መግቢያ
ሁሉም ሕጎች በራሳቸው ምሉዕ አይደሉም፡፡ በመሆኑም ሕጎችን በተገቢው የአተረጓጎም ሥርዓት መሠረት ተርጉሞ ሥራ ላይ ማዋል ያስፈልጋል፡፡ በተለይ ደግሞ አጠቃላይ መርሆዎችን የደነገጉ ሕጎችን የያዙ እንደ ሕገ-መንግሥት ዓይነት ሕጎች በከፍተኛ ጥንቃቄ መሠረታዊ የአተረጓጎም መርሆዎችን በተከተለ ሁኔታ ፍጹም ገለልተኛና ብዘሀኑን በሚወክል ብቃት ባለው ሕገ-መንግሥት ተርጓሚ ሊተረጎም ይገባዋል፡፡ ይህም በመሆኑ ብዙ ሐገራት ሕገ-መንግሥት የሚተረጉም ራሱን የቻለ ተቋማትን አቋቁመዋል፡፡
ሐገራችን ኢትዮጵያም እንደሌሎች ሐገራት የሕገ-መንገስት ትርጉም ጥያቄ ሲቀርብ ጉዳዩን ተቀብሎ ተገቢውን ውሳኔ የሚሰጡ ተቋማትን አቋቁማለች፡፡ የኢ.ፊ.ዲ.ሪ ሕገ-መንግሥት የሕገ-መንግስታዊ ክርክር ጉዳይ ሲነሳ ጥያቄው እንዴት መልስ ያገኛል ለሚለው ድንጋጌ አስቀምጧል፡፡ በሕገ-መንግስቱ አንቀጽ 62 ላይ የፌደሬሽን ምክር ቤት ሕገ-መንግስቱን የመተርጎም ሥልጣን ይኖረዋል፡፡ የሕገ-መንግስታዊ ክርክር ጉዳይ ሲነሳ በፌደሬሽን ምክር ቤት ውሳኔ ያገኛል በማለት ደንግጓል፡፡ የፌደሬሽን ምክር ቤቱም የሕገ-መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔ በሚያቀርብለት ሕገ- መንግስታዊ ጉዳይ ላይ በሠላሳ ቀናት ውስጥ ውሳኔ ይሰጣል፡፡
የፌደሬሽን ምክር ቤት ሕገ-መንግስታዊ ትርጉም በሚሰጥበት ጊዜ ሞያዊ ዕገዛ የሚሰጠው የሕገ-መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔ ሥልጣንና ተግባር በሕገ-መንግስቱ አንቀጽ 84 ላይ ተዘርዝሮ ተቀምጧል፡፡