- Details
- Category: General - ልዩ ልዩ
እናንት ዳኞች የበየናችሁብኝን የሞት ፍርድ ያለይግባኝ ተቀብያለሁ፡፡ ይግባኝ ብዬ ጉዳዬን የሚመለከትልኝ የኢትዮጵያ ሕዝብ ቢሆን ኖሮ ይግባኝ ማለት በፈለግሁ ነበር፡፡ ነገር ግን ይህ እንደማይሆን አውቃለውና በይግባኝ የአፄ ኃ/ስላሴን ፊት ማየት አልፈቅድም፡፡
በእግዚያብሔር ስም ተሰይማችሁ ከተቀመጣችሁበት የፍርድ ወንበር ላይ ከመቀመጣችሁ በፊት በእኔ ላይ የምትሰጡትን የዛሬውን ፍርድ ታውቁት እንደነበር ሳስብና ፍርድ እስከዚህ መርከሱን ስታዘብ ሀዘኔ ይበዛል፡፡
እኔ የተነሳሁት ከትክክለኛ ሕግና ከህሊናችሁ ውጭ ለመፍረድ እንዳትገደዱ ለማድረግ ነበር፡፡ በአጭሩ በእኔ ላይ ለመፍረድ የቸኮላችሁትን ያህል አስር እና አስራ አምሰት ዓመት በቀጠሮ የምታጎላሉትን ሕዝብ ጉዳይ እንደዚህ አፋጥናችሁ ብትመለከቱትና ብትሸኙት ኖሮ የእኔ መነሳት ባላስፈለገም ነበር፡፡
ለኢትዮጵያ ሕዝብ አንድነት፣ ነፃነትና ርምጃ የተነሳሁ ወዳጅ ነኝ እንጂ ለማፋጀት የተነሳሁ ወንበዴ አይደለሁም፡፡ ይህንን ማድረግ ፈልጌ ቢሆን ኖሮ ማንም የማይወዳደረው ሰራዊትና መሣሪያ ሳላጣ ዛሬ እዚህ ከእናንተ ፊት ለመቆም ባልበቃሁ ነበር፡፡
እኔ ከኃ/ስላሴ ድንክ ውሾች ያነሰ ደመወዝ የሚያገኙ ሁለት የተራቡ ወታደሮችን አጣልቼ ለማደባደብና አገር ለማፍረስ አለመምጣቴን የሚያረጋግጥልኝ እናንተ በትዕዛዝ ያገኛችሁትን ፍርድ ለመቀበል እዚህ መቆሜ ነው፡፡
ከእኔ በፊት በግፍ የፈሰሰው ንፁህ የኢትዮጵያዊያን ደም ብዙ ነው፡፡ በየአፄ ኃ/ስላሴ ዘመነ መንግስት ግፍ ሽልማት በመሆኑ እኔ ለመሞት የመጀመሪያው ሰው አልሆንም፡፡ ሥልጣን አላፊ ነው፡፡ እናንተ ዛሬ ከጨበጣችሁት የበለጠ ስልጣን ነበረኝ፡፡ ሀብትም አላጣሁም፡፡ ነገር ግን ሕዝብ የሚበደልበት ሥልጣንና ድሃ የማይካፈለው ኃብት ስላልፈለግሁ ሁሉንም ንቄ ተነሳሁ፡፡ አሁንም እሞታለሁ፡፡ ሰው ሞትን ይሸሻል፡፡ እኔ ግን በደስታ ወደሞት እሄዳለሁ፡፡
ለኢትዮጵያ ኽዝብ ታላቅነት ቀድመውኝ መስዋዕት የሆኑትን አብረውኝ ተነስተው የነበሩትን ጀግኖች ወንድሞቼን ለመገናኝት ናፍቄአለሁ፡፡ የጀመርኩት ሥራ ቀላል አይደለም፡፡ አልተሸነፍኩም፡፡ ወገኔ የሆነው ድሃው የኢትዮጵያ ሕዝብ የጀመርኩለትን ሥራ በቅርብ ጊዜ ውስጥ ፈፅሞ ራሱን በራሱ እንደሚጠቅም አልጠራጠርም፡፡
ከሁሉ በበለጠ የሚያስደስተኝ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ልሰራለት ካሰብኳቸው ስራዎች አንዱ የኢትዮጵያ ወታደር ዋጋና ክብር ከፍ ማድረግ ሲሆን ይህ ሃሳቤ ህይወቴ ከማለፉ በፊት ሲፈፀም ማየቴ ነው፡፡
ዛሬ መኖራችሁን በማየቴ ነገ መሞታችሁን ረስታችሁ አሜን ብላችሁ ቀናችሁን በማስተላለፍ በመገደዳችሁ በእኔ ላይ ሳትፈርዱ በራሳችሁ ላይ የፈረዳችሁ መሆናችሁን አላስተዋላችሁም፡፡
እኔ የተነሳሁት ከትክክለኛ ሕግና ከህሊናችሁ ውጭ ለመፍረድ እንዳትገደዱ ለማድረግ ነበር፡፡ በአጭሩ በእኔ ላይ ለመፍረድ የቸኮላችሁትን ያህል አስር እና አስራ አምሰት ዓመት በቀጠሮ የምታጎላሉትን ሕዝብ ጉዳይ እንደዚህ አፋጥናችሁ ብትመለከቱትና ብትሸኙት ኖሮ የእኔ መነሳት ባላስፈለገም ነበር፡፡
ከእናንተ ከዳኞቹና የሞት ፍርድ እንድትበይኑብኝ ካዘዛችሁ ሰው ይልቅ እኔ ፍርድ ተቀባይ የዛሬ ወንጀለኛ የነገ ባለታሪክ ነኝ፡፡
የኔ ከጓደኞቸ መካከል ለጊዜው በህይወት መቆየትና ለእናንተ ፍርድ መብቃት የመመዘኑን ፍርድ ለመጭው ትውልድ የሚያሳይ ይሆናል፡፡
ዋ ! ዋ ! ዋ ! ለእናንተና ለገዢአችሁ፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ሃሳቤ በዝርዝር ገብቶት በአንድነት በሚነሳበት ጊዜ የሚወርድባችሁ መዓት አሰቃቂ ይሆናል፡፡ በተለይ የአፄ ኃ/ስላሴ የግፍ መንግስት ባላደራዎች ሆነው ድሀውን የኢትዮጵያ ህዝብ ሲገሸልጡት ከነበሩት መኮንን ሀ/ወልድና ገ/ወልድ እንግዳወርቅን ከመሳሰሉት በመንፈስ የታሰሩ በስጋ የኮሰሱ መዠገሮች መካከል ጥቂቶቹን ገለል ማድረጌን ሳስታውስና የተረፉትም ፍፃሜያቸውን በሚበድሉት በኢትዮጵያ ህዝብ እጅ ላይ መውደቅ ሲሰማኝ ደስ ይለኛል፡፡
መንግስቱ ንዋይ : መጋቢት 19 ፣ 1953 ዓ.ም
- Abyssinia Law | Making Law Accessible! By
- Hits: 18241
- Details
- Category: General - ልዩ ልዩ
- ሕገ መንግሥታዊ መሰረት
- የመገናኛ ብዙሃን ነፃነት
- የዋና አዘጋጅ ኃላፊነት
- በመገናኛ ብዙሃን አማካኝነት ለሚፈፀሙ ወንጀሎች የኃላፊነት ቅደም ተከተል
እንዴት ናችሁ ሰላም ነው? በዛሬው ፅሁፋችን የምናነሳው ስለመገናኛ ብዙሃንና የመረጃ ነፃነት አዋጅ ቁጥር 540/2000 እና ሌሎች ተያያዥነት ያላቸውን ሕጎች ምን እንደሚሉ እንመለከታለን።
ሕገ መንግሥታዊ መሠረት
ሕገ መንግሥታችን በአንቀጽ 29 ሥር ካረጋገጣቸው ነፃነቶች አንዱ ያለማንም ጣልቃ ገብነት ሃሳብን የመግለፅ ነፃነት ነው። ይህ ነፃነት በሀገር ውስጥም ሆነ ከሀገር ውጭ ወሰን ሳይደረግበት በቃልም ሆነ በጽሑፍ ወይም በኅትመት በሥነ ጥበብ መልክ ወይም በመረጠው በማንኛውም የማሰራጫ ዘዴ ማንኛውንም ዓይነት መረጃና ሃሳብ የመሰብሰብ የመቀበልና የማሰራጨት ነፃነቶችን ያካትታል። በተጨማሪ ይህን ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ ሕገ መንግሥታዊ መብት ለማረጋገጥ በአንቀጽ 29(3) ስር የፕሬስና የመገናኛ ብዙኃን እንዲሁም የሥነ ጥበብ ፈጠራ ነፃነት መረጋገጡን ይደነግጋል። በተለይ የፕሬስ ነፃነትን በተመለከተ
- በማንኛውም መልኩ ቅድመ ምርመራ ክልክሏል፣
- የሕዝብን ጥቅም የሚመለከት መረጃ የማግኘት እድል የፕሬስ ተቋሙ እንደሚኖራቸው ማረጋገጫ ሰጥቷል።
ሆኖም ግን ይህ መብት ፍፁም አይደለም። ይሄን በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 29(6) ስር ሌሎች መብቶችንና ጥቅሞችን ለመጠበቅ ሲባል ገደብ ሊጣልበት ይችላል። ሆኖም ግን ገደቦቹ ሊጣሉ የሚገቡት የሃሳብና መረጃ የማግኘት ነፃነት በአስተሳሰባዊ ይዘቱና ሊያስከትለው በሚችለው አስተሳሰባዊ ውጤት ሊገታ አይገባውም በሚል መርህ ላይ ተመስርተው በሚወጡ ሕጎች ብቻ መሆኑን ያሰምርበታል። በተጨማሪ የወጣቶችን ደህንነት ለመጠበቅ የሰውን መልካም ስም እና ክብር ለመጠበቅ ሲባል እነዚህ ነፃነቶች በህግ ሊገደቡ እንደሚችሉ ሕገ መንግስቱ ያስቀመጠ ሲሆን የጦርነት ቅስቀሳዎችና ሰብዓዊ ክብርን የሚነካ የአደባባይ መግለጫዎች በሕግ የሚከለከሉ መሆናቸውንና እነኚህን ሕጎች ጥሶ የተገኘ የተቀመጡትን ገደቦች የተላለፈ ማንኛውም ዜጋ በሕግ ተጠያቂ እንደሚሆን ተደንግጓል።
ይህን ሕገ መንግሥታዊ አንቀጽ መሠረት በማድረግ ወደወጣውና በስራ ላይ ያለውን ሕግ እንመልከት።
በአዋጁ ቁጥር 590/2000 አንቀጽ አራት ላይ በሕገ መንግሥታችን ለመገናኛ ብዙሃን የተሰጠውን እውቅና በማስተጋባትና ቅድመ ምርመራ በማንኛውም መልኩ መከልከሉን በድጋሚ በመደንገግ ይጀምራል። በአንቀጽ 4(3) ላይ ደግሞ መገናኛ ብዙሃን ስራቸውን በሚያካሂዱበት ጊዜ ከተለያዩ የመንግስት አካላት መረጃ በመንፈግ ወይም መረጃ እንዳያገኙ እንቅፋት በመሆን ሊያሳድሩባቸው የሚችሉትን ተፅዕኖ ለመከላከል
- ዜና ወይም መረጃን የመሰብሰብ የመቀበልና የማሰራጨት፣
- በልዩ ልዩ ጉዳዮች ላይ አስተያየት ወይም ትችት የማቅረብ፣
- የተለያዩ ሌሎች ዘዴዎችን በመጠቀም የሕዝብን አስተያየት የመቅረፅ ሂደት የመሳተፍ መብታቸውን ማክበር እንደሚኖርባቸው ደንግጓል። ይህ የመገናኛ ብዙሃን ነፃነት ሊገደብ የሚችለው በግልፅ በሕገ መንግሥቱና በመገናኛ ብዙሃን አዋጁ አንቀጽ 4(2) በሚወጡ ሕጎች ብቻ ነው።
የማሳተምና የመደራጀት መብት
የመገናኛ ብዙሃን እና የመረጃ ነፃነት አዋጅ በአንቀጽ 5 ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዜግነት ያለው ሰው በመገናኛ ብዙሃን ስራ የመሰማራት መብት እንዳለው ይደነግጋል። ይህ መብት የተሰጠው ለግለሰቦቹ ሳይሆን በአዋጁ አንቀጽ 7(6) መሠረት በሀገራችን ሕግ መሠረት እውቅና ለተሰጣቸው ተቋማት ወይም ድርጅቶች ብቻ ነው። እነዚህ ድርጅቶችም ቢሆኑ ኢትዮጵያዊ ኩባንያዎች መሆን አለባቸው ይህም ማለት
- የኩባንያው የካፒታል ምንጭ ሙሉ በሙሉ ከሀገር ውስጥ የሆነ እና
- የአክስዮን ባለድርሻዎች በሙሉ ኢትዮጵያውያን የሆኑበት ማለት ሲሆን
የሀገር ውስጥ ማህበር ለመባል ደግሞ በበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ሕግ መሠረት እንደ አገር በቀል ማህበር የተመዘገበ ማህበር ነው።
በሌላ በኩል ደግሞ የመገናኛ ብዙሃን በአንድ ዓላማ ወይም አደረጃጀት ባለው ተቋም ውስጥ ውጤታማ ተፅዕኖ ያለው ሰው በተመሳሳይ ቋንቋ በሚታተምና በተደራራቢ ገበያ የሚሰራጭ የህትመት ሥራን ከሚሰራ ሌላ ኩባንያ ካፒታል ወይም አክስዮን ላይ ውጤታማ ቁጥጥር እንዳይኖረው በአዋጁ አንቀጽ 7(3) ላይ የተደነገገ ሲሆን ውጤታማ ቁጥጥር የሚለካበት ሕግ እስኪወጣ ድረስ ውጤታማ ቁጥጥር የሚባለው በማንኛውም ኩባንያ ወይም ድርጅት አክስዮኖች ወይም ካፒታል በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ 15 ከመቶ በላይ ድርሻ ያለው ሰው ነው።
በአዋጁ የትርጓሜ ክፍል የመገናኛ ብዙሃን ማለት በየጊዜው የሚወጡ የህትመቶች እና ብሮድካስቶችን የሚያካትት መሆኑን ይገልጻል። የህትመት ሥራን ሲተረጉም ደግሞ የመገናኛ ብዙሃንንና በህዝብ እንዲደርሱ ታስበው የሚሰራጩ የሙዚቃ ስራዎችን፣ የአዲዮቪዥዋል ሥራዎችን፣ ስዕሎችን፣ ተውኔቶችን፣ ካርቱኖችን መፅሐፍትን፣ በራሪ ፅሁፎችን፣ ፊልሞችን፣ ፖስተሮችን የንግድ ማስታወቂያዎችን፣ ዜና አገልግሎትንና ማንኛውም አይነት ሌሎች ህትመቶችን የሚያካትት በመሆኑ ከተለመዱት ጋዜጣ መፅሄቶች መፅሐፍት በተጨማሪ በርካታ ሃሳብን የመግለጫና መረጃ የማስተላለፊያ መንገዶችን እንደሚያካትት መረዳት ይቻላል።
በየጊዜው የሚወጡ ህትመት የሚባለው ደግሞ አንድ ቋሚ ስያሜ በመያዝ በተወሰነ የጊዜ ክፍተት ሳይቋረጥ በተከታታይ እንዲወጣ ታስቦ ቢያንስ በዓመት ሁለት ጊዜ የሚታተም አጠቃላይ ስርጭት ያለውና በጠቅላላው ህብረተሰብ ወይም በአንድ በተወሰነ የህዝብ ክፍል እንዲነበብ ታስቦ የሚሰራጭ ጋዜጦችን እና መፅሔቶችን የሚያካትት የህትመት ሥራ መሆኑን አዋጁ አንቀጽ 2(3) ይደነግጋል።
በመገናኛ ብዙሃን ስራ ውስጥ ዋና አዘጋጅ ትልቁን ሚና የሚጫወትና ሙሉ ኃላፊነት የኤዲቶሪያል ስልጣን ያለው ሰው ነው። በአዋጁ አንቀጽ 6 ላይ በዋና አዘጋጅነት የሚሾም ሰው በስሩ የሚታተሙትን ህትመቶች ይዘት የመቆጣጠርና ማንኛውንም ነገር ያለ ፈቃድ እንዳይታተም የማድረግ ስልጣን ተሰጥቶታል። ይህን ስልጣኑን የሚገድብ ማንኛውም አይነት አሰራር ወይም ስምምነት በሕግ ፊት ፈራሽ ነው።
ይህን ስልጣኑን ተግባራዊ ለማድረግ ዋና አዘጋጁ ሙሉ የሕግ ችሎታ ያለው ሊሆን ይገባል። ይህም ማለት እድሜው ለአካለ መጠን የደረሰ በአእምሮ ወይም በአካል ጉዳት በፍ/ቤት ያልተከለከለ ወይም በተጣለበት የወንጀል ቅጣት ከመብቶቹ ያልተሻረ መሆን አለበት።
የመገናኛ ብዙሃን አዋጁ ለዋና አዘጋጁ ስልጣን ብቻ ሳይሆን ኃላፊነትም ሰጥቶታል። በመሆኑም ለመገናኛ ብዙሃኑ ውጤት ይዘቶች ሙሉ የሕግ ተጠያቂነት አለበት።
በአዋጁ አንቀጽ 2(12) አሳታሚ ማለት የመገናኛ ብዙሃኑን የሚወክል ወይም የመገናኛ ብዙሃኑ ባለቤት የሆነ፣ በድርጅቱ ውስጥ የጎላ የባለንብረትነት ጥቅም ያለው ወይም የድርጅቱን የሥራ አስተዳደር የሚመራ ማንኛውም ሰው ሲሆን አታሚ የሚባለው ደግሞ የህትመት ሥራውን ለማተም ከአሳታሚው ጋር የተዋዋሉ ማተሚያ ቤቶችን የሚመለከት ነው።
አዋጁ አከፋፋይ እና አስመጪ የሚባሉትን በመገናኛ ብዙሃን ስርጭት ውስጥ ትልቅ ድርሻ ያላቸውን አካላትም ትርጓሜ ተሰጥቷቸዋል። አከፋፋይ የህትመት ስራን በጅምላ ለማከፋፈል በአሳታሚው የተሾመ ወይም የተዋዋለ ሰው ነው። አስመጪ ደግሞ የመገናኛ ብዙሃንን በሀገር ውስጥ ለማሰራጨት በማሰብ ወደ ሀገር የሚያስገባ ወይም በሀገር ውስጥ የሚያሰራጩ የውጭ ህትመቶች ወኪል የሆነ ማንኛውም ሰው ነው።
በመገናኛ ብዙሃን የሚፈፀም ኃላፊነት የሚያስከትል ድርጊትን በተመለከተ በወንጀል ሕጋችን አንቀጽ 43 ላይ በቅደም ተከተል ያስቀመጠ ሲሆን በመጀመሪያ ደረጃ ተጠያቂነቱ የፕሬስ ውጤቱ ሲታተም በዋና አዘጋጅነት ወይም በምክትል አዘጋጅነት የተመዘገበ ሰው ለወንጀሉ ኃላፊ ሲሆን ዋና አዘጋጁ፤ ዋና አዘጋጅ ለመሆን የሚያበቃ ሁኔታዎችን ካላሟላ ወይም በዋና አዘጋጅነት መስራቱን ካቆመ የፕሬሱ አሳታሚ ኃላፊ ይሆናል። አሳታሚው ካልታወቀ አታሚው፣ አታሚውም ሊታወቅ ካልቻለ የፕሬስ ውጤቱ ያሰራጨው ሰው የወንጀል ኃላፊነት እንደሚኖርበት ይደነግጋል።
- ኪዳኔ መካሻ By
- Hits: 16529
- Details
- Category: General - ልዩ ልዩ
‹‹ይሄ የማይታመን ነው፡፡ ዛሬ ለስድስተኛ ጊዜ ዳኛው ውሳኔ ለመስጠት ቀጠሩኝ፡፡ ከጠዋት 3፡00 እስከ 6፡30 ተቀምጬ እጠባበቃለሁ፡፡ የያዝኩት ጉዳይ ሲጣራ ዳኛው ጉዳዩ ውስብስብ ስለሆነ አይተው እንዳልጨረሱ ይነግሩኛል፡፡
የጉዳዮች ብዛትና የዳኞች ቁጥር እንደማይመጣጠን አሳምሬ አውቃለሁ፡፡ ነገር ግን ምንም ላልተሠራ ነገር ደንበኛዬና ወዳጅ ዘመዶች በዚህ የትራንስፖርት ችግር በሌሊት ከቤት ወጥተውና ሥራ ፈተው እዚህ መቀመጣቸው በጣም የሚያሳዝን ነው፡፡ ፍትሕ ለማግኘት እምነት ቋጥረው ቢመጡም፣ በየቀኑ መሠረታዊ የመብት ጥሰት እየተፈጸመባቸው ነው፡፡››
ልደታ በሚገኘው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሪፖርተር ዘጋቢ በቅርቡ ለሥራ በሄደበት ወቅት ያገኛቸው ጠበቃ የነገሩት ቅሬታ ነበር፡፡ ፍትሕ የማግኘት መብት ወይም የፍትሕ ተደራሽነት ላይ ቅሬታ ያላቸው ጠበቆች ብቻ አይደሉም፡፡ በሒደቱ ቀጥተኛ ተሳታፊ የሆኑት ፖሊሶች፣ ዓቃቤ ሕጎች፣ ራሳቸው ዳኞችና የማረሚያ ቤት መኮንኖችን ጨምሮ ተገልጋዩ ማኅበረሰብ ፍትሕ የማግኘት መብት አፈጻጸም መሠረታዊ ችግሮች እንዳሉበት ይገልጻሉ፡፡ የመንግሥት ይፋዊ ሪፖርቶችም ችግሩን ለመቅረፍ የተደረጉ ዘርፈ ብዙ ጥረቶች ላይ ቢያተኩሩም፣ ችግሩ አሁንም ጥልቀት እንዳለው ግን ይቀበላሉ፡፡ ነገር ግን የችግሩ ምንጭና ምክንያት ላይ ሁሉም አካላት ተመሳሳይ ጉዳዮችን አይጠቅሱም፡፡
ይህ መሠረታዊ ልዩነት የኢትዮጵያ የሕግ ባለሙያዎች ማኅበር በኢትዮጵያ መንግሥትና የአውሮፓ ኅብረት ሲቪል ሶሳይቲ ፈንድ II በተደረገ የገንዘብ ድጋፍ ‹‹ፍትሕ የማግኘት መብት››ን አስመልክቶ ያዘጋጀው የግማሽ ቀን የፓናል ውይይት፣ ጥቅምት 12 ቀን 2007 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ቸርችል ሆቴል በተዘጋጀበት ወቅት በስፋት ተንፀባርቋል፡፡ ጠበቆች፣ የዩኒቨርሲቲ መምህራን፣ የመንግሥት ተወካዮች፣ የሲቪል ማኅበራት ተወካዮችና ሌሎች ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት በተሳተፉበት በዚህ ውይይት፣ የፍትሕ ተደራሽነትን ከሚያስፋፉት ይልቅ የሚገድቡት ጉዳዮች የገዘፉ ስለመሆናቸው ተነግሯል፡፡
ፍትሕ የማግኘት መብት ይዞታ በኢትዮጵያ
በፓናል ውይይቱ ላይ ፍትሕ የማግኘት መብት በዓለም አቀፍ ስምምነቶችና በኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት ያለውን ገጽታ አስመልክቶ የጥናት ጽሑፍ ያቀረቡት አቶ ደበበ ኃይለ ገብርኤል ጠበቃና የሕግ አማካሪ ሲሆኑ፣ ቀደም ብሎ ዳኛና አክሽን ፕሮፌሽናል አሶሴሽን ፎር ፒፕል የተሰኘ አገር በቀል ሲቪል ማኅበር ዋና ሥራ አስፈጻሚ በመሆንም አገልግለዋል፡፡ አቶ ደበበ ፍትሕ የማግኘት መብትን ዜጎች ወይም በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ የሚገኙ የኅብረተሰብ ክፍሎች ፍትሕ ለማግኘት የሚጠይቁበት፣ ምክንያታዊ በሆነ ጊዜ ውስጥ መፍትሔ የሚያገኙበት ሥርዓት ነው ሲሉ ይተረጉሙታል፡፡ ይህ መብት ሦስት አንኳር ክፍሎችን እንደሚያቅፍ ይጠቅሳሉ፡፡ እነዚህም ፍትሕ የመጠየቅ ችሎታ፣ የተጠየቀውን ፍትሕ የማግኘት ዕድልና በምን ያህል ጊዜ ፍትሕ ይገኛል የሚሉት ጉዳዮች ናቸው፡፡
ፍትሕ የማግኘት መብት ሦስት መሠረታዊ ባህርያት እንዳሉትም አቶ ደበበ ያስረዳሉ፡፡ እነዚህም በዓለም አቀፍ ሰብዓዊ መብት ስምምነቶችና በኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት ዕውቅና የተሰጠው ሰብዓዊ መብት መሆኑ፣ ሌሎችን መብቶች ለማስከበር መሣሪያ ሆኖ ማገልገሉና እንደ በሕግ ፊት እኩል ሆኖ የመታየት መብት ካሉ ተያያዥ መርሆዎች ተነጥሎ ለብቻው የሚቆም አለመሆኑ ናቸው፡፡
አቶ ደበበ ኢትዮጵያ ያፀደቀቻቸው ዓለም አቀፍ ስምምነቶችና ሕገ መንግሥቷ ፍትሕ የማግኘት መብትን በአግባቡ መያዛቸውን ያስገነዝባሉ፡፡ ኢትዮጵያ ከፍትሕ የማግኘት መብት ጋር የተቆራኙ መርሆዎችን መቀበሏን ያመላክታሉ፡፡ ከእነዚህ መርሆዎች መካከልም ቁልፍ የሚባሉት በሕገ መንግሥቱና በሕግ የተሰጠን መብት ለማስከበር መንግሥት የገባው ኃላፊነት፣ ብቃት ያለው፣ በሕግ የተቋቋመ ነፃና ገለልተኛ ፍርድ ቤት በመጠቀም ግልጽና ፍትኃዊ የፍርድ ሒደት ማደራጀት፣ አቅም ለሌላቸው ሰዎች የሕግ ዕርዳታ መስጠትና ተነፃፃሪ በሆነ አቅም ላይ ተከራካሪዎችን ማስቀመጥ (Equality of arms) በኢትዮጵያ ሕጎች ቦታ እንደተሰጣቸው አቶ ደበበ ያስረዳሉ፡፡
በሕጎቹ አማካይነት ኢትዮጵያ እነዚህን መርሆዎች ብትቀበልም፣ አፈጻጸማቸውን ለማሳለጥ ተቋማት ብታደራጅም፣ ሥነ ሥርዓትና አሠራሮችን ብትቀርፅም ፍትሕ የማግኘት መብትን በአግባቡ ለመፈጸም በርካታ ጋሬጣዎች ወይም መሰናክሎች እንዳሉ ግን አቶ ደበበ ይጠቁማሉ፡፡ የፍትሕ ተደራሽነትን ከሚያውኩ ዋና ዋና ጋሬጣዎች መካከል አቶ ደበበ ማኅበራዊና ባህላዊ፣ የሕግና የአስተዳደር፣ በፍትሕ ሒደቱ ውስጥ ያሉ መዋቅራዊ ችግሮችና በቂ የሆነ የሕግ ዕርዳታ ያለመኖርን ይጠቅሳሉ፡፡ ዜጎች በፍትሕ ሥርዓቱ ላይ ያላቸው እምነት ዝቅተኛ መሆን እንዲሁም በተከራካሪ ወገኖች የበቀል ዕርምጃ ሊወስድብኝ ይችላል ብሎ መፍራት፣ ከማኅበራዊና ከባህላዊ ጋሬጣዎች መካከልም እንደሚመደብም አስገንዝበዋል፡፡ እንደ ምሳሌም በሃይማኖትና በብሔር ልዩነት የተነሳ ዜጎች ፍትሕ ላላገኝ እችላለሁ ብለው ማሰባቸውን ጠቅሰዋል፡፡
የፌዴራል ፍትሕ ተቋማት በፍትሕ ሚኒስቴር መሪነት በ2006 ዓ.ም. ያወጡት የጋራ ሪፖርት ከ2003 ዓ.ም. ጀምሮ ያላቸውን አፈጻጸሞች ይዳስሳል፡፡ በዚህም የሰው ኃይል ብቃትን በማጎልበት፣ የፍትሕ ዘርፍን አመራር ውጤታማነት በማሳደግ፣ የፍትሕ ዘርፍን አሠራር ቅልጥፍና በማሳደግ፣ የፍትሕ ሥርዓቱን የግልጽነትና የተጠያቂነት አሠራርን በማሻሻል፣ የአገልግሎት ተደራሽነትን በማሳደግ፣ በፍትሕ ሥርዓቱ የዜጎችን ተሳትፎ በማሳደግና ሥርዓቱን በኢንፎርሜሽን ኮሙዩኒኬሽን በመደገፍ የመጡትን መሠረታዊ ለውጦች ይዘረዝራል፡፡
ይሁንና የፍትሕ ዘርፉ በአመራርም ሆነ በፈጻሚው ዘንድ የለውጥ ሥራውን በመምራትና በማስፈጸም ረገድ ከግንዛቤ ጀምሮ የአስተሳሰብ፣ የክህሎትና የግብዓት ችግሮች በሰፊው እንደሚስተዋሉበትና የሰው ኃይል እጥረትና ፍልሰት የተቋማቱ የወል ችግር እንደሆነ ሪፖርቱ ያመለክታል፡፡ ለበርካታ ዓመታት ሲካሄድ የነበረው የፍትሕ ሥርዓት ማሻሻያም ሆነ የፍርድ ቤቶች ማሻሻያ ፕሮግራም በሚፈለገው መንገድ ተፈጻሚ እንዳልሆነም ሪፖርቱ ይጠቁማል፡፡ ቀላል የማይባል ባለሙያና አመራር በሙስና ተግባር ተሠማርቶ የሚገኝ መሆኑንም ሪፖርቱ ያመለክታል፡፡
በጥቅምት ወር 2006 ዓ.ም. ተግባራዊ መደረግ የጀመረው ብሔራዊ የሰብዓዊ መብት የድርጊት መርሐ ግብር እነዚህን ችግሮች ከሞላ ጎደል የተቀበለ ሲሆን፣ ፍትሕ የማግኘት መብትን ከማረጋገጥ አኳያ የሚከናወኑ ተግባራትን ያስቀምጣል፡፡ እነዚህም ዕቅዶች በዋነኛነት መርሐ ግብሩ ከለያቸው ችግሮችና ተግዳሮቶች የተነሱ ናቸው፡፡ ፍርድ ቤቶች በበቂ ሁኔታ የተደራጁ ባለመሆኑ የፍርድ ቤቶች ተደራሽነት አጥጋቢ አለመሆኑ፣ የሰበር ሰሚ ችሎት ውሳኔዎች የሚሠራጩበት ውጤታማ ሥርዓት አለመዘርጋቱ፣ የተከላካይ ጠበቆች ጽሕፈት ቤቶች በወረዳ ደረጃ ያልተቋቋሙ መሆኑና በከፍተኛ ፍርድ ቤቶች ደረጃም በበቂ ሁኔታ የማይገኙ መሆኑ፣ በተለያዩ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት የሚሰጡ የነፃ የሕግ ድጋፍ አገልግሎቶች በተቀናጀ መልኩ የሚከናወን አለመሆኑና የኅብረተሰቡን የሕግ ግንዛቤ ለማሳደግ የመገናኛ ብዙኃንንና ሌሎች ዘዴዎችን በመጠቀም በሰፊው አለመሥራቱ፣ ከተጠቀሱት ችግሮችና ተግዳሮቶች መካከል ይገኛሉ፡፡
መንግሥት እነዚህን ችግሮች ለመቅረፍ ጥናቶች እንደሚያከናውን፣ ተጨማሪ ምድብ ችሎቶችን እንደሚከፍት፣ ተጨማሪ አካላት እንደሚያቋቁም፣ አቅም ለማሳደግ ሥልጠናዎች እንደሚሰጥ፣ የተከላካይ ጠበቆች ተጨማሪ ቅጥር እንደሚያከናውን፣ አዳዲስና ነባር ሕጎች ለኅብረተሰቡ ተደራሽ ይሆኑ ዘንድ የሽያጭ ጣቢያዎች እንዲስፋፉ እንደሚያደርግ፣ ሕጎችን ወደ ተለያዩ የአገሪቱ ቋንቋዎች የመተርጎም፣ የማጠናከርና የማሠራጨት ሥራዎች አጠናክሮ እንደሚቀጥል፣ በቪዲዮ ኮንፈረንስ የሚደረግ የችሎት ሥርዓት (e-litigation) በሁሉም ክልሎች ጥራቱን በጠበቀ ሁኔታ እንዲስፋፋ ለማድረግ ጥረት እንደሚያደርግ፣ ነፃ የሕግ ድጋፍ አገልግሎቶችን የሚያቀናጅ ብሔራዊ የነፃ የሕግ ድጋፍ አገልግሎት ስትራቴጂ አዘጋጅቶ ተግባራዊ እንደሚያደርግና አለመግባባቶችን በሕግ የሚፈታና በፍትሕ ሥርዓቱ ላይ እምነት ያለው ኅብረተሰብ ለመፍጠር የሚያስችሉ ሥራዎች እንደሚያከናውን ዘርዝሯል፡፡
የድርጊት መርሐ ግብሩ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ይበቃል ግዛው፣ ባለፉት ወራት አብዛኛውን ዕቅድ ለመፈጸም መንግሥት መንቀሳቀሱን ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ ይሁንና የተከናወኑት ተግባራት ያለውን ችግር ለመቅረፍ በቂ አለመሆናቸውን አመልክተዋል፡፡ በተያዘው ዓመት ቀሪ ሥራዎችን አጠናክሮ ለመቀጠል እየተሠራ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡
ፍትኃዊ ሕግ የማግኘት መብት
በፓናል ውይይቱ ላይ በኢትዮጵያ ስላለው ፍትሕ የማግኘት መብት አፈጻጸም ጥናታዊ ጽሑፍ ያቀረቡት አቶ ፊሊፖስ አይናለም ጠበቃና የሕግ አማካሪ እንዲሁም አስተማሪ ናቸው፡፡ አቶ ፊሊፖስ ፍትሕ የማግኘት መብት ጥሩ ወይም ፍትኃዊ ሕግ የማግኘት መብትን እንደሚጨምር ተከራክረዋል፡፡
አቶ ፊሊፖስ ፍትኃዊ ሕግ ፍትሕ ለመስጠት ተስማሚ የሆነ ሕግ እንደሆነም አመልክተዋል፡፡ መለያ ባህርያቱን በተመለከተ ሲያብራሩም ለሞራል የሚስማማ፣ ተፈጻሚነት ያለው፣ የአገሪቱን ነባራዊ ሁኔታ ያገናዘበ፣ ምክንያታዊ የሆነ፣ ደረጃውን የጠበቀ፣ ዘለቄታዊነት ያለው፣ ለወንጀል ጥፋት ተመጣጣኝ ቅጣትን የሚደነግግ፣ እኩልነትን ያረጋገጠና ወንጀል መሆን የማይገባውን በወንጀልነት የማይፈርጅ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡
ፍትሕ የማግኘት መብትን ለማስከበር መንግሥትና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ትልቅ ሚና እንዳላቸው የሚጠቅሱት አቶ ፊሊፖስ፣ ሦስቱ የመንግሥት አካላት ሊያስከብሩት የሚገባውን መብት በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ራሳቸው ሲጥሱት እንደሚስተዋልም አመልክተዋል፡፡ ይህ ችግር በሕግ አስተርጓሚውና አስፈጻሚው አካል ጭምር የሚታይ ችግር ቢሆንም፣ አሳሳቢ የሆነው ችግር ግን በሕግ አውጪው በኩል የሚወጡና ለሕግ አስፈጻሚው ሰፊ ነፃነትን የሚሰጥበት አሠራር እንደሆነ አቶ ፊሊፖስ ያስገነዝባሉ፡፡ ሕግ አስፈጻሚው እነዚህን ክፍተቶች ተጠቅሞ ፍትሕ የማግኘት መብትን የሚጥሱ ደንቦችንና መመርያዎችን ማውጣቱንም ምሳሌ በመጥቀስ ያስረዳሉ፡፡
አቶ ፊሊፖስ ፍትሕ የማግኘት መብት ላይ ተፅዕኖ ይፈጥራሉ ካሏቸው አዋጆች መካከል አንዱ በባንክ በመያዣ የተያዙ ንብረቶችን የሐራጅ ሽያጭ የሚደነግገው አዋጅ ነው፡፡ ባንኮች በሕጉ መሠረት ኃላፊነታቸውን ባይወጡ፣ ፍርድ ቤቶች ጣልቃ እንዳይገቡ መከልከላቸው ፍትሕ የማግኘት መብትን እንደሚያጣብብም አመልክተዋል፡፡ በተመሳሳይ የከተማ ቦታ ይዞታ አዋጅ ለሕዝብ ጥቅም ንብረቱ የተወሰደበት ሰው ይግባኝ ሊጠይቅ የሚችለው በካሣ ጉዳይ ላይ ብቻ መሆኑ፣ ፍትሕ ከማግኘት መብት ጋር የሚጋጭ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የመንግሥት ቤቶች ማቋቋሚያ አዋጅ የተባረረ ተከራይ ፍርድ ቤት ሄዶ እንዳይከራከር መከልከሉ ፍትሕ የማግኘት መብትን ከመፃረሩም በላይ ሙስና እንዲበራከት ማድረጉን አቶ ፊሊፖስ አስረድተዋል፡፡ የፍትሐ ብሔር ሕግን ለማሻሻል የወጣው አዋጅ ቁጥር 639/2001 ተጠቅሞ ሕግ አውጪው አስቀድሞ የተወሰነ የሕግ ተርጓሚውን ውሳኔ በሕግ መሻሩም ፍትሕ ከማግኘት መብት መርሆዎች ጋር የሚቃረን እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡ አቶ ፊሊፖስ የንግድ ምዝገባና ፈቃድ አዋጅ፣ የገቢዎችና ጉምሩክ ሥልጣንና ተግባር ለመወሰን የወጣው አዋጅና የግብር ሕግጋቶች እንዲሁ ፍትሕ የማግኘት መብት ላይ ጫና እንደሚፈጥሩ በዝርዝር አብራርተዋል፡፡ የሰበር ሰሚ ችሎቱ ውሳኔዎች እንደ ሕግ መቆጠራቸውን በመጥቀስ የችሎቱ አንዳንድ ውሳኔዎች ፍትሕ የማግኘት መብት ጋር የማይጣጣሙ እንደሆኑም አሳይተዋል፡፡
ዶ/ር አደም ካሴ በጀርመን ሃይድልበርግ ዩኒቨርሲቲ በሚገኘው የማክስ ፕላንክ ፋውንዴሽን ዓለም አቀፍ ሰላምና የሕግ የበላይነት ተቋም ከፍተኛ ተመራማሪ ናቸው፡፡ ዶ/ር አደም እንደ አቶ ፊሊፖስ ሁሉ ፍትሕ የማግኘት መብት ከፍርድ ቤቶች ባሻገር ከአስተዳደራዊ ተቋማት ውሳኔ አሰጣጥና ሕግ አወጣጥ ጋር የተቆራኘ መሆኑን ይገልጻሉ፡፡ እነዚህ ውሳኔዎችና መመርያዎች በአብዛኛው በመርህ ያልተደገፉና ከሥርዓት ይልቅ በተቋማዊ ባህል እንደሚመሩም አመልክተዋል፡፡ የአስተዳደር ሥነ ሥርዓት ሕግ ቢኖር የአስተዳደራዊ ሕጎች አወጣጥና የውሳኔ አሰጣጥ ሥነ ሥርዓት ተገማችነትና ሥርዓትን ሊፈጥር ይችል እንደነበርም ጠቅሰዋል፡፡ ይህን ሕግ ለማውጣት በተለያዩ ጊዜያት ሙከራዎች የተደረጉ ሲሆን፣ በ1996 ዓ.ም. የተዘጋጀው ረቂቅ አልፀደቀም፡፡
ነፃ የሕግ አገልግሎት ድጋፍ
አቶ ፈቃዱ ደምሌ በፍትሕ ሚኒስቴር የጥብቅና ፈቃድና አስተዳደር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ናቸው፡፡ በፓናል ውይይቱ ላይ ነፃ የሕግ አገልግሎት ድጋፍን በተመለከተ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ እየሠራቸው ያሉ ሥራዎችን አብራርተዋል፡፡ አቶ ፈቃዱ ነፃ የሕግ አገልግሎት ድጋፍን በተመለከተ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የሚሠራው ሥራ በሕግ ከተሰጠው ሌሎች ተልዕኮዎች ጋር የተቆራኘ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ፍትሕ ሚኒስቴር የፌዴራል መንግሥትን በሕግ ጉዳይ የማማከር፣ የሕግ ጥናት የማድረግ፣ ሕግ የማርቀቅ፣ ሕግን የማስረጽ፣ ወንጀል የሚቀንስበትን ስልት የመንደፍና የመከላከል ኃላፊነት ተጥሎበታል፡፡ የፌዴራል ፍርድ ቤት ጠበቆችን በተመለከተ ፈቃድ የመስጠት፣ የማደስ፣ ነፃ የጥብቅና አገልግሎት የሚሰጡ ጠበቆችን ጉዳይ የመስጠት ሥልጣን ሌሎች ኃላፊነቶችን ለመወጣት አስፈላጊ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
የፍትሕ ተደራሽነትን ለማስፋፋት ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የተለያዩ መመርያዎችን ማውጣቱን ያስታወሱት አቶ ፈቃዱ፣ በኢትዮጵያ ጠበቆች በገዛ ፈቃዳቸው በሕግ የተጣለባቸውን በዓመት ለ50 ሰዓታት ነፃ የሕግ አገልግሎት የመስጠት ግዴታቸውን እንደማይወጡ አመልክተዋል፡፡ ጉዳዮችን ወስደው አቅም የሌላቸውን ዜጎች ለመርዳት ሰበብ እንደሚደረድሩ፣ ከወሰዱም በኋላ ተገቢውን ትኩረት ሰጥተው እንደማይከታተሉ ወቅሰዋል፡፡
ጠበቆች በተናጠል ከሚያቀርቡት ነፃ የሕግ አገልግሎት በተጨማሪ የሙያ ማኅበራት፣ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች፣ በተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ሥር የተቋቋሙ የሕግ ትምህርት ቤቶች ነፃ የሕግ አገልግሎት መስጫ ማዕከላትን አቋቁመው አገልግሎቱን ይሰጣሉ፡፡ አገልግሎቶቹን ለማቀናጀት በብሔራዊ የሰብዓዊ መብት የድርጊት መርሐ ግብሩ በታቀደው መሠረት ስትራቴጂ ለማውጣት ግብረ ኃይል ተቋቁሞ ሥራ መጀመሩን አቶ ይበቃል አስታውቀዋል፡፡
ፍትሕ የማግኘት መብትን ለማሻሻል መንግሥት በርካታ ሥራዎችንና ጥረቶችን እያከናወነ ቢሆንም፣ ጉድለቶች ይበልጥ ገዝፈው እንደሚታዩ የተለያዩ ጥናቶች ይጠቁማሉ፡፡ አቶ ፊሊፖስ ‹‹ፍትሕ የማግኘት መብት በአጠቃላይ ፈተና ላይ ነው፡፡ ፈተናውን ሙሉ በሙሉ አላለፈም፤›› ብለዋል፡፡ የባለድርሻ አካላትን ግንዛቤ የማሳደግ ሥራ ቅድሚያ ሊሰጠው እንደሚገባ ሁሉም ቢስማማም፣ ፍትሕ የማግኘት መብት መሠረታዊ ችግሮች ላይ ስምምነት አለመኖሩ ችግሩ በቅርቡ ሊፈታ እንደማይችል ይጠቁማል፡፡
በአላስፈላጊ ቀጠሮዎች የተማረረው ጠበቃ ግን አንዳንድ ችግሮች በመጠነኛ ሥራዎች ሊፈታ እንደሚችል ይገልጻል፡፡ ‹‹በሞባይል መልዕክት፣ በስልክ ወይም በኢንተርኔት ጉዳዩ እንደማይታይ ቀድሞ ቢነገርና ባለጉዳዩ ወጪውን ቢሸፍን በጥቂት ወጪ ከድካም፣ ከገንዘብ ኪሳራና ከጊዜ ብክነት መገላገል ይቻል ነበር፤›› ሲልም ይደመድማል፡፡ አቶ ደበበ የኢትዮጵያ የፍርድ ሒደት ‹‹ሥርዓት የማብዛት ሁኔታ (Formalism) ያበዛል፤›› ብለዋል፡፡ እንዲህ ዓይነት አቋራጭ መንገዶች ከክብሬ ጋር አይመጥንም ብሎ ይሆን ፍርድ ቤቱ ያን ሁሉ ሰዓት ቁጭ ላሉ ሰዎች በምሳ ሰዓት ዛሬ ጉዳያችሁ አይታይም የሚለው?
- EthiopianReporter By
- Hits: 14660
- Details
- Category: General - ልዩ ልዩ
ጎሮ ሰፈራ አካባቢ ለወትሮው በሚታጠፍበት ቦታ ላይ ሲደርስ ከፊት ለፊቱ ያሉ ተሽከርካሪዎች ሲፈተሹ ያያል፡፡ ስለዚህ ትራፊክ ፖሊሶቹ የሦስተኛ ወገን ኢንሹራንስ ጨምሮ ስለመሟላታቸው ለሚቀርቡላቸው ጥያቄ አሽከርካሪዎች
ሲመልሱ ተራው ደርሶት በሒደቱ ውስጥ ለማለፍ መጠባበቅ ጀመረ፡፡ መጠባበቁ ከምክንያታዊ ጊዜ ሲያልፍ ወጣቱ ትራፊክ ፖሊሶቹ እንዲያስተናግዱት መጣራት ጀመረ፡፡ ሰሚ አጥቻለሁ ብሎ በማሰቡ ታጥፎ ለመንቀሳቀስ መንገድ ጀመረ፡፡
ድንገት ግን ‹‹ነውር አይደለም እንዴ?›› የሚል ጥያቄ ድምፁን ከፍ አድርጎ ከኋላ ከሚከተል የትራፊክ ፖሊስ ሰማ፡፡ ወጣቱም ተሽከርካሪውን ካቆመ በኋላ ‹‹ነውሬ ምንድን ነው?›› ሲል አጠገቡ የቆመውን ትራፊክ ፖሊስ ጠየቀው፡፡ ለጥያቄው ምላሽ መስጠቱን ወደ ጎን በማድረግ የሚፈልጋቸውን ሰነዶችና ጥያቄዎች አከታትሎ መጠየቅ ጀመረ፡፡ ወጣቱ የተጠየቀውን ሁሉ ካሟላ በኋላ በድጋሚ የሠራው ነውር ምን እንደሆነ ለማወቅ እንደሚፈልግ ገለጸ፡፡ መንጃ ፈቃዱን ጨምሮ ሌሎች መረጃዎችን ለትራፊኩ ሰጥቶ የነበረው ወጣት ሳያስበው ፊቱ ላይ ተወረወሩበት፡፡ የሁለት ዓመት ሕፃን ልጁና ባለቤቱን ይዞ የነበረው ወጣት በፍጥነት ከተሽከርካሪው በመውጣት ትራፊክ ፖሊሱን ተከትሎ ‹‹ለምን እንዲህ ታደርጋለህ?›› ሲል ጠየቀ፡፡ አሁንም ያልጠበቀው ምላሽ ገጠመው፡፡ ትራፊክ ፖሊሱ በቦክስ መታው፡፡
ይህ ሁሉ ድርጊት ሲፈጸም የሚመለከቱት የአካባቢው ሰዎች ብቻ ሳይሆኑ ሌሎች የትራፊክ ፖሊስ ባልደረባዎችም ጭምር ነበሩ፡፡ ወጣቱ ትራፊክ ፖሊሱን ለመክሰስ እንደሚፈልግ በመግለጽ አሁንም መከተሉን አላቆመም፡፡ በአካባቢው የተሰባሰቡት አራት ተጨማሪ የትራፊክ ፖሊሶች ምን እንደተከሰተ እንኳን ለማጣራት ሳይሞክሩ ወጣቱን ይበልጥ በማዋከብና በመገፈታተር መንገዱን እንዲቀጥል አዘዙት፡፡ ‹‹አለቃችሁን ማግኘት እፈልጋለሁ?›› የወጣቱ ቀጣይ ጥያቄ ነበር፡፡ የክፍል አለቃው ራሱን አስተዋውቆ በተሻለ አቀራረብ አነጋገረው፡፡ የሆነውን ሁሉ በጥሞና ከሰማ በኋላ እሱም ቢሆን ጉዳዩን በእርቅ እንዲጨርስ ጠየቀው፡፡ ወጣቱ እንደ ትራፊክ ፖሊሶቹ ሁሉ የመንግሥት ሠራተኛ እንደሆነና አገሩን እንደሚያገለግል፣ የግለሰቡ ድርጊትም በምንም ዓይነት መንገድ አግባብ እንደሌለው እያስረዳ መታወቂያውን አሳየው፡፡
መታወቂያውን በማየት ብቻ የትራፊክ ፖሊሶቹ ያሳዩት የአመለካከት ለውጥ ግን ወጣቱን ይበልጥ አስደነገጠው፡፡ ያዋክቡት የነበሩት ትራፊክ ፖሊሶች ወጣቱ ክሱን በመተው በእርቅ እንዲጨርስ ይወተውቱት ጀመር፡፡ አሁን ፖሊሱ ለምን ያህል ዓመት እንደሠራ፣ ልጆችና ትዳር እንዳለው በመጥቀስ ነገሩን እንዲረሳው ይማፀኑት ጀመር፡፡ ድርጊቱን መማርያ ለማድረግ የተነሳው ወጣት ግን ጥያቄያቸውን ችላ ብሎ ወደ ክፍለ ከተማው ፖሊስ መምሪያ አመራ፡፡ ወደ ቅጥር ግቢው ደርሶ ክስ የሚመሠረትበትን ክፍልና የምርመራ ኃላፊውን አገኘ፡፡ ኃላፊው የወጣቱን ጉዳይ ከሰሙ በኋላ መደብደቡን ሲገልጽላቸው ቀጣዩ ጥያቄያቸው ‹‹ከዚያስ?›› መሆኑ ወጣቱን ግራ አጋባው፡፡ ድርጊቱ በተከሰተበት ቦታ ያገኛቸው ሽማግሌ፣ የትራፊክ ፖሊሱ ባልደረቦች፣ መርማሪ ፖሊሶቹ፣ ዓቃቤ ሕጉ እንዲሁም የወጣቱ ጓደኞች ክስ መክሰሱ የበቀል ዕርምጃ እንደሆነና የሚያስተምረውም ሆነ የሚቀይረው ነገር እንደሌለ ማመናቸው ሊፈጽመው ያሰበው ነገር ትርጉም እንዲያጣ አደረጉት፡፡ ምንም እንኳን ከብዙ መንገላታት በኋላ በፖሊስ ጣቢያው ቃል መስጠትና ሚስቱን ማስመስከር ቢችልም፣ በጉዳዩ ለመግፋት ግን ተነሳሽነቱ እንዲሞት እንዳደረጉት ይገልጻል፡፡
ወጣቱ የሺዋስ ፈንታሁን ይህ አጋጣሚ የደረሰበት በግንቦት ወር 2005 ዓ.ም. ነበር፡፡ እርግጥ ነው በፖሊስ ጣቢያዎች ሥር የተዋቀሩት የወንጀል መከላከል የሥራ ሒደት፣ የምርመራና ክትትል ሥራ ሒደት እንዲሁም የትራፊክና ደኅንነት ክፍል ባልደረቦች አደረሱት ተብሎ የሚሰማው የሰብዓዊ መብት ጥሰት የሺዋስን ከገጠመው በአብዛኛው ይልቃል፡፡ ነገር ግን ጉዳዩ ይመለከታቸዋል የሚባሉ አካላት ቸልተኝነትና ፍላጎት ማጣት፣ እንዲሁም በቁርጠኝነት ጥሰቶችን ለማረም ለሚደረጉ ጥረቶች ድጋፎች አለመኖር ሁኔታውን ማወሳሰቡ በሁሉም ጉዳዮች የጋራ ችግር እንደሆነ ኤክስፐርቶች ያስረዳሉ፡፡
ሕገ መንግሥቱን በማክበርና በማስከበር ወንጀልንና የወንጀል ሥጋትን በመከላከልና በመቀነስ፣ አስተማማኝ ሰላምና ፀጥታ በየአካባቢው እንዲረጋገጥ ማድረግና የሕዝቡን ሰላማዊ ኑሮና ደኅንነት ማስጠበቅ የፖሊስ ዋነኛ ተግባር ነው፡፡ ሆኖም ግን ጥቂት በማይባሉ አጋጣሚዎች ራሱ ፖሊስ በወንጀል ድርጊት ተሳታፊ ሆነ ተብሎ ሲነገር ይሰማል፡፡
በተለይ በጥበቃ ሥር ያሉ ሰዎች በፖሊስ የተለያዩ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ደረሰብን ማለታቸው የዜጎችን ትኩረት ከሳቡ የወንጀል ጉዳዮች ጋር ተያይዞ የተለመደ ሆኗል፡፡ ከ1949 ዓ.ም. ጀምሮ በዘመናዊ መንገድ ተደራጅቶ ተግባራዊ መሆን የጀመረው የኢትዮጵያ የወንጀል ፍትሕ አስተዳደር ሥርዓት በጥበቃ ሥር ላሉ ሰዎች የተለያዩ መብቶች ዕውቅናና ጥበቃ ይሰጣል፡፡
በጥበቃ ሥር ያሉ ሰዎች መብቶች ተብለው በኢትዮጵያ ከሚታወቁት መካከል ያለመናገር ወይም ቃል ያለመስጠት መብት፣ በ48 ሰዓት ውስጥ ፍርድ ቤት የመቅረብ መብት፣ በዋስ የመለቀቅ መብት፣ የተፋጠነ ፍትሕ የማግኘት መብት፣ ጥፋተኛ ሆኖ ያለመቆጠር መብት፣ በሕግ ባለሙያ ወይም አማካሪ የመወከል መብት፣ ክብርን ከሚያዋርድ አያያዝና ቅጣት የመጠበቅ መብት፣ ከቤተሰቦቻቸውና ከሕግ አማካሪዎቻቸው ጋር የመገናኘት መብቶች ተጠቃሽ ናቸው፡፡
እነዚህን መብቶች ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችሉ ፖሊሲዎች፣ ሕገ መንግሥት፣ ዝርዝር ሕጎች፣ ተቋማትና አሠራሮችን ለመቅረፅ የተለያዩ ጥረቶች ተደርገዋል፡፡ ይሁንና እነዚህ በወረቀት ላይ ከፍተኛ ምቾት የሚሰጡ መብቶች በአፈጻጸም ወቅት ምቾት እንደሚነሱ የዜጎች ምስክርነት ያሳያል፡፡
በግንቦት ወር 2005 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ‹‹በጥበቃ ሥር ያሉ ሰዎች መብት አከባበር በኢትዮጵያ ፖሊስ ጣቢያዎች፡- የክትትል ሪፖርት›› በሚል ርዕስ ያወጣው ሪፖርት የእነዚህ መብቶችን አፈጻጸም የዳሰሰ ነው፡፡
ኮሚሽኑ በአንዳንድ የፖሊስ አባላትና መርማሪዎች ያልተመጣጠነ ኃይል በመጠቀም ተጠርጣሪን መያዝ፣ ዛቻ፣ ስድብና ድብደባ በተጠርጣሪዎች ላይ መፈጸምና አስገድዶ ቃላቸውን መቀበል ‹‹በተወሰኑ›› ፖሊስ ጣቢያዎች መከሰቱን በሪፖርቱ አመልክቷል፡፡ በአብዛኛው ጣቢያዎች ተጠርጣሪዎች በሚያዙበት ጊዜ ያለመናገር መብት እንዳላቸውና የሚናገሩት ማንኛውም ቃል ራሳቸው ላይ እንደማስረጃ ሆኖ እንደሚቀርብባቸው እንደማይነገራቸውም ሪፖርቱ ይጠቁማል፡፡
በጥበቃ ሥር ባሉ ተጠርጣሪዎች ላይ
እነዚህን ክስተቶች በመጥቀስ በኢትዮጵያ ፖሊስ በጥበቃ ሥር ባሉ ተጠርጣሪዎች ላይ የሚያደርሰው የሰብዓዊ መብት ጥሰት የመንግሥት ይሁንታ የተቸረውና ተቋማዊ አደረጃጀት ያለው ነው የሚሉ አሉ፡፡ የመንግሥት ፖሊሲ፣ ሕጎችና አሠራሮች የሰብዓዊ መብት ጥሰትን የሚዋጉ በመሆናቸው የግለሰቦች ጥሰት አጋጣሚ እንጂ የሥርዓቱ መገለጫ አይደለም በሚል በሌላ ወገን ክርክር ይቀርባል፡፡ የእነዚህ ሁለት ጽንፍ የያዙ ክርክሮች መቋጫ ጥፋት አጥፍተው በተገኙ የፖሊስ አባላት ላይ የሚወሰደው ዕርምጃ ነው፡፡
የፖሊስ ተጠያቂነት
ሪፖርተር ያነጋገራቸው የሰብዓዊ መብት ኤክስፐርት፣ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ፈጽመዋል ስለሚባሉ ፖሊሶች በየጊዜው ዜና የሚሰማው ዜጋ፣ ለፍርድ ቀርበው ለድርጊታቸው ተጠያቂ መደረጋቸውን ግን ሪፖርት የሚያደርግለት ካላገኘ ተቋማዊ ጥሰት እንዳለ ቢያስብ እንደማይፈረድበት ያስረዳሉ፡፡
የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ሪፖርት አሠራር ተቋማዊ ጥሰትን አይቀበልም፡፡ ግለሰቦች የሚፈጥሯቸው ችግሮች በተቋሙ መፍትሔ እየተሰጣቸው እንደሆነ ያትታል፡፡
አቶ ምትኩ መኰንን በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን የሰብዓዊ መብት ጥበቃና ክትትል ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ናቸው፡፡ እንደ እሳቸው ገለጻ፣ ኮሚሽኑ በጥበቃ ሥር ያሉ ሰዎች መብትን መጣስ የፖሊስ ተቋም የያዘው አቋም እንዳልሆነ ድምዳሜ ላይ የደረሰው በሥራ ገጠመኞች የተነሳ ነው፡፡ ኮሚሽኑ በፖሊስ አማካይነት የሰብዓዊ መብት ጥሰት መፈጸሙ ሪፖርት ተደርጎለት ምርመራ አድርጎ ጥሰቱን ባረጋገጠባቸው ጉዳዮች ሁሉ መንግሥት ዕርምጃ መውሰዱን አቶ ምትኩ ይመሰክራሉ፡፡
መንግሥት የወሰዳቸውን ዕርምጃዎች ለኮሚሽኑ ሪፖርት የሚያደርግ ቢሆንም፣ ለኅብረተሰቡ መረጃውን የማድረስ ችግር እንዳለ ግን ይጠቁሉ፡፡ ‹‹ስህተት በሠሩ ፖሊሶች ላይ ዕርምጃ ሲወስድ ለኅብረተሰቡ የሚገለጽበት አሠራር የለም፡፡ በዚህ የተነሳ በተቋም ደረጃ የተሠራ ሊመስል ይችላል፤›› በማለትም ያብራራሉ፡፡ ይሁንና በተቋም ደረጃ ጥሰቶቹ የሚደገፉ ቢሆን ኖሮ ጉዳዮች ይደበቁና ይድበሰበሱ እንደነበር ይከራከራሉ፡፡ ‹‹እኛ የምናውቃቸውን ጉዳዮች መርምረን፣ ጥያቄ አቅርበን ያልተከሰሰና ዕርምጃ ያልተወሰደበት አላገኘንም፡፡ ከሥራ የተባረሩ፣ የብዙ ዓመት እስራት የተወሰነባቸው ብዙ ጉዳዮችን እናውቃለን፤›› ሲሉም የተቋማቸውን አቋም አንፀባርቀዋል፡፡
የሰብዓዊ መብት አፈጻጸምን ለማሳለጥ ይረዳል የተባለው የብሔራዊ የሰብዓዊ መብት የድርጊት መርሐ ግብር በጥቅምት 2006 ዓ.ም. ወደ ሥራ ገብቷል፡፡ ባለድርሻ አካላትን የሚሠሯቸውን ሥራዎች በማቀናጀት በወረቀት ላይ ያሉ መብቶችን ወደ መሬት በማውረድ ለእያንዳንዱ ዜጋ ተደራሽ የማድረግ ዓላማ ያለውን ይህን ሰነድ አፈጻጸም የሚከታተለው ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ይበቃል ግዛው፣ እንደ አቶ ምትኩ ሁሉ የአፈጻጸም ክፍተቶችና የግለሰቦች ስህተት ቢያጋጥምም ተቋማዊ የሆነ የፖሊስ የሰብዓዊ መብት ጥሰት አለ ብለው እንደማያምኑ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ በሰብዓዊ መብት ጥሰት የወደቁ ሥርዓቶችን የተካ መንግሥት የሰብዓዊ መብት ጥሰትን ተቋማዊ አሠራር ያደርጋል ብሎ መገመት አስቸጋሪ እንደሆነም አቶ ይበቃል ያስገነዝባሉ፡፡ ‹‹ይሄ መንግሥት ሰብዓዊ መብትን ማክበርና ማስከበር የአገር ህልውና መሠረት አድርጎ ይወስዳል፤›› ሲሉም የሰብዓዊ መብት መከበር የምርጫ ጉዳይ እንዳልሆነ አመልክተዋል፡፡
አቶ ይበቃል እንደ ሌሎች መብቶች ሁሉ በጥበቃ ሥር ያሉ ሰዎች መብቶች ሕገ መንግሥታዊ ዕውቅና በመስጠት ሳይገደቡ ተጽፈው ብቻ እንዳይቀሩ አፈጻጸማቸውን ወደ መሬት ለማውረድ የሚያስችሉ ተቋማዊ አደረጃጀቶች እንዳሉ ይገልጻሉ፡፡ አደረጃጀቶቹ ስህተት የሚፈጽሙ የፖሊስ አባላትን ተጠያቂ ለማድረግ የሚያስችሉ እንደሆኑም ያስረዳሉ፡፡ ‹‹በርካታ ከፍተኛ የፖሊስ አመራሮች፣ የማረሚያ ቤቶች አመራሮች መብት መጠበቅ አልቻላችሁም ተብሎ ዕርምጃ ተወስዶባቸዋል›› ሲሉም የፖሊስ ተጠያቂነት በወረቀት አለመገደቡን ይመሰክራሉ፡፡
የድርጊት መርሐ ግብሩ ፖሊሶች በወንጀል የተጠረጠሩ ሰዎችን በቁጥጥር ሥር ሲያውሉ ተጠርጣሪዎቹ ያላቸውን መብት ሊገልጹላቸው እንደሚገባ ያስቀምጣል፡፡ ይህንን ያለማድረግ አስተዳደራዊ ዕርምጃ የሚያስወስድ እንደሆነ በፖሊስ ኮሚሽኖች የአባላት የሥነ ምግባር ደንቦች ውስጥ እንዲካተት ሥልጠናዎች እንዲሰጡም ምክረ ሐሳብ ያቀርባል፡፡ አቶ ይበቃል ሁለቱንም ድርጊቶች ለማሳካት ጥረት መደረጉን አመልክተዋል፡፡
የወንጀል ጉዳዮችን በመያዝ ለታወቁት ጠበቃ አቶ አምሃ መኰንን ግን በዜጎች ዘንድ የፖሊስ ጥሰት ተቋማዊ እንደሆነ ተደርጎ መታሰቡ የሚገርም ነገር አይደለም፡፡ ‹‹ለምሳሌ ደንበኛዬ በፖሊስ ሲመረመር እንዳማክር ጥሪ ተደርጐልኝ አያውቅም፡፡ ይሄ የማይታሰብ ነገር ነው፤›› ሲሉ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ ‹‹በርካታ በፖሊስ የተፈጸሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን ታዝቤያለሁ፡፡ ነገር ግን ተጠያቂነትን ከማረጋገጥ ይልቅ ጉዳዩን ስታነሳ ቂም ይያዝብሃል፤›› ሲሉም አክለዋል፡፡
አቶ ምትኩም ሆኑ አቶ ይበቃል ያጠፉ ፖሊሶችን ተጠያቂነት የማረጋገጥ ሥራ በሚፈለገው መልኩ እየተሠራ እንዳልሆነ ያምናሉ፡፡ የግለሰቦች ጥፋት እየተበራከተ ሲመጣ ተቋማቱ ግለሰቦችን መቆጣጠር እንደተሰናቸው ስለሚያሳይ ኃላፊነቱን እንደሚጋሩ በመጠቆም፣ ጉዳዩ ይበልጥ ትኩረት ሊሳብ እንደሚገባ አቶ ምትኩ ይመክራሉ፡፡
የተራዘመ የምርመራ ጊዜ
ቀልብ በሳቡ ጉዳዮች ተደጋግሞ እንደታየው በጥበቃ ሥር ያሉ ሰዎች በተራዘመ የምርመራ ሒደት ያልፋሉ፡፡ እንደ አቶ አምሃ ገለጻ፣ የችግሩ ዋና ምንጭ ፖሊሶች ወንጀል ተፈጽሟል ብለው እንዲያምኑ የሚያደርጋቸውን ማስረጃ ሳይዙ ተጠርጣሪዎችን ለማሰር የማያመነቱ መሆኑ ነው፡፡ በተለይ የፖለቲካ ትኩሳት ባለባቸው ጉዳዮችና የመንግሥት ልዩ ፍላጎት በሚንፀባረቅባቸው ጉዳዮች ላይ አላስፈላጊ መንዛዛቶች እንደሚስተዋሉ አቶ አምሃ ገልጸዋል፡፡
‹‹የወከልኳቸው የዞን ዘጠኝ ጉዳይ ክስ ሳይመሠረትባቸው 83 ቀናት ያህል በምርመራ ቆይተዋል፤›› ሲሉም አቶ አምሃ እንደ አንድ ማሳያ ያስረዳሉ፡፡ ‹‹ደንበኞቼ በጥበቃ ሥር እያሉ ለ20 ቀናት ያህል ልጎበኛቸው አይደለም በምርመራው ሒደት ላማክራቸው አልቻልኩም፤›› ሲሉም ይከሳሉ፡፡
ይህ አቶ አምሃ ከልምዳቸው በመነሳት የሚገልጹት ሁኔታ ሪፖርተር ያነጋገራቸውና በዘፈቀደ የመረጣቸው ዜጎች የሚጋሩት ነው፡፡ እንደ እነዚህ ሰዎች እምነት ፖሊስ በወንጀል የጠረጠራቸውን ሰዎች ለመመርመር ካልታሰሩ ሥራውን የሚሠራ አይመስለውም፡፡ በኢትዮጵያ ሕግም ሆነ ዓለም አቀፋዊ ተቀባይነት ባላቸው አሠራሮች በመርህ ደረጃ ዜጎች ነፃነታቸው ተጠብቆና በቁጥጥር ሥር ሳይውሉ የተጠረጠሩበትን ወንጀል አጣርቶ አስተማማኝ መረጃ በቅድሚያ መያዝ ያስፈልጋል፡፡
አቶ ምትኩ ሰው ታስሮ መረጃና ማስረጃ መሰብሰብ ተገቢነት የሌለው አሠራር መሆኑን ቢገልጹም፣ በተግባር ግን ፖሊስ ከእስር በኋላ መረጃና ማስረጃ የሚሰበስብበት አሠራር እንደሚስተዋል ይጠቁማሉ፡፡ አቶ ምትኩ በኢትዮጵያ ባህል በወንጀል የተጠረጠረ ሁሉ ወንጀለኛ ነው የሚል እምነት መኖሩ፣ ፖሊሶችም አልፎ አልፎ አመለካከታቸው በዚያው እንዲቃኝ ሳያደርግ እንዳልቀረ ያመለክታሉ፡፡ ይህንን ለመቀየር በርካታ ቀሪ ሥራም እንዳለ ይገልጻሉ፡፡
ለአቶ ምትኩም ሆነ ለአቶ ይበቃል ችግሩን ለመቅረፍ ትልቁ ቁም ነገር የፖሊሶችን ግንዛቤ ማሳደግ ነው፡፡ ‹‹ሰብዓዊ መብት እንደ ባህል ሊዳብር ይገባል፡፡ ከግንዛቤ እጥረት የሚነሱ የአፈጻጸም ክፍተቶች ይኖራሉ፡፡ ሰብዓዊ መብት በተፈጥሮው ሥር ለመስደድ ጊዜ ይወስዳል፡፡ የሕግ ሥርዓት ተበጅቷል፣ የፖለቲካ ርዕዮተ ዓለምና አመለካከቶች በግልጽ ተተንትነው ቀርበዋል፣ ሕጎች ወጥተዋል፣ አሠራሮች ተዘርግተዋል፡፡ ሰብዓዊ መብትን ማወቅ ብቻ ሳይሆን የአመለካከት አካል ለማድረግ ጊዜ ይወስዳል፤›› በማለት አገሪቱ ያለባትን ተግዳሮት የጠቆሙት አቶ ይበቃል፣ በድርጊት መርሐ ግብሩ አማካይነት የተሠሩት ሥራዎች ነገሮች በትክክለኛ አቅጣጫ ላይ እንዳሉ እንደሚያሳዩ አስገንዝበዋል፡፡ ጽሕፈት ቤታቸውም ለፖሊስ፣ ለማረሚያ ቤቶች አስተዳደር፣ ለፍርድ ቤቶች፣ ለፍትሕ ቢሮዎችና ለፍትሕ ሚኒስቴር ሰፊ የአቅም ግንባታ ሥልጠና መስጠቱንም አስታውሰዋል፡፡ ‹‹ግንዛቤ ማስጨበጥ ብቻ ሳይሆን እንዲፈጽሙት የቤት ሥራ እንሰጣለን፤›› በማለትም ጽሕፈት ቤቱ ተግባራዊ እንቅስቃሴን ያገናዘበ ሥራ እንደሚሠራ ገልጸዋል፡፡
አቶ አምሃ ግን ፖሊሶች የሰብዓዊ መብት ጥሰት የሚፈጽሙት ከግንዛቤ እጥረት እንዳልሆነ ይከራከራሉ፡፡ ‹‹የተጠርጣሪዎቹን መብት የማያውቅ መርማሪ አለ ብዬ አላምንም፤›› ሲሉም አቋማቸውን ገልጸዋል፡፡ ‹‹መርማሪዎቹ ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት ለመውሰድ ከውጭ ካሉ መረጃዎችና ማስረጃዎች ይልቅ ጥገኛ የሚሆኑት በእምነት ቃልና በምስክሮች ላይ ነው፡፡ እነዚህ የምርመራ ጊዜውን ማራዘም ብቻ ሳይሆን ለሰብዓዊ መብት ጥሰትም ይጋብዛሉ፤›› ሲሉም አብራርተዋል፡፡
ጥሰት ተፈጽሟል ብለው ባመኑበት አጋጣሚ ክስ ከሰው ያውቁ እንደሆነ በሪፖርተር የተጠየቁት አቶ አምሃ፣ የፖሊስ ባልደረባን ከሰው እንደማያውቁ ገልጸዋል፡፡ ማስረጃ የማግኘት ችግርና በተጠያቂነት ሥርዓቱ ላይ እምነት ማጣት ምክንያት እንደሆኑም ጠቅሰዋል፡፡ ‹‹ግለሰቡ ተጠያቂ ቢሆን የተቋሙ ስም የሚጠፋ ይመስላቸዋል፤›› ሲሉም አክለዋል፡፡ አቶ ምትኩ ፖሊሶችን ተጠያቂ ለማድረግ ማስረጃ ማግኘት ከባድ መሆኑን ይጋራሉ፡፡
ወጣቱ የሺዋስም ከትራፊክ ፖሊሱ ጋር በገጠመው ሁኔታ እንዲሁም በሌሎች ጉዳዮች ይህን ችግር እንዳስተዋለ ጠቁሟል፡፡ ‹‹ከሥራ ባልደረቦቻቸው አንዱን ለመርዳት ማሰቤን ብቻ ነበረ ያስተዋሉት፤›› ሲልም ክስ የመክሰስ ሐሳቡን እንዲተው ያስቻለውን ነጥብ ያመለክታል፡፡
አቶ ይበቃል የዜጎችን አመለካከት መቀየር ቁልፍ በመሆኑ ከአፈጻጸም ጎን ለጎን ግንዛቤ ማስጨበጥ ተጠናክሮ እንደሚሠራ ይገልጻሉ፡፡ አቶ ምትኩ በተጨማሪ የሰው ኃይልና የቁሳቁስ ችግርን ይጠቅሳሉ፡፡ ሌሎች የመንግሥት ቁርጠኝነት የበለጠ መሠረታዊ ችግር መሆኑን ያጎላሉ፡፡
- EthiopianReporter By
- Hits: 13198
More Articles …
Page 2 of 3