ሕግ ጭራሽ ካለመከበሩ በከፋ ተመርጦ ሲከበር የበለጠ አልተከበረም፡፡ አሁን ባለን መረጃ ሀገሪቱ ከቻይና ጋር ስለገባነው የብድር ስምምነት የሚያትትውን 1000ኛውን አዋጅ ካወጀች ብኋላ  እንኳ ከመቶ በላይ አዋጆች ወጥተዋል፡፡ ኑሮው፣ ፖለቲካው፣ ኢኮኖሚውና ማህበራዊ ጉዳያችን ብዙ ነው እና ሕጎቹ በዙ አይደለም ጉዳዩ፡፡ ስንቱ በርግጥ ወጥቶ ሥራ ላይ ዋለ ነው ጥያቄው፡፡ የማናከብረውን እና የማንተገብረውን ሕግ ማውጣት ከሕግ አልባነት አይሻልም፡፡ 

ይህ ጽሑፍ ስለ መረጃ ነፃነት ነው፡፡ ሰብአዊና አለማቀፋዊ የሆነው የመረጃ ነፃነት  መብት ተጥሷል፡፡ በአጭር ቋንቋ ህገ መንግስቱ ተጥሷል፡፡ የተጣሰው ደግሞ ህጉ በወጣለት ህዝብም ፤ ህጉ በወጣበት መንግስትም ፤  ህጉ በወጣላቸው ሚዲያዎችም ጭምር ነው፡፡

ሁሉን ብፅፍ ቀለም አይበቃም እንዲል ሊቁ እኔ ግን እናተን በረጅም ጽሑፍ ላለማሰልቸት  እንደሚከተለው አሳጥሬዋለሁ፡፡ በሕገ መንግሥቱ የተከበረው እና የታፈረው የዜጎች መረጃ የማግኘት መብት በሚዲያዎች እና በመንግስት ተቋማት በአደባባይ እየተሻረ ነው፡፡ ግልፅ ነው ዜጎች ስለማናቸውም ጉዳይ እጅግ ውስን ከሆኑ በስተቀሮች በቀር መረጃ የማግኘት መብት አላቸው፡፡ ዴሞክራሲ ጎዞ ጀምሯል የሚባለው ጠያቂ ሚዲያ ፣ መለሽ መንግስትና አድማጭ ህዝብ ሲኖርም ጭምር ነው፡፡ ያለ መረጃ ነፃነት ዴሞክራሲ የለም አይኖርምም፡፡ ካልተማሩ እንዴት ያውቃሉ ካላወቁ እንዴት ይጠይቃሉ እንዲል መጽሐፍ የመረጃ ነፃነት ወይም መረጃ የማግኘት መብት የዴሞክራሲ አምድ ነው፡፡

ሚዲያዎች መንግስት ሃላፊዎችን እና የመንግስት ተቋማትን የሚያጋልጡ መረጃዎችን ጨምሮ ማናቸውንም የህዝብ መረጃ የመጠየቅ ጠይቆ የማግኘት መብትም ግዴታም አለባቸው፡፡ መንግስት እጅግ ጥቂት ከሆኑ እንደ ሃገር ደህንነት የሚመለከቱ ጉዳዮች በቀር ምን? ለምን? እንደሚሰራ ዜጎች የማወቅ እና በጉዳዩ ላይ በሻቸው መንገድ ሃሳባቸውን የመግለፅ መብትና አቋም የመያዝ መብት አላቸው፡፡ ጉዳዩ አዋጃዊ አይደለም ህገመንግስታዊ ጭምር ነው፡፡  ስለዚህ  ይህን መብት አለማክበር ህገ- መንግስትን አለማክበር ነው፡፡ ህገ-መግስት አልተከበረም የሚባለው የየግል ቁስላችን ሲናካና ትላንት ድንጋይ ወደ መንግስት ሲወረወር  ዛሬ የፌደራል ስረአቱ ሲነካ ብቻ አይደለም ፡፡ በህገ-መግስቱ በግልፅ እና በቅድሚያ የተደነገጉት የግለሰብ እና የህዝብ መብቶች ሲጣሱም ጭምር ነው፡፡ የህገ-መንግስቱን  መጣስ ሁሌ ከፌደራል ስረአት መከበር አለመከብር ጋር ማያያዝ ህገመግስቱ  ለግለሰቦች የሰጣቸውን በረጅም የህዝቦች ትግልና መሰዋትነት  አለማቀፋዊነት ደረጃ ያገኙ  መብቶችን መጣስ ነው፡፡ መቼስ ስረአቱ የተዘረጋው ለህዝቦች መብት ሰላም እና ደህንነት ከሆነ የግለሶችን እና የህዝቦች መብት እየጣሱ ስረአቱን መጠበቅ ውሃውን እያፈሰሱ  ቧንቧውን እንደመንከባከብ ያለ አባካኝነት ነው፡፡

ትልንትም ሆነ ዛሬ መርጠን ተግተን የምንተገብራቸው ህጎች ያሉትን ያህል  ስለመውጣታቸው ህጎቹ የተቀመጡበት መደርደሪያ እጅ የሚመለከተው ፈፃሚ የማያውቃቸው ህጎች ለቁጥር ይታክታሉ፡፡  ሲያስፈልጉን ብቻ እንደካርታ ጨዋታ መርጠን የምንተገብራቸው ህጎች መሰረታዊውን የእኩልነት እና ከአድሎ የነፃ መሆን የሚጠይቀውን ህገ-መንግሰታዊ መርህ ይጥሳሉ፡፡  በአድሎ ከሚፈፀም መልካም ሕግ ይልቅ በእኩልነት የሚተገበር ጨቋኝ ሕግ የሚሻል ይመስለኛል፡፡

አሁንም መንደርደሪያው ስለ መረጃ ነፃነት ነው፡፡ በቅርብ ወራት በተከታተልኳቸው ጉዳዮች ብቻ ጉዳዩን ብንመዝነው መረጃ ሲጠየቁ መለስ ለመስጠት የማይፈልጉ ፤ ስልካቸውን እና ቢሯቸው ለተራው ዜጋ አይደለም ለጋዜጠኞች  የከረቸሙ ፤ ደግነታችን ይዘመር  ነውራችን ግን ይሸሸግ  የሚሉ የመግስት ተቋማት እና ሃላፊዎች በርክተዋል፡፡ የተቋማቱን እና የሃላፊዎቹን ፅድቅ እንጅ ኩነኔ ለመግለፅ የሚተጉ ሚዲያዎችን ማግኘት ይቸግራል (ከበስተቀሮቹ ውጭ )

አፋር የሆነው ነገር ምንድነው?  ጎንደረስ? በርግጥ ታከለ ሊነሳ ነው? ለምን?  የአዲስ አበባው ሰልፍ ለምን ተከለከለ? ችግሩ የማን ነው? ለምድንው የክልል ፕሬዘዳንቶች በሞጋች የጋዜጠኛ ጥያቄ እንደ ተራው ፖለቲከኛ እና አክቲቪስት የማይጠየቁት?  ቆይ ከምርጫ በኋላ ያለው የሃገሪቱ ሁኔ ምን እንደሚመስል መወያየት ያለብን መቼ ነው?  ማን ካሸነፈ አገሪቱ ምን ትመስላለች ? መንግድ ተዘግቷል? ለምን? ፖሊስ ሕግ እያስከበረ ነው እየጣሰ? የእንትን ሚኒስቴር ምን እየሰራ ነው እያለማነው እያጠፋ ? እነትና ታስረው ለምን እነትና ዝም ተባሉ? እስኪ እናንተም ጠይቁ ግን እንዲህ እንዲያ  እያልን ብንጠይቅ  በአሉባልታ እና በአሉሽ አሉሽ እንጅ በመረጃ አልተደገፍንም ስለዚህ እየተናቋርን እየተደናቆርም፡፡

ምን ለማለት ነው፡፡ በሐይል መብቱ የሚያስከብር ሳይሆን መብቱን በሰለማዊ መገድ የሚጠይቅ ህዝብ (ይህ ሃሳብ መንግስት ተገቢ ህጋዊ መብት በሰላማዊ መነገድ ተጠይቆ አሻፈረኝ ሲል የሚደረግ ሃይልን አይጨምርም) የመንግስ አፈ-ቀላጤ ሳይሆን የህዝብ ድምፅ የሆነ ሚዲያ ፤  ጀብዳቸው ብቻ ሳይሆን ጉዳቸው እዲወጣ የሚፈቅዱ ፤ ሲያጠፉ በፈቃዳቸው ሃላፊነታቸውን የሚለቁ የሥራ ሃለፊዎች ከሌሉ  ህገ መንግስቱን እየተጣሰ ነው፡፡ ህገመንግስቱን ከተጠረራጠራችሁት  አለማቀፋዊውው መረጃ የማግኘት በመረጃ እና በእውቀት ተመስርቶ  የመወያየት የማወቅ እና የመሰለውን አቋም የመያዝ መብታችን እየተጣሰ ነው፡፡ ይህ ደግሞ የአንድ ጠቅላ ሚኒስተር ጉዳይ ብቻ ከመሰለን በርግጥ ስህተት ነው፡፡ ድርሻህን ተወጣ ድርሻህን ለመጠየቅ መብት ይኖርሃል፡፡

እና ምን ለማለት ነው እንኳን ጋዜጠኛ እኔ ተራ ዜጋው  የጠቅላይ ሚንስትሬን ደመወዝ ስንት እንደሆነ በፅኁፍ በአጭር ግዜ እንዲሰጠኝ የመጠየቅና የማግኘት መብት አለኝ፡፡

በዚህ ጽሑፍ ውስጥ ፁፉን ለማብራረት የገቡ ምሳሌዎች በወቅታዊነታቸው እንጅ ለኔ ባላቸው አንገብጋቢነት ብቻ እንዳልተመረጡ ይታወቅልኝ ፡፡