ባለንበት ዘመን ሕገ መንግሥት ወይም ስለመንግሥት አሠራርና አመራር የሚደነግግ ሕግ የሌሎው ሀገር ለማግኘት ያስቸግራል፡፡ ሳስበው ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓት መደንገግና በዛው ልክ መቆጣጠር ያስፈለገበት መሠረታዊ ምክንያት የሰው ልጅ ካለፈባቸው የችግርና የጦርነት ውጤት የቀሰመው አብይ መፍትሔ እንደሆነ ይሰማኛል፡፡ አብዛኞቹ ሀገራት በሕገ መንግሥታቸው ውስጥ ከሚያካትቱት መሠረታዊና ጥቅል ድንጋጌዎች መካከል የመንግሥት ሥልጣንና ተግባር፣ የዜጎች መሠረታዊ መብትና ግዴታ፣ የመንግሥት አስተዳደርና የሥልጣን ክፍፍል እንዲሁም የአሠራር ሁኔታ ይገኙበታል፡፡
የጉዳዩ መነሻ
ለዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆነኝ በመዝገብ ቁጥር 78398 በአቶ ሽፈራዉ ደጀኔ እና ወ/ሮ ጸሀይ ተስፋዬ በአንድ በኩልና በአቶ ሲሳይ አበቡ በሌላ በኩል በተደረገ ሙግት የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ችሎት ጥቅምት 19 2005 የሰጠዉ ዉሳኔ ነዉ፡፡ ጉዳዩ የተጀመረዉ በወረዳ ፍርድ ቤት በአቶ ሲሳይ አበቡ ከሳሽነትና በአቶ ሽፈራዉ ደጀኔ እና ወ/ሮ ጸሀይ ተስፋዬ ተከሳሽ ነዉ፡፡ ከሳሹ እንደሚለዉ በእሱና በተከሳሹ መካከል ሐምሌ 17 2003 የተቋቋመ የቤት ሽያጭ ዉል አለ፡፡