • Home
  • Laws
    • Search Federal Laws
    • Regional Laws
    • Constitutions
    • Audio Legal Resources
  • Decisions
    • Cassation Decisions by Volume
    • Cassation Decisions Database
    • FFI Court Commercial Bench Decisions
  • Blog
  • Resources
    • Researches Papers
    • Policies and Strategies
    • Codes, Commentaries and Explanatory notes
    • Legal Forms
    • Bench Books
    • Human Right Documents
    • Modules and Materials
    • About Our Laws
    • Quick links
  • Study On-line
  • know your rights
  • Lawyers
  • About Us
    • Who Are We
    • Our Partners
    • Advertise with Us
    • Privacy Policy
    • Contact us
    • Professional Advice?
    • How to submit a blog post
  • login

ከስም እና ከክብር ጋር በተያያዙ መብቶች ላይ የሚፈፀም ጥፋት ቁጥር /2044/

Details
Category: Non-Contractual Liability (Tort Law)
18.Feb
Hits: 11058

ይህ  ድርጊት በፍትሐብሔርም በወንጀል ሕግም ጥፋት ነው የወንጀል ሕግ ቁጥር 613ን  ተመልከቱ እነዚህ ቁጥሮች  በኘሬስና  ሀሳብን  በነፃ  የመግለፅ  ሕገ  መንግስታዊ መብት ላይ  የተደረጉ  ገደቦች ናቸው፡፡  በተመሳሳይ  ሁኔታ የኢፊዲሪ  ሕገ  መንግስት  አንቀፅ  39 /3/ ስር  የኘሬስና የሌሎች  መገናኛ  ብዙሃን  እንዲሁም የሥነ ጥበብ ፈጠራ ነፃነት መረጋገጡን  ደንግጉ  አንቀፅ  29/6/ ስር  የሰውን ክብርና  መለካም  ስም  ለመጠበቅ  ሲባል  ሕጋዊ ገደቦች  በእነዚህ  መብቶች  ላይ ሊደነገጉ ይችላሉ ይላል፡፡ ስለሆነም በዚህ ገደብ  አማካኝነት  ጥበቃ  የተደረገላቸው  መልካም ስምና ክብር ናቸው፡፡

 

ይህን  ያህል ለመግቢያ ካልን  አንዳንድ ነጥቦችን  አንስተን  እንወያይ  የስም  ማጥፋት  ድርጊት የሚፈፀምበት ሰው በሕይወት ያለ መሆን አለበት ይህም የሰም ማጥፋት  የሚደረገው  ስሙ የጠፋው ሰው  እንዲጠላ ወይም   እንዲዋረድ  ወይም  እንዲሳቅበትና  ብሎም  ስሙ  በጠፋው  ሰው ላይ  ሌላው እምነት  እንዳይኖረው  ለማድረግ  ወይም  መልካም  ዝናው  ወይም  የወደፊት  ዕድሉ እንዲበላሽ  ለማድረግ ነው፡፡ ይህን  ያደረገ  ጥፋተኛ  ነው፡፡

 

አንዳንድ  ምሳሌዎችን  እንውሰድ፡፡  አንድ ሰው በወንጀል  ሕግ  የሚያስቀጣ  ወንጀል ሳይፈፀም  ሰርቷል  ወይም  አንድን  የሕክምና ዶክተር  ችሎታ  እያለው  ችሎታ  የለውም  ማለት አንድን ነጋዴ  ሳይከስር   ዕዳውን  ለመክፈል  አይችልም  ማለት ተላላፊ በሽታ  ሳይኖርበት  እንዳለበት አድርጐ   ማውራት   ለስም  ማጥፋት እንደምሳሌ ልንወስዳቸው  እንችላለን፡፡ እንዲሁም ነገሩ  እውነት ሆኖም ሰውዬውን ለመጉዳት  ብለን ካደረግነው  ድርጊታችን  ጥፋት ይሆናል፡፡ /የወ.ሕግ  613/

 

አንድ  ቃል ወይም  አረፍተ ነገር  ስም ማጥፋት  ነው እንዲባል ቃሉ  ወይም  ዐረፍተ  ነገሩ  ለሶስተኛ  ሰው  ሊነገር  ይገባል፡፡  ለሶስተኛ  ሰው  ሳይሆን  ለራሱ  ለተበዳዩ ቀጥታ የተነገረ  እንደሆነ  ስም  ማጥፋት  ሳይሆን  ስድብ /insult/ ነው የሚሆነው፡፡

 

ስም የማጥፋት ድርጊት በቃል ሊሆን ይችላል፡፡ በፅሁፍና እንዲሁም በሌላ ዘዴ /ለምሳሌ ሌላ የኪነ ጥበብ ውጤት / ሊሆን ይችላል፡፡  ስም  ማጥፋት  አለ ለማለት  የግድ  የመጉዳት ሃሳብ   መኖር የለበትም፡፡ 2045 /1/ እንዲሁም  ቁጥር  2ዐ45/2/ ስር  እንደተደነገገው  በብድን  ስም  /group defamation/ የለም፡፡ ስለሆነም አንድ ሰው  ስም አጠፋ   ለማለት  በንግግሩ  ወይም  በፅሁፍ  የማንንም ሰው በተለይ ካልገለፀ በቀር ስም እንዳጠፋ አይቆጠርም፡፡  ሆኖም  ግን  ይህ አድራጉቱ ሌላ  ሰው እንዲጉዳ አስቀድሞ  ለመረዳት መቻሎ  ከተረጋገጠ  አላፊ  ሊሆን እንደሚችል  ቁጥር  2ዐ41/3/  ይደነግጋል፡፡

 

ቀጥለን  መከላከያዎችን  እንመለከታለን፡፡  የመጀመሪያው  መከላከያ  ቁጥር  2ዐ46 ስር የተደነገገው  የሕዝብን  ጥቅም  በሚነኩ ጉዳዩች  ላይ  አሳብን መግለፅ  ነው፡፡ ይህ  የተገለፀው  ሃሳብ  ሌላውን ሰው  በሕዝብ  ዘንድ  የሚያስወቅስ  እንኳን  ቢሆን  እንደስም  ማጥፋት  አይቆጠርም ሆኖም  ስም አጠፋ የተባለው ሰው ጠፋ   የተባለው  ሰው  ላይ  የሰጠው  አስተያየት  ሃሰት  መሆኑን በእርግጠኝነት  ካወቀ  ጥፋተኛ  ይሆናል፡፡

 

ሁለተኛው  መከላከያ  ደግሞ  የተነገረው  ነገር  እውነት መሆኑ ነው፡፡ ይህንንም በማስረጃ ማረጋገጥ አለበት  ሆኖም  ግን  የተባለው ነገር እውነት ቢሆንም  ስሙ  ጠፋ  የተባለውን ሰው  ሆን ብሎ  ለመጉዳት ቃሉን ወይም  ዓረፍተ  ነገሩን   የተናገረው  ተከሣሽ  ጥፋተኛ  ይሆናል፡፡ /በቁጥር 2ዐ47/

 

ሶስተኛ  መከላከያ  ደግሞ   የማይደፈር  መብት  በእንግሊዝኛው /immunity/ የሚባለው  ነው፡፡  ይህ መብት ለተወሰኑ  ሰዎች  የተሰጠ ነው  ለፖርላማ  አባላትና በፍርድ ቤት ፊት  ለሚከራከሩ ወገኖች፡፡  አንድ የፖርላማ አባል  በፖርላማ ውስጥ  በሚደረግ  ውይይት  ሀሳቡን  ሲገልፅ  ግለሰብን  አንስቶ ሊናገር  ይችላል፡፡  ይህ ግን  የፖርላማ አባሉን  በስም  ማጥፋት  ተጠያቂ ሊያደርግው አይችልም፡፡

 

በፍርድ  ሂደት ክርክርም  የሰዎች  ስም  ሊነሳ ይችላል ለፍትህ አሰጣጥ የግድ  ከሆነ ግለሰብ  ሊነሳ ይችላል፡፡  ይህን ያነሳ ተከራካሪ  በስም  ማጥፋት  ጥፋተኛ አይባልም፡፡

 

በተጨማሪም ቁጥር  2ዐ45/2/ ስር  እንደተደነገገው  በምክር ቤት ወይም በፍርድ  ቤት  የተደረገን ንግግርና ክርክር  እንዳለ /እንደወረደ እንደሚባለው/ የገለጠ  ሰውም በአላፊነት  ሊጠየቅ የሚችለው  ስሙ  በውይይቱ  ወይም በክርክሩ      የተነሳውን ሰውዬ  ለመጐዳት ብቻ አስቦ ከሆነ ብቻ ይሆናል፡፡

 

በመጨረሻም  የስም  ማጥፋት  ተግባር  በጋዜጣ  ላይ  ሊደረግ  ይችላል፡፡ ይህ  በሚሆንበት ጊዜ  ስም አጠፋ የተባለው ሰው  ፋጥተኛ  የሚሆነው፣

  • አንድን  ሰው  ለመጉዳት ብሎ  አስቦ ከሆነ
  • ይህንንም  የፈፀመው በከፍተኛ ቸልተኝነት ከሆነ
  • ወዲያውኑ መልሶ  ይቅርታ ካልጠየቀ ነው፡፡

 

በሌላ  አባባል  ስም  ማጥፋቱን  የፈፀመ አንድን  ሰው ለመጉዳት ሆን ብሎ  አስቦ  ሳይሆንና  በቸልተኝነት  ካልሆነ ይህንንም  ካደረገ  በኃላ  ወዲያውኑ  መልሶ  ይቅርታ  ከጠየቀ ጥፋተኛ  አይሆንም፡፡  2ዐ49/1/

ቁጥር 2ዐ49 /2/ እና /3/ የይቅርታው  አጠያየቅ  ጊዜ  እና በምን  ላይ መሆን  አለበት  የሚለውን  ይመልሳሉ፡፡  በንዑስ  ቁጥር  ሁለት  መሠረት ስም ማጥፋት  ድርጊቱ  የተደረገው  ከአንድ  ሳምንት  በበለጠ ጊዜ  በሚወጣ  ጋዜጣ  ላይ  ከሆነ  ይቅርታው  የግድ  የሚቀጥለው  ጋዜጣ  እስኪወጣ  መጠበቅ  የለበትም ይህ ከሆነ  ተበዳዩ  ይጉዳል፡፡  የጠፋውንም  ስምና ጉዳቱንም  ማስተካከል  የማይቻልበት  ደረጃ  ላይ  ሊደረስ  ይችላል፡፡ ስለዚህ  ይቅርታው  ተበዳዩ  በሚመርጠው  ጋዜጣ  ላይ  መውጣት  አለበት፡፡ ይህ ጋዜጣ  የበዳዩም  ሊሆን  ይችላል፡፡ የሌላ ሰወ  ጋዜጣም  ሊሆን ይችላል፡፡ ተበዳዩ  ጋዜጣ  ካልመረጠ በንዑስ  ቁጥር ሶስት  መሠረት  የስም  ማጥፋቱ ነገርና  የይቅርታው  መጠየቁ   የሚታተመው  ስምን ማጥፋቱ  በወጣበት ተከታይ ዕትም ላይ  ይሆናል፡፡

የሌላን ሰው ነፃነት ስለመንካት ቁጥር 2040

Details
Category: Non-Contractual Liability (Tort Law)
18.Feb
Hits: 7741

የኢፌዲሪ  ሕገ መንግስት  አንቀፅ 17 ስር  በሕገ ከተደነገገው ሥርዓት ውጭ ማንኛውም ሰው ወንድም ሆነ ሴት ነፃነቱን/ቷን አያጣም /አታጣም ተብሎ ተደንግጓል፡፡ በተጨማሪም ንዑስ አንቀፅ ሁለት ስር ማንኛውም  ሰው  በሕግ ከተደነገገው ሥርዓት ውጭ ሊያዝ እንደማይችል ተደንግጓል፡፡ ስለሆነም ይህ የነፃነት መብት  ሕገ መንግስታዊ መብት ነው፡፡

 

ይህም በመሆኑ  ነው  የፍትሐብሔር  ቁጥር 2ዐ4ዐ/1/ አንድ ሰው ሕግ ሳይፈቀድለት ለተወሰነ ጊዜም ቢሆን የሌላውን ሰው ነፃነት /ሕገ መንግስታዊ ነፃነት/የነካና አንደተፈቀደለት መጠን ካንዱ ቦታ ወደ ሌላው  እንዳይዘዋወር /የኢፌዲሪ ሕገ  መንግስት አንቀፅ 32/ ሰውየውን የከለከለ እንደሆነ ጥፋተኛ ነው በማለት የደነገገው፡፡

 

እዚህ ላይ  አንዳንድ  ነጥቦችን  እንመልከት የመጀመሪያው ሕግ  ሳይፈቀድለት የሚለው ነጥበ ነው፡፡ በሌላ  አባባል  አንድ ሰው  ሌላውን  ሰው ከቦታ  ቦታ  እንዳይዘዋወር መከልከል  ሕግ የፈቀደለት  ከሆነ  ጥፋተኛ  አይሆንም  ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ  የፍሐብሔር  ሕግ ቁጥር 265  እና በተሻሻለው  የቤተሰብ ሕግ /1992/  አንቀፅ  256  መሠረት አሳዳሪው አካለ  መጠን ያልደረሰውን ልጅ  መኖሪያ  ቦታ  የመወሰን ስልጣን  ብቻ ሳይሆን  አካለመጠን  ያላደረሰ ልጅ  ያለአሳዳሪው ፈቃድ  ያን ቦታ  ሊተው  አይችልም፡፡  ስለሆነም  አካለ መጠን  ያለደረሰው  ልጅ  ያን ቦታ ትቶ  የሄደ  እንደሆነ  አሳዳሪው  መኖሪያ  ቦታው  ላይ  እንዲመለስ ሊያስገድደው ይችላል፡፡ ስለዚህ  አካለመጠን  ያለደረሰውን ልጅ  የመዘዋወር ነፃነት  የመገደብ ስልጣን ለሞግዚቱ  አለው ማለት ነው፡፡

 

እንደተፈቀደለት የሚለው  ደግሞ   መብራራት ያለበት ሁለተኛው ነጥብ ነው፡፡ በእንግሊዝኛ / As he is  entitled to/ የሚለው  ነው፡፡ የእንግሊዝኛው የተሻለ  ይገልፀዋል፡፡ ይህ  ሐረግ  ቀጥታ  ሕግ  መንግስቱን ነው የሚያመለክተው የሕግ  መንግስቱ አንቀፅ 32 /1/ ይህን መብት ሲደነግግ

“ማንኛውም  ኢትዩጵያዊ  ወይም  በሕጋዊ መንገድ  ሀገሪቱ  ውስጥ  የሚገኝ  የውጭ ዜጋ  በመረጠው የሀገሪቱ አካባቢ የመዘዋወር እንዲሁም በፈለገው ጊዜ ከሀገር የመውጣት ነፃነት አለው”  ብሏል፡፡

 

ስለሆነም አንድ  ሰው  ሕግ  ሳይፈቅድለት  ከቦታ ቦታ እንዳይዘዋወር  የከለከለው ከሆነ ሕገ መንግስታዊ  መብቱን መንካት  መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

 

ሶስተኛው  ነጥብ  ደግሞ  መከልከሉ የግድ  ለረዥም ጊዜ መሆን የለበትም፡፡ በአማርኛው  ለተወሰነ ጊዜ  ይለዋል፡፡ እንግሊዝኛው ግን / Even for  a short time/ በማለት  ይገልፀዋል፡፡ ስለዚህ ይህ  መከልከል የግድ  ረዥም  ጊዜ  መሆን  የለበትም  ለአጭር ጌዜም  ቢሆን  ከልካዩን  ጥፋተኛ ያደርጋል፡፡ እንዲሁም   በተበዳይ /victim/ ሰውነት ላይ የግድ ጉዳት ማድረስ ይለበትም፡፡

 

 

መከላከያ  ቁጥር / 2ዐ42 እና 2ዐ43/

 

የመጀመሪያ  መከላከያ  ቁጥር  2ዐ42  ስር የተደነገገው  ነው፡፡ በዚህ ቁጥር መሠረት በሌላ ሰው  ነፃነት  ጣልቃ  የገባው  ሰው /ተከሣሽ/ ሁለት ነገሮችን  ማስረዳት ይጠበቅበታል፡፡

 

የመጀመሪያው ነፃነቱ የተነካበት ሰው  አንድ  የወንጀል  ድርጊት ሰርተዋል የሚለው  ነው፡፡ ድርጊቱ የወንጀል ድርጊት መሆን አለበት፡፡ በፍትሐብሔር  ሕግ  ተጠያቂ  ሊያደርግ የሚችል መሆን  የለበትም፡፡  ሁለተኛው  ነጥብ ደግሞ  የወንጀል  ድርጊቱን  ሰርቶአል  ብሎ  ለማሰብ የሚያስችለው  በቂ ምክንያት መኖሩን ማስረዳት አለበት፡፡ ይህን  በምሳሌ  እናስረዳ፡፡

 

አንድ  ሰው  በደም  የተበከለ ቢላዋ  ከደም  በተጨማለቀ እጁ  ይዞ   ቢገኝ  ይህን ሰው  ወንጀል ሰርተዋል ብሎ ለማሰብ በቂ ምክንያት  ሊሆን አይችልም  ሆኖም  ይህንኑ ሰው ሌሎች ሰዎች “ያዘው ያዘው” እያሉ  እየጮሁ  ቢያበሩት  እነዚህ ሁሉ  ተደምረው  ይህ ሰው  የወንጀል  ድርጊት ፈፅሟል  ብሎ  ለማሰብ በቂ ምክንያት ሊሆን  ይችላል፡፡ ስለሆነም ይህን ሰው  በቁጥጥር ስር ያለው ሰው  ጥፋተኛ  አይደለም ማለት ነው፡፡

 

ሌላ አንድ ምሳሌ  እንጨምር አንዲት የቤት እመቤት ባለቤቷን  በሌላ ሴት ትጠረጥረዋለች፡፡ እንበል አንድ ቀን ለቅሶ መሄዴ ነው  ብሎ  ሲወጣ በስውር ትከተለዋለች አባዋራውም  አንዲት  ጋለሞታ  ቤት ይገባና በሩ ይዘጋል ሚስትም  የተከረቸመውን በር እንዲከፍት  ብታንኳኳ  አይከፈትላትም በዚህ ጊዜ  በሩን ከኃላ  በቁልፍ ትቆልፍና ፖሊስ  ትጠራለች  ይህ ድርጊቷ ጥፋተኛ   አያሰኛትም ምክንያቱም  የመዘዋወር ነፃነቱ  የተነካበት /ባሏ/ ወንጀል  ሰርትዋል ብሏ ለማሰብ  በቂ  ምክንያት  /ከሌላ ሴት ጋር በሩን  መቆለፍ/ ስላላት ነው፡፡

 

ይህን  ወንጀል ሰርቷል ተብሎ  የተጠረጠረውን ሰው   አሳሪው  ወዴያውኑ  ለባለሥልጣኑ /ፖሊስ/ ማስረከብ ይኖርበታል፡፡ በምሳሌው ላይ የተጠቀሰችው  ሲትዩ በሩን  በቁልፍ  ከቆለፈች በኃላ  ወዲያውኑ  ፖሊስ  ጠርታለች፡፡ ደግሞ  የተጨማለቀውንም  ሰውዩ  ወዲያውኑ  ለፖሊስ  ማስርከብ  ያስፈልጋል፡፡  ይህ  ካልሆነ  ግን የዛን  ሰውዩ  የመዘዋወር ነፃነት የገደበው ሰው  በቁጥር 2ዐ42 /2/ መሠረት ጥፋተኛ ይሆናል፡፡

 

ሁለተኛው  መከላከያ  ቁጥር 2ዐ41  ስር  የተደነገገው ነው  በርግጥ ይህን ቁጥር  ለማስረዳት  እላይ   የገለፅነው   የአካለ  መጠን  ያለደረሰው  ልጅ  ሞግዚት ድርጊትን  መጠቀም  እንችላለን፡፡ ሆኖም  አንድ  ሌላ  ምሳሌ  እንውሰድ ፡፡

 

አንድ  ሰው  በሕግ  አግባብ  ቁጥጥር ስር  የዋለ  እንደሆነ የመዘዋወር  ነፃነቱ  ይገደባል፡፡  ይህንንም  የሚያስፈፅም  ሰው  ለምሳሌ  ፖሊስ  ጥፋት ሰራ  አይባልም  ሕግ  በሚፈቅድለት  አኳኋን  መሆን  እንዳለበት ቁጥር  2ዐ41     ይደነግጋል፡፡  በሌላ አባባል   በስልጣኑ  ስር  ያለን  ሰው  ማንገላታት የለበትም ነው  ይህ  እንደሆነም  የኢፌዲሪ  ሕገ መንግስት አንቀፅ  21  ስር

“በጥበቃ  ስር ያሎና  በፍርድ  የታሰሩ ሰዎች ሰብዓዊ ክብራቸውን  በሚጠብቁ ሁኔታዎች የመያዝ  መብት አላቸው” 

 

በማለት  ደንግጓል፡፡ ስለሆነም  የመዘዋዋር ነፃነታቸው   የተገደበ ሰዎች   ሰብዓዊ ክብራቸውን በሚነካ  ሁኔታ  መያዝ  የለባቸውም  ይህን የጣሰ ሰው  የተያዡን ሕገ  መንግስታዊ  መብት ስለሚነካ  ጥፋተኛ  ይሆናል፡፡

 

ሌላው  መነሳት ያለበት ነጥብ  ደግሞ ነፃነቱ  የተነካበት ሰው   ነፃነቱን በነካው  ሰው  ስልጣን  ስር ያለ  መሆን አለበት ይህ ስልጣን  ከሕግ  ወይም  ከፍርድ ቤት ትዕዛዝ  ሊመነጭ  ይችላል፡፡  ሞግዚቱ አካለ  መጠን  ባለደረሰ ልጅ ላይ  ያለው  ስልጣን  የሚመነጨው ከሕግ  /የፍትሐብሔር  ሕገ ቁጥር 265 እና  የተሻሻለው የቤተሰብ  ሕግ ቁጥር 256/ ሲሆን የፖሊስ ደግሞ ከፍርድ ቤት ትዕዛዝ ወይም  ከሕግ የመነጨ ሊሆን ይችላል፡፡

 

በመጨረሻም ዋስ  የሆነ  ሰው  ዋስ የሆነለት ሰው  ሊጠፋ ነው የሚያስብል  መሰናዶ ማድረጉን  የሚያሳምን   በቂ  ምክንያት  ካለው የዚህን ሰው  ነፃነት  ቢነካበት ጥፋተኛ  እንደማይሆን  ቁጥር  2ዐ43  ይደነግጋል፡፡ ይህን ቁጥር በጥንቃቄ  መመልከት  የሚያሻ  ይመስለኛል፡፡  ምክንያቱም ቀድሞ  ግዞት   ከሚባል ፅንሰ  ሃሳብና  ተግባር ጋር  የተያያዘ ሊሆን ይችላል፡፡ ይህን   የሚልበት ምክንያት  አንድ ሰው  ለሌላ ሰው  ዋስ የሚሆነው ዋስ የተገባለት  ሰው ባንድ  በተወሰነ ቦታ እንዲኖር  ነው፡፡  ይህን  ዋስትና  የሚሰጠው  ደግሞ  ለመንግስት ባለስልጣናት  ነው፡፡  ስለዚህ  ዋሰ  የተገባለት  ሰው ዕዳ  ኖሮበት ወይም  የወንጀል  ድርጊት በመፈፀም  ተጠርጥሮ  ሳይሆን ዋስ የሚኮንለት  ባንድ በተወሰነ ቦታ እንዲኖር  ነው፡፡  በቀድሞ  ጊዜ  ሰዎች  ለንጉስ  ነገስቱ  የፖለቲካ  ተቀናቃኝ  ከሆኑ   ወደ ገጠር  ይወሰዱና  አንድ  አካባቢ  ብቻ  እንዲኖሩ  ለዚህም  ጠዋትና   ማታ  ፖሊስ  ጣቢያ  ሪፖርት   እንዲያደርጉ  ይደረጋሉ፡፡  ያን  ስፍራ  እንደማይለቁ ደግሞ   ዋስ  ይጠራሉ  ያ ዋስ  ነው እንግዲህ  ግዞተኛው  ቦታውን  ለቆ ለማምለጥ   መሰናዳቱን የሚያሳምን  በቂ ምክንያት  /ለምሳሌ  ዕቃዎችን  ያሰናዳ መንገድ  ለመሩት ከሚችሎ  ሰዎች  ጋር  ተነጋግሮ  ቀብድ  ከከፈለ ወዘተ/  ካለው  ይህ ሰው እንዳይንቀሳቀስ ሊያግደው  ይችላል፡፡  ይህን ማድረጉ ግን  ጥፋተኛ  አያደርገውም፡፡

 

ግዞት  ግን በአሁኑ  ጊዜ ቀርቷል፡፡ ሰዎች   ለፖለቲካ   አመለካከት  የመያዝ  ብቻ ሳይሆን ያን  አመለካከት  በሰላማዊ  መንገድ  የማራመድ  በነፃ የፖሊቲካ  ውድድር ተወዳድሮ  የመንግስት ስልጣን  የመያዝ  መብታቸው  በኢፊድሪ  ሕገ መንግስት  ተረጋግጧል፡፡  ይህን  በማድጋቸው   በግዞት በአንድ  ቦታ እንዲቆዩ  የሚደረጉበት ምክንያት  የለም፡፡ /በአንድ  ቦታ ለመቆየት ጥሩ  ምሳሌ  የሚትሆነን የበርማዋ ተወላጅ  የናቢል  ሰላም ተሸላሚዋ ሚስ ሳንሶዥ ናት ዛሬ ይህች   ፖለቲከኛ  በወታደራው ጁንታ ከቤቷ እንዳትወጣ /House  arrest ይሉታል ፈረጆች/   ተወስኖባታል፡፡ ምናልባት  ለዚህ አንድ  ሰው ዋሰ  እንዲሆኗት ጠርታ  እንደሆነና ዋስ   ልትጠሩ  መሰናዶ  ብታደርግ  ዋስ  የሆኗት ሰው  ከዛ ቤት እንዳትወጣ  ሊያደርጋት ይችላል፡፡ 

ሰውነትን ስለ መጉዳት ቁጥር /2038/

Details
Category: Non-Contractual Liability (Tort Law)
18.Feb
Hits: 7612

የኮመን  ሎው  አገሮች  /Battery/ ይሉታል፡፡ ሲቪል ሎው  አገሮች  ደግሞ  /Physical assault/ የሚሉት  ነው፡፡  በኢፌዲሪ ሕገ መንግስት አንቀፅ  14 መሠረት ማንኛውም  ሰው  ሰበዓዊ በመሆኑ የማይደፈርና የማይገሰስ በሕይወት የመኖር  የአካል ደህንነትና  የነፃነት መብት  አለው፡፡ የአካል ደህንነትና የነፃነት  መብትን ይህን ቁጥር ማለት 2ዐ38ን እና  ቀጣዩን  ቁጥር ማለት ቁጥር 2ዐ4ዐ ስንወያይ እናነሳቸዋለን፡፡  እነዚህ  ሐገ መንግስታዊ  መብቶች  ላልናቸው  ቁጥሮች  መሠረቶች  ናቸው፡፡

ስለሆነም   የኢፌዲሪ  ሕገ መንግስት አንቀፅ  16 እንደሚደነግገው ማንኛውም ሰው በአካሉ ላይ ጉዳት እንዳይደርስበት  የመጠበቅ  ሕገ መንግስታዊ መብት  አለው፡፡ ይህ መብት በፍትሐብሔር  ሕገ  ቁጥር 2ዐ38  እንደተደነገገው  አንድ ሰው ሳይፈቅደ ሰውነቱ ያለመነካት  መብትንም  ይጨምራል፡፡ ስለሆነም አንድ ሰው  ሆን ብሎ  ሌላው ሰው  ሳይፈቅድ  ሌላውን ሰው ከነካ  ነኪው  ጥፋተኛ  ነው፡፡ ይህ ቁጥር የሚነግረን  አንድ ሰው  በሰውነቱ ላይ አዛዥ   ራሱ ብቻ መሆኑን  ነው፡፡  ለዚህም ይመስላል የኢፌዲሪ  ሕገ መንግስት አንቀፅ 14 ስር  ለማንኛውም ሰው  ሰብዓዊነት አፅንዎት  የሰጠው ይህን  የፍታብሔር ቁጥር አስመልክቶ  አንዳንድ ነጥቦችን እናንሳ፡፡ የመጀመሪያው የሌላን  ሰው  ሰውነት የሚነካው ሰው ንኪኪውን የሚያደርገው  ሆን ብሎ /Intentionally/ ነው፡፡ ሁለተኛ  የተነኪው  ፍላጐት የለም፡፡ ስለሆነም  ነኪው  የነኪውን ሰውነት ተገዶ ቢነካ  ወይም በቸልተኝነት  ቢነካ የተነኪው  ፍላጐት በይኖርም  እንኳን  ጥፋተኛ አይሆንም፡፡

 

በተጨማሪ ደግሞ ነኪውን  ጥፋተኛ  ለማድረግ  የተነካው  ሰው ላይ ጉዳት መድረስ የለበትም፡፡ ሌላው  መነሳት  ያለበት ነጥብ የሌላን  ሰው ሰውነት የሚነካው  ሰው መንካቱን የግድ በቀጥታ ማድረግ  አይጠበቅበትም  እንዲሁም ድርጊቱን ለመፈፀም  ሕይወት ያለው  ነገር ወይም የሌለው  ነገር  መጠቀም ይችላል፡፡

 

በምሳሌ  እናስረዳ ጫልቱ  ዛፍ ስር ጥላ  ፍለጋ ተቀምጣለች  እንበል፡፡ መሐመድ  ዛፋን ሆን ብሎ  በማነቃነቅ  የዛፍ ቅጠሎች እና ፍሬዎች በጫልቱ ላይ  እንዲወድቅ  ቢያደርግ  በቁጥር  2ዐ38/2/ መሠረት  ተጠያቂ ይሆናል፡፡ መሐመድ  ጫልቱን ለመንካት እዚህ ጋ የተጠቀመው ሕይወት ያለውን ነገር  ቀጥታ ባልሆነ   መንገድ ነው፡፡ በሌላ  በኩል ደግሞ አቶ  ጊግሶ  ውሻ አልጥኖ  ውሻው  የሌላን  ሰውነት እንዲነካ  ሆን ብሎ  ቢያደርግ  አቶ  ጊግሶ ጥፋተኛ  ይባላል እንዲሁም  በሩቅ ቁጥጥር በሚደረግበት  አሸንጐሊት  የሌላን  ሰው  ያለፍላጉት መንካትም  ጥፋተኛ ያደርጋል፡፡ ቀጥለን  መከላከያዎችን  እንመለከታለን፡፡

 

በቂ ምክንያት ቁጥር /2ዐ39/

 

በዚህ  ቁጥር  ስር  አራት ንዑስ ቁጥሮች አሉ፡፡ የመጀመሪያው  ሀ ስር  ያለው  ሲሆን እንዲህ ይነበባል፡፡

              “ከሣሹ በአአምሮ ግምት ሊያስበው የማይችል መሆኑ የታወቀ እንደሆነ “

 

ይህን  በምሳሌ  ለማስረዳት እንሞክር  ፋጡማና ከድር  የአንድ ክፍል ተማሪዎች  ጓደኛሞች ናቸው እንበል፡፡ ሁለቱ ጓደኛሞች  ሁልጊዜ  ሲገናኙ   ይጨባበጣሉ ይላፋሉ እንበል በመሃል ፋጡማ ወደ እስልምና ትምህርት  የሚሰጥበት ትምህርት ቤት  መሄድ በመጀመሯ ሊጋቡ  የሚችሉ  ወንድና ሴት ባልና ሚስት ካልሆኑ  ሰውነታቸው  መነካካት  ይለበትም  የሚል ትምህርት  ተማረች እንበል፡፡ አንድ ጠዋት ከድር ከኃላዋ  መጥቶ አይኗን  ቢይዛትና  ፋጡማ በቁጥር 2ዐ38  መሠረት ክስ ብትመሠርት ከድር ቀድሞ ከነበራቸው  ግንኙነት አንፃር ፋጡማ የእሱን  አድራጉት  እንደምትቃወም በአእምሮው  ግምት ሊያሰበው  የማይችል  መሆኑን ካስረዳ  ጥፋተኛ መሆኑ ይቀርለታል፡፡

 

ሁለተኛው  የመከላከያ ነጥብ  አንድ ሰው  የራሱን ወይም  የሌላን ሰው ከአደጋ ለመከላከል  ወይም በደንቡ መሠረት  ንብረቱ  የሆነውን ወይም  በይዞታው  ስር ያለን ንብረት ለመከላከል በሚደረግ   ትንንቅ የሊላን ሰው ሰውነት ቢነካ ጥፋተኛ  መባሉ  ይቀርለታል፡፡ ለምሳሌ አንድ  ጐረምሳ አንዲትን  ልጅ  የሐይል  ጥቃት ሊያደርስባት  ፈልጐ  ጐረምሳውን  ገላጋይ  ቢይዘው ገላጋዩ  ጥፋተኛ አይባልም፡፡ እንዲሁም የፍትሐብሔር  ቁጥር 1148/2/ ስር እንደተደነገገው በእጁ ያደረገውን ነገር  በንጥቂያ  ወይም በስውር የተወሰደበት  እንደሆነ ነገሩን  በግፍ /በጉልበት/ ሲወሰድ  ከተገኘው ወይም ይዞ  ሲሸሸ ከተያዘው  ነጣቂ ላይ ወዲይውኑ በጉልበት  ለማስለቀቅ የተወሰደበትን  ነገር  ለመመለስ ስለሚችል  ይህን ለማድረግ  የነጣቂውን ወይም  የሌላውን ሰውነት  የግድ  መንካት ስለሚኖር  ነኪው  ጥፋተኛ አይሆንም፡፡

 

በቁጥር 2ዐ39 /ሐ/ ስር ያለው  መከላከያ  በአሁኑ   ጊዜ  ተገቢነት ያለው አይመስለንም፡ በሁለት  ምክንያት  የመጀመሪያው በኢፌዲሪ ሕገ መንግስት አንቀፅ 36/1//ሠ/ ስር  እንደተደነገገው  ህፃናት በአካላቸው  ከሚፈፀም  ወይም ከጭካኔና  ኢሰብአዊ  ከሆነ  ቅጣት ነፃ የመሆን መብት አላቸው፡፡ ሁለተኛ  ደግሞ  ይህ የመከላከያ ንዑስ  ቁጥር የሚያመለክተው  የፍትሐብሔር ቁጥር 267/2/ ነበር፡፡ በዚህ ንዑስ ቁጥር መሠረት አሳዳጊው ቀለል ያሉ  የሰውነት ቅጣቶችን  አካለ መጠን ባለደረሰ ልጅ ላይ ለመፈፀም  ይችላል፡፡ ሆኖም ግን የኢፌዲሪ ሕገ መንግስት  በህፃናት  ላይ  ማንኛው ዓይነት  የሰውነት  ቅጣት  እንዳይፈፀም  ይከለክላል፡፡  በተለይ እንግሊዝኛው  “ To be free of corporal punishment” ይላል፡፡ ይህንኑ ተከትሎ  የወጣውም አዲሱ የተሻሻለው የቤሰተብ ሕግም እላይ የጠቀስነውን ቁጥር 267/2/ ትን  አንቀፅ 258/2/ ስር  አሳዳሪው  አካለመጠን ለልደረሰው ልጅ መልካም አስተዳደግ  ተገቢነት ያለውን የዲስፒሊን እርምጃ ለመውሰድ ይችላል፡፡ በማለት ተክቶታል፡፡ ከዚህ ሁሉ  የምንረደው  በልጅ  ላይ  የሚፈፀም  ቅጣት ጥፋት እንደሆነና መከላከያ እንደማይሆን ነው፡፡ ለልጅ ያልነው ነገር ሁሉ ለተማሪም ለአሽከርመ /ለሠራተኛ/ ይሆናል፡፡ ስለሆነም ለተማሪ እና ሠራተኛ  ስውነት ላይ ቅጣት  መፈፀም ኢ-ሕገመንግስታዊ ስለሆነ እንደመከላከያ ሊያገለግል አይችልም፡፡

 

ሶስተኛው  የመከላከያ  ነጥብ አንድ  ዕብድ  በራሱ ወይም  በሌላ ሰው  ላይ  እንዲሁም በንብረት  ላይ ጉዳት እንዳያደርስ  ለመከላከል  በሚደረግ ጥረት  የሚፈጠር መንካት  ነው፡፡ ለምሳሌ  የፍትሐብሔር ቁጥር 342 ስር አንድ ሰው  ዕብደቱ  በግልፅ  የታወቀ ነው የሚባለው  አብረውት  የሚኖሩት  ወይም  ቤተዘመዶቹ  የተባለው  ሰው  መዘዋወር ላይ ገደብ ሲያደርጉ ነው፡፡ የዚህ ገደብ ማድረጊያ  አንዱ መንገድ  ዕብዱን ሰው በገመድ ማሰር ነው፡፡ ይህ ድርጊት የግድ ዕብድ  የተባለው ሰው  ሰውነት መንካትን  ይጋብዛል፡፡ በዚህ ሁኔታ ስር  ነኪው ጥፋት ሰርቷል አይባልም፡፡ አንድ ነጥብ እናክል፡፡ ይህ መንካት  የሚፈቀደው አደገኛ ዕብዱን አደጋ እንዲያደርስ በሌላ አኳኃን ለመከላከል  ካልተቻል ነው፡፡ ለምሳሌ  ሐኪም  እንዲያስተኛው  ብሎም  እንዲረጋጋ የሚይደርገው መድሃኒት አዞለት እያለ ያን መድሃኒት እንዲወስድ  ማድረግ ሲገባን  ያን ሳናደርግ ከቀረን እንደ ማለት ነው፡፡ በመጨረሻም ዕብዱ ማንኛውም ተራ ዕብድ  ሳይሆን አደገኛ ዕብድ  መሆን አለበት፡፡ ይህን የምናረጋግጠው አደገኛ ዕብድ  ነው  የተባለው  ከፈፀማቸው የቀድሞ ተግባሮችና ጉዳቶች በመነሳት  ወይም አዋቂ በማስመስከር ሊሆን ይችላል፡፡

 

የመጨረሻው መከላከያ ደግሞ ትክክለኛ አእምሮ ያለው ሰው /reasonable man/ ትክክለኛ ነው ብሎ የሚገምተው ከሆነ ድርጊቱ እንደጥፋት አይቆጠርም፡፡ 

ከውል ውጪ የአላፊነት ምንጮች

Details
Category: Non-Contractual Liability (Tort Law)
18.Feb
Hits: 8928

ከውል ውጭ የሆኑ የአላፊት ምንጨች ሶስት  ናቸው፡፡  የመጀመሪያው  ጥፋት  ነው፡፡ ሁለተኛው  የአንድ ሰው እንቅስቃሴ  /Activity/ ወይም  በእጅ  የያዘው ወይም ንብረቱ የሆነ  ነገር ነው፡፡ ሶስተኛው  ደግሞ አላፊ የሆኑለት ሰዉ  በጥፋት ምክንያት ወይም በሕጉ  መሠረት  አላፊ መሆን  ነው፡፡ የፍትሐብሔር  ሕግ ቁጥር 2ዐ77 /1/ የመጀመሪያውን አንድ ሰው  በራሱ  በኩል ምንም የገባው ግዴታ ሳይኖር በራሱ  ጥፋት  በሌላው ሰው ላይ  ጉዳትን ካደረሰ አላፊ  ነው ይላል፡፡  በዚህ ድንጋጌ  ቁጥር  ስር  የሚመደበት ከቁጥር  2ዐ28 እስከ ቁጥር 2ዐ65  ያሉ ናቸው፡፡  እነዚህን  ቁጥሮች በአራት ንዑሳን  ክፍሎች  ከፍለን  በዝርዝር እንመለከታለን፡፡

ቁጥር  2ዐ27/2/ ደግሞ ሁለተኛውን ምንጭ ሲደነግግ አንድ  ሰው  በሕጉ ላይ እንደ ተመለከተው በሌላ ሰው ላይ ጉዳት ሊያደርስ የሚችለው ሥራ  ከሠራ /ከቁጥር 2ዐ66-ቁጥር 2ዐ76/ ወይም በእጅ  የያዘው  ነገር /ከቁጥር 2ዐ77-ቁጥር 2ዐ85/ በሌላ ሰው  ላይ ጉዳት ካደረሰ  አላፊ  ይሆናል ይላል፡፡

 

ሶስተኛው ምንጭ ሲደነገግ በጥፋት ምክንያት /በቁጥር 2ዐ28-2ዐ65/ ወይም በሕጉ መሠረት ሲኖር ሌላ ሰው ለፈፀመው  አድራጐት  በሕጐ  አላፊነት አለበት የተባለው ሰው አላፊ ነው ይላል፡፡

 

በእነዚህ ንዑስ ቁጥሮች ውስጥ ከወዲሁ መብራራት ያለባቸው  ሀረጐች  አሉ፡፡  በቁጥር 2ዐ28/1/ ስር  አንድ  በራሱ  በኩል ምንም የገባው ግዴታ  ሳይኖር   የሚል  ሀረግ  አለ፡፡   ይህ  ሀረግ የምያነሳው  እላይ  በውልና ከውል ውጨ  አላፊነት  ሕጉች  ልዩነት   ስንወያይ የግዴታዎች  ምንጨች ይለያያሉ ያለውን ነው  የሚያጠናክረው፡፡  በሌላ አባባል በውል ሕግ መሠረት  ለአላፊነት  ምንጩ  የተዋዋይ ወገኖች  ስምምነት ሲሆን  ከውል ውጭ አላፊነት መሠረቱ  ግን የተዋዋይ ወገኖች ውል ሣይሆን  ሕግ ነው ማለት ነው፡፡ 

 

ስለሆነም በ2ዐ28/1/ መሠረት አላፊ ለመሆን  አጥፊው  ጥፋት ቢሰራ  አላፊ እሆናለሁ  በማለት ግዴታ መግባት የለበትም፡፡ አላፊ  ለመሆን የሚያስፈልገው  ጥፋት መስራት በጥፋት ደግሞ  ጉዳት ማድረስ ለጉደቱ ደግሞ የተፈፀመው  ጥፋት ምክንያት መሆን ናቸው፡፡ንዑስ ቁጥር  ሁለት ስር  ደግሞ   በሕጉ ላይ እንደተመለከተው የሚል  ሀረግ አስፈላጊነት  አንድ  ሰው  በሰራው ሥራ በሌላ ሰው  ላይ ጉዳት በማድረስ አላፊ የሚሆነው  ሕግ  አላፊ ይሆናል ሲል ነው፡፡  ለዚህ ምሳሌ የሚሆነን ቁጥር 2ዐ7ዐ ነው፡፡  በዚህ ቁጥር  መሠረት ሥራ ብቻውን  አላፊነትን አያስከትልም፡፡  ሥራው ጥፋት ያለበት መሆን  አለበት፡፡  ያን  ጊዜ ብቻ ነው በሥራው ምክንያት ጉዳት ያደረሰ ሰው  አላፊ የሚሆነው፡፡

 

በጥፋት ላይ  ስለተመሠረተ አላፊነት

 

ይህ አላፊነት  የተደነገገው በፍተሐብሔር  ሕግ ቁጥር  2ዐ28-2ዐ65 ድረስ  ባሉት  ነው፡፡  ይህ ደግሞ  እንደገና በሁለት ይከፈላል፡፡  ከቁጥር  2ዐ28-2ዐ37  ድረስ ያሉት ጠቅላላ ደንቦች  በሚል ስር  የተመደቡ ሲሆን ከ2ዐ38-2ዐ65 ድረስ ያሉት ደግሞ ልዩ ሆኔታዎች  በሚለው ስር ተመድበዋል፡፡

 

በጥፋት  ላይ  የተመሠረተ አላፊነትን  በሶስት  ክፍሎች ከፍለን ማየት እንችላለን፡፡ የመጀመያው  ከሰው ሰውነት  ጋር  በተያያዙ መብቶች  ላይ  የተደረገ ጥፋት  ብለን  መመደብ እንችላለን፡፡  በመጨረሻም  በንብረትና  በኢኮነሚያዊ መብት ጋር  በተያያዘ የተደረገ ጥፋት ማለት እንችላለን፡፡ ሶስተኛ  ደግሞ  ሌሎች  ብለን መመደብ  እንችላለን፡፡

 

ከሰው ሰውነት ጋር  በተያያዘ መብቶች ላይ  የተደረገ ጥፋት

 በሞያ ሥራ ላይ  የሚደረግ ጥፋት /2ዐ31/

  

ይህ  የጥፋት ዓይነት  በሞያተኛ የሚፈፀም የጥፋት  ዓይነት  ነው፡፡  ስለሆነም ሞያ   ማለት ምን  ማለት እንደሆነ ማወቅ አስፈላጊ  ነው፡፡ የተለየ ስልጠና  ክህሎት እና እውቀት   የሚያስፈልገው  ክወና /activity/ ሞያ  ይባላል፡፡  ለምሳሌ  መኪና መንዳት ሞያ ነው፡፡  ድንጋይ በባሬላ ማጓጓዠ ወይም  ከጭነት መኪና  ላይ በርበሬ መጫን  ወይም ማራገፍ ሞያ አይባልም፡፡

 

ሞያ  የራሱ የሆነ  ሕጉች ወይም  መመሪያዎች  አሉት፡፡  እነዚህ  ሕጐች  በፅሑፍ የተቀመጡ  ወይም ያልተፃፋ  ሊሆኑ  ይችላሉ፡፡  ለምሳሌ  የመኪና  መንዳት  ሞያ  ሕጐች   በፅሁፍ ያሉ ናቸው፡፡ እነዚህን የተፃፋ ሕጐች እያንዳንዱ አሽከረካሪ አውቋቸው  በዛው መሠረት መኪናውን ማሽከርክር  አለበት፡፡  የሞያው ሕጐች  /rules/ ማየት ያስፈልጋል ለዚህም ይመስላል ቁጥር  2ዐ35 /1/ ስር አንድ ሰው  በሕግ ላይ  በትክክል ተገልጾ የተመለከተውን ልዬ  ድንጋጌ  ልዬ ደንብና  ስርዓት የጣሰ እንደሆነ ጥፋተኛ ነው በማለት የደነገገው በፅሑፍ ካልሆነ ግን  ባለሞያ  ጠርተን  መሰማት የግድ  ይላል፡፡ 

ሞያን አስመልክቶ ቁጥር  2ዐ3ዐ /2/  ስር የተቀመጠው  ትክክለኛ አእምሮ  /reasonable man/ ያለው ሰው ተብሎ  የቀመጠው ትክክለኛ  አአምሮ  ያለው  ባለሞያ ማለት መሆኑን  መዘንጋት አያስፈልግም፡፡

 

የመጉዳት ሃሳብ ቁጥር 2ዐ32

 

ይህ ቁጥር  ዋና መሠረተ  ሀሳብ  / Intention /  ነው  ስለሆነም   አንድን ሰው   በዚህ ቁጥር  መሠረት ጥፋተኛ  ለማድረግ ሀሳብ  /Intention/  መኖሩን ማረጋገጥ  ይጠይቃል፡፡  ምክንያቱም ንዑስ  ቁጥር /1/ ስር በማሰብ የሚል ቃል ሲኖር  ንዑስ  ቁጥር /2/ ስር ደግሞ  እያወቀ የሚል ቃለ እናግኛለን፡፡   ስለሆነም   የጤነኛ አአምሮ  መኖርን  ይጠይቃል ማለት ነው፡፡  ይህም በመሆኑ ቁጥር 2ዐ3ዐ /3/ ለዚህ ቁጥር አግባብንት ያለው አይመስልም፡፡ 

 

በዚህ ቁጥር ንዑስ ቁጥር 1  እና 2 ያሉ ልዩነቶችን  እንመልከት፡፡ የመጀመሪያው ልዩነት ንዑስ  ቁጥር /1/ ስር አንድ ሰው ሆን ብሎ ድርጊቱን  የሚፈፀመው የግል  ጥቅሙን ለመፈለግ አይደለም፡፡  በንዑስ  ቁጥር ሁለት  ስር ድርጊቱን የሚያከናውነው የራሱን ጥቅም  ሲፈለግ ነው፡፡  ስለሆነም በንዑስ ቁጥር  አንድ ስር ዋና አለማው የግል ጥቅም ማግኘት ሳይሆን ሌላውን መጉዳት ነው፡፡  በንዑስ  ቁጥር 2 ስር ግን ዋናው ግብ የራስን ጥቅም ማግኘት ነው፡፡  ሌላው ከንዑስ  ቁጥር ሁለት ጋር  ተያያዞ  መነሳት  ያለበት  ጥፋት ፈፀመ  የተባለው በዚህ ንዑስ  ቁጥር  መሠረት    ተጠያቂ ለማድረግ የደረሰው ጉዳት ከተገኘው  ጥቅም ብልጫ ያለው መሆን አለበት ሌላው ነጥብ ደግሞ ጉዳቱን ያደረሰው  ድርጊት  በሕግ የተፈቀደ ድርጊት መሆን አለበት፡፡

 

በስልጣን ያለአግባብ መጠቀም ቁጥር 2ዐ33

 

በዚህ ቁጥር  ስር ሁለት የስልጣን ዓይነቶችን  እናገኛለን፡፡ አንደኛው ዓይነት  ስልጣን የግለሰብ ጥቅምን ለመጠበቅ /Interest of a given private individual/  የተሰጠ ሥልጣን ሲሆን ሁለተኛው ዓይነት  ደግሞ  ለጠቅላላው ጥቅም እንዲያገለግል / In the  interest of the public/  የተሰጠው ስልጣን ነው፡፡ ለመጀመሪያው  ዓይነት  ስልጣን  ምሳሌ  የሚሆነን    በተለያየ ምክንያት ችሎታ ያጡ  ሰዎችን  ጥቅም  ለመጠበቅ ለአሳዳሪውና ለሞግዚት የተሰጠ ስልጣን  ሲሆን ለሁለተኛው ደግሞ ዳኛና ዓቃቢ  ሕግ  ያላቸው ስልጣን ምሳሌ  ሌሆን ይችላል፡፡

 

እንዲሁም የትኛውም ዓይነት  ስልጣን  ይሆን  አንድ ሰው የተሰጠውን ስልጣን ለግል ጥቅሙ የሠራበት   እንደሆነ  በስልጣን  ያለአግባብ መጠቀም አለ እንላለን፡፡  በሁሉተኛው የስልጣን  ዓይነት  የመንግስት ሠራተኛው  በሹመት ያገኘውን  ስልጣን  ለተለየ ሰው  ጥቅም ካዋለውም በስልጣኑ  ያለ አግባብ ተጠቅሟል ይባላል፡፡  ሁለቱም ዓይነት  በስልጣን  ያለ አግባብ መጠቀም ጥፋት ነው፡፡

 

የዚህን ቁጥር ንዑስ ቁጥር ሁለትን  አስመልክቶ  አንዳንደ ነጥቦችን  ግልፅ እናድርግ  የመጀመሪያው  ግለሰቡ  የመንግስት ሠራተኛ  መሆን  አለበት፡፡ የመንግስት  ሠራተኛ  ማለት በአዋጅ ቁጥር 262/1994 አንቀፅ 2/1/ ስር ከ ሀ - ሠ ያሉትን  ሳይጨምር  በመንግስት መሥሪያ  ቤት ውሰጥ  በቋሚነት  ወይም  በጊዜያዊነት  ተቀጥሮ የሚሰራ ሰው  ማለት ነው፡፡  ሁለተኛ  ስልጣኑ የተሰጠው ለጠቅላላው ጥቅም ሲባል መሆን አለበት የስልጣኑ /Public interest/ ምንጭ ደግሞ  ሹመት ወይም ሥራው  / Powers conferred up on him….. by  his office / መሆን አለበት፡፡

 

ስለ መብቶች ግብ ቁጥር /2ዐ34/

  

ንብረቶች  ኢኮነሚያዊና ማህበራዊ ግቦች አሏቸው፡፡ ለምሳሌ የአንድ ቤት ኢኮነሚያዊና ማህበራዊ ግብ የመኖሪያነት ወይም አከራይቶ ኪራይ  መሰብሰብ ሊሆን  ይችላል፡፡ የአንዲት ሚኒባስ  ኢኮነሚያዊና ማህበራዊ ግብ ሰዎችን በማጓጓዝ ገቢ ማግኘት ሊሆን ይችላል፡፡

 

የቤቱ ባለቤት ቤቱን ላይኖርበት፣ ላያከራየው ቆልፎ ሊያስቀምጠው ይችላል፡፡ የሚኒባሱም ሰውዩ ሚኒባሷን ሳይጠቀምባት ሊያቆማት  ይችላል፡፡  ባለንብረቶቹን  ይህን  ለምን  አደረጋችሁ ብሎ የሚጠይቃቸው  የለም፡፡  በንብረት ያለመጠቀም  መብት  ከንብረት መብቶች አንዱ ነውና፡፡  ለዚህ ይመስላል ቁጥር 2ዐ34 አንድ ሰው የተሰጠውን በሥራ ላይ ያዋለበት ሁኔታ ከኢኮነሚክና /የቁጠባ ዘዴ/ ከማህበራዊ አሰተዳደር ጋራ ተስማሚ አይደለም በማለት መንቀፍ አይቻልም በማለት የደነገገው፡፡ 

 

ሆኖም  በዚህ ቁጥር  መግቢያ ላይ  ከዚህ በላይ ባሉት ቁጥሮች  የተመለከቱት ደንጋጌዎች  ሳይነኩ  የሚል ሀሪግ  አለ፡፡  ይህን ሀረግ  እላይ ያስቀመጥነውን  አንድ ምሳሌ  በመውሰድ እናስረዳ፡፡  የትራንስፖርት  እጥረት አለ አንበል፡፡ አቶ ዘበርጋ ሚኒባሱን  ምንም ዓይነት ብልሽት  ሳይኖርባት  አቆማት አንበል አንድ ግምት መውሰድ እንችላለን፡፡  አቶ  ዘበርጋ  ሚኒባሷን  ያቆማት ሆን ብሎ ጐዳት ለማድረስ /Injure/ ነው በማለት ነው፡፡

 

ሌላም ምሳሌ  እንውሰድ የአዲስ አበባ ሚኒባስ ታክሲዎችና አንዳንድ ግለሰቦች  ከግንቦት 1997 ዓ.ም  ምርጫ ማግስት ለተወሰኑ ቀናት ሚኒባስአቸውን   እንዳይሰሩ  አድርገው ነበር አንዳንድ ግለቦችም  ሱቅአቸውን ዘግተው  ነበር በአዘቦት ቀን /Normal days/ ቢሆን  ኖሮ   ያ ድርጊታቸው  አይነቀፍም  ነበር፡፡ ግን  በዛን  ጊዜ  ያ  ድርጊት የተደረገው ሆን ብሎ  ጉዳት / Intention to injure 2032/  ስለሆነ መንግስት  ሥራ  ካልጀመሩ  የሥራ ፍቃዳቸው እንደሚነጥቃቸው አስጠነቀቃቸው፡፡  መንግስት ይህን ያደረገው  የባለንብረቶቹ ድርጊት  መብታቸውን በሥራ ላይ  ያዋሉበት ሁኔታ   ከኢኮነሚክስና ከማህበራዊ አስተዳዳር ጋራ  ተስማሚ  ስላልነበረ አልነበረም፡፡  ይልቁንም ድርጊቶቹ የተፈፀሙት  ሆን ብሎ በሌሎች ላይ ጉዳት ለማደረስ ተብሎ ስለነበረ ነው፡፡

 

ሕግን ስለመጣስ ቁጥር /2ዐ35/

 

አንድ ሰው  አታድርግ የተባለውን በማድረግ / Commission /  ወይም  አድርግ የተባለውን ባለማድረግ / Omission / ሕግን ሊጥስ ይችላል፡፡  በዚህ ቁጥር  የተጣሰው ድንጋጌ  / Law / ልዩ ደንብ   / decree /  ወይም ስርዓት  /Administrative  regulations / ሊሆን ይችላል፡፡  በአማርኛውና በእንግሊዝኛው  መካከል ስለሚታየው አለመጣጣም አሁን  ምንም አንልም ይልቅ አንድ ሶስት ነጥቦችን እናንሳ፡፡

     

የመጀመሪያ የተጣሰው  ሕግ /specific/ መሆን አለበት በሌለ አባባል /General/ አጠቃላይ  መሆን የለበትም፡፡ ማለት ለትርጉም የተጋለጠ መሆን የለበትም፡፡ ይህን በምሳሌ  እናስረዳ ይህን የምናደርገው  ቁጥር 1758 እና ቁጥር 2323  በማወዳዳር  ነው፡፡ ቁጥር 1758 /1/ የሚደነግገው ስለባለዕዳ ነው፡፡  ባለዕዳው     ሻጭ  ወይም ገዥ  ሊሆን ይችላል፡፡ አካራይም ወይም ተከራይም ሊሆን ይችላል፡፡  ቁጥር 2323 ግን  ስለገዥው  ነው የሚደነግገው፡፡ በቁጥር 1758 ትም በቁጥር 2323 ትም  ስለ አደጋ /risk/ ነው የተደነገገው  ግን  ቁጥር  1758 ከቁጥር  2323 ጋር  ሲነፃፀር  አጠቃላይ ሲሆን ቁጥር 2323 ግን ልዬ  /Specific/ ነው፡፡  ስለሆነም  ቁጥር 1758 ለትርጉም የተጋለጠ ነው፡፡

 

ሌላው  ስለቁጥር 2ዐ35  ማንሳት የሚገባን  ነጥብ የተጣሰው  ሕግ  /explicit / መሆን አለበት፡፡  /Implicit/ መሆን ይለበትም፡፡  ማለትም ግልፅ  መሆን  አለበት ሶስተኛ ነጥብ ደግሞ ጥፋቱ በሌሎች  ከውል ውጨ አላፊነትን በሚደነግጉት ቁጥሮች የሚስተናገድ ከሆነ ቁጥር 2ዐ35 ን እንጠቀምም፡፡  በመጨረሻም ከተዋዋዩች  ወገኖች  መሃል አንዱ በውሉ መሠረት ግዴታውን ባይፈፀም  ምንም እንኳን  ግዴታውን   አለመፈፀሙ ሕግን መጣስ ቢሆንም ቁጥር  2ዐ37 ሥር  እንደተደነገገው  አንድ ሰው በአንድ ውል  ምክንያት የመጣበትን  ግዴታ  ሳይፈፅም  በቀረ  ጊዜ የውል አለመፈፀም ደንብ  ብቻ ተፈፃሚ  ይሆንበታል፡፡

  

የበላይ ትዕዛዝ ቁጥር 2ዐ36

 

የበላይ  ትዕዛዝን  አስመልክቶ ሶስት የተለያዩ መነሻዎች  አሉ፡፡ የመጀመሪያው  ሁሌም ሕግን  ብቻ ታዘዝ የሚለው ሲሆን  ይህ ማነሻ  ሁሌም ሰው ሕግን ያውቃል የሚለውን ግምት መሠረት  ያደረገ ነው፡፡ ይህ  መነሻ  በትልቋ ቢሪታኒያ  ተቀባይነት አለው፡፡ ይህ መነሻ  ውይይትን ስለሚጋብዝ  ተግባራዊ መሆኑ /በተለይም በሠራዊቱ ውስጥ/ አጠያያቂ ነው ለማለት ይቻላል፡፡

 

ሁለተኛው  መነሻ ደግሞ ሕግን እርሳው  አለቃህን ብቻ ታዘዝ  የሚል ነው፡፡  ይህ ደግሞ  አለቆች  ሕግን በደንብ ያውቃሉ የሚል ግምትን መሠረት ያደረገ ነው፡፡ /ስለሆነም አለቆች  በሕጉ መሠረት ትዕዛዝ ይሰጣሎ፡፡

 

ይህ መነሻ በሠራዊቱ ውስጥ  ጥሩ ሊሆን ይችላል፡፡  ሆኖም በሁለተኛው የዓለም ጦርነት  ጊዜ   በሰው እና  በንብረት ላይ በደረሰው  ስቃይና ውድመት ይህ  መነሻ ተተችቷል፡፡  ምክንያቱም ወታደሮች  በሰው ልጅ ላይ በዛን ጦርነት ጊዜ የደረሰውን  እለቂትና ግፍ የፈፀምነው ከላይ  ትዕዛዝ ስለተሰጠን ነው፡፡ በማለታቸው ነበር፡፡

 

ሶሰተኛው  መነሻ  ሕጉንም ትዕዛዙንም ታዘዝ  የሚለው ነው፡፡ ይህ መነሻ  ነው ቁጥር 2ዐ36 ሥር  የተንፀባረቀው በዚህ ቁጥር መሠረት በመጀመሪያ  ትዕዛዙን በሚሰጠውና ትዕዛዙን በሚቀበለው  መሃል  የአለቃና  አመንዝራ  ግንኙነት  ሊኖር ይገባል፡፡ ይህም ግንኙነት /Superiority in  authority /  እንጂ  /Superiority in rank/  ላይ  የተመሠረቱ መሆን  የለበትም፡፡  ይህን በምሳሌ  እናስረዳ  በመከላከያ  ሠራዊት  ውስጥ ባለ አንድ  ጀነራልና  በፖሊስ ውስጥ ባለ አንድ ተራ ፖሊስ መሃል ያለ ግንኙነት  / Superiority in rank/ እንጂ /Superiority in authority/ አይደለም፡፡  በዚህ  ምሳሌ መሠረት ጀነራሉ ለፖሊሱ ትዕዝዝ ቢሰጠው ትዕዛዙ  ሕግ ወጥ  ይሆናል ምክንያቱም  ቁጥር 2ዐ36/2/  እንደደነገገው ትዕዛዝ ሰጪው /ጀነራሉ/ ለፖሊሱ ትዕዛዝ የመስጠት ስልጣን ስለሌለው ነው፡፡

  

እንዲሁም አለቃው /Superiority in authority / እንኳን ቢኖረው ትዕዛዙ  የአመፅ ጠባይ ካለው ትዕዛዙ  አሁንም ሕግ ወጥ  ይሆናል፡፡ በተጨማሪም  የሰጠው ትዕዛዝ  አስወቃሽ ማለትም ተጠያቂነትን የሚያስከትል  ከሆነ ትዕዛዙ  ሕገ ወጥ ይሆናል፡፡ 

 

ለማጠቃለል ትዕዛዝ ተቀባዩ  ማለት ምንዝሩ በእሱ እና  ትዕዛዙን  በሰጠው መሃል ያለው ግንኙነት / Superiority in  rank  / እንጂ / Superiority in authority /የሌለ መሆኑን እያወቀ ትዕዛዙን  ተቀብሎ ተግባራዊ ካደረገ ወይም /Superiority in  authority / ቢኖርም  ትዕዛዙ  የአመፅ ጠባይ  ያለው  መሆኑን ወይም  አስወቃሽነቱን  እያወቀ ሰርቶት  እንደሆነ  ትዕዛዙን ፈፃሚው  ጥፋተኛ ይሆናል /2ዐ36 /2/

ቁጥር  2ዐ36 /2/ ትዕዛዙን ለተገበረ ሰው መከላከያ  ይመስላል፡፡  ምክንያቱም  ትዕዛዙን  ፈፃሚው ጥብቅ በሆነ በመንግስታዊ ወይም  በወታደራዊ ዲስኘሊን ምክንያት  በተሰጠው ትዕዛዝ ለመከራከር ወይም ያንን የታዘዘውን እንጂ ሌላ ነገር ለማድረግ  በማይችልበት ሆኔታ ውስጥ ከመገኘት የተነሳ  ከሆነ  ጥፋት የለበትም ስለሚል ነው፡፡

 

ግን ጥፋት ባይኖርበትም  አላፊ ከመሆን ላይድን ይችላላ፡፡ ምክንያቱም  ምንም እንኳን  በአስፈላጊ  ሁኔታ /Under necessity/ ስር ማለት አስገዳጅ  በሆነ ሆኔታ ስር ያን ቢፈፅምም በቁጥር 2ዐ66 /1/ መሠረት አላፊ  ይሆናል፡፡ ምናልባትም  በቁጥር 2ዐ37/1/ መሠረትም አላፊ  ማድረግ ይቻላል፡፡ ግን  አንድን ሰው በአንድ በኩል ጥፋት  የለበትም  በሌላ በኩል ደግሞ  አላፊ  ማድረግ ሰሜት ላይሰጥ ይችላል፡፡ ለደረሰው ጉዳት ሌላ አማራጭ ልንፈልግ ይገባል፡፡  ምናልባት  ትዕዛዝ  ስጪውን በቁጥር 2ዐ35  እና  በወንጀል  ሕግ  መሠረት ተጠያቂ ማድረግ ይቻላል፡፡

 

የውል አለመፈፀም ቁጥር /2ዐ37/

 

አንድ ሰው በገባው ውል መሠረት ግዴታውን አለመፈፀሙ ከውል ውጭ አላፊነት ስር ጥፋተኛ አያስኘውም፡፡  ከሣሽ  ለክሱ መሠረት ማድረግ ያለበት ስለውል አለመፈፀም የሚደነግጉትን   ድንጋግዎች  ነው፡፡ አንዳንድ  ጊዜ  ግን የትኛውን  /ከውል ውጨ  ወይስ የውል/ ድንግጌ ነው ለክሳችን  መነሻ ማድረግ ያለብን የሚለው አስቸጋሪ የሚሆንበት ሁኔታ ያጋጥመናል፡፡

  

ይህን  በምሳሌ  እናስረዳ በቁጥር 2533 መሠረት ሠራተኛው የሥራ ውል ካለቀ በኃላም ቢሆን በሥራው  ጊዜ  ያወቃቸውን የአሰሪውም ምስጢሮች  መጠበቅ እንዳለበት ተደንግጓል፡፡ ሠራተኛው ይህን  ቁጥር ጥሶ  ቢገኝ  ተጠያቂ የሚሆነው  በየትኛው  ሕግ መሠረት ነው፡፡ በውሉ መሠረት ነው፡፡  እንዳንል ውል  ተቋርጧል፡፡ ቁጥር 2ዐ35 ትን  እንዳንጠቀም ደግሞ ቁጥር 2ዐ37 ይከለክለናል፡፡ ምናልባት ቀጥሉ ባለው መንገድ  መከራከር እንችላለን፡፡ ውል ቢቋረጥም  ሕግ ግን  ሠራተኛው  የአሰሪውን ሚሰጢር እንዳያወጣ ግዴታ ጥሎበታል፡፡ ስለሆነም ሠራተኛው  ሚስጥሩን  ቢያወጣ  ግልፅ  የሆነን  ሕግ አንደጣሰ  ተቆጥሮ  በቁጥር  2ዐ35  መሠረት ተጠያቂ  ልናደርገው እንችላለን፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ  ምንም እንኳን  በአጠቃላይ  ውል ቢቋረጥም  ምስጢር ያለማውጣት ግዲታ ግን ይቆያል / Persist/ ስለሆነም ሚስጢር ሲያወጣ ያለማድረግ ግዴታን  / Obligation not to do/ እንደጣሰ  ተቆጥሮ  በውል ሕግ ቁጥር መሠረት  ተጠያቂ ልናደርግው  እንችላለን፡፡ 

  • Administrative Law (30)
  • African Human Rights Law (18)
  • African Union Law (6)
  • Alternative Dispute Resolution (33)
  • Agency (6)
  • Bankruptcy Law (4)
  • Civil Procedure (12)
  • Conflict Laws (3)
  • Constitutional Law (5)
  • Construction Law (3)
  • Contract Law (7)
  • Criminal Law (10)
  • Criminal Procedure (6)
  • Criminology (4)
  • Customary Law (4)
  • Employment and Labor Law (17)
  • Environmental Law (5)
  • Evidence Law (6)
  • Family Law (5)
  • Gender and the law (4)
  • Human Right Law (5)
  • Humanitarian Law (7)
  • Insurance, Banking and Negotiable Instrument Law (6)
  • Intellectual Property Law (4)
  • International Organizations (4)
  • Introduction to law and Law of Persons (4)
  • Investment Law (10)
  • Islamic Law (2)
  • Judgment writing (0)
  • Jurisprudence (1)
  • Land Law (10)
  • Law and Development (0)
  • Legal History (0)
  • Legal Profession (0)
  • Legal Research Methods (0)
  • Legal Writing (0)
  • Legislative Drafting (0)
  • Maritime Law (3)
  • Non-Contractual Liability (Tort Law) (10)
  • Pre-Trial Skills and Trial Advocacy (0)
  • Property Law (27)
  • Public Enterprises and Cooperatives (0)
  • Public International Law (0)
  • Refugee Law (0)
  • Sales and Security Devices (0)
  • Sentencing and Execution (4)
  • Succession Law (6)
  • Taxation Law (4)
  • Trade and Business Organizations (2)
  • Administrative Contract (16)
  • Federalism (3)
Copyright © 2025 Abyssinia Law | Making Law Accessible! . All Rights Reserved.
Maintained by Liku Worku Legal Services!
Learn More ×