ቼክ በተግባር በሰፊው ከሚሰራባቸውና በሕግ ከተቀመጡት ንግድ ሰነዶች አንዱና ዋነኛው ነው፡፡  በቼክ ላይ እምነት የሚታጣበት ከሆነ የንግድ ዝውውር ደህንነት (security of transaction) ላይ ሊያሳድር የሚችለው ተፅዕኖ እጅግ ከፍተኛ ነው፡፡ የንግድ ሥራው እያደገ በመጣ ቁጥር በቼክ የሚደረጉ የንግድ ልውውጦች የሚጨምሩ እንደሚሆን የሚታመንና በተግባርም የሚታይ ነው፡፡ የቼክ ዝውውር እየጨረ እንደመጣም መገመት አያዳግትም፡፡ እየጨመረ የመጣውን የቼክን ዝውውር አስተማማኝነት ለማሳደግ ሕጎች ሥርዓቱን ሊቆጣጠሩት ይገባል፡፡ በዚህም መሠረት በእኛ ሀገር የንግድ ሕጉ እና የወንጀል ሕጉ ይህንኑ የቼክ ጉዳይ በዋናነት ይህን ሥርዓት ዘርግተው ይገኛሉ፡፡ ባብዛኛው የቼክ ጉዳይ የሚያከራክር ጉዳይ የሌለበት ቢሆንም አልፎ አልፎ ግን አከራካሪ ጉዳዮች መታየታቸው አልቀረም፡፡ ይህ ጽሑፍ ዓላማውም በቼክ ዙሪያ ያሉትን አስፈላጊ የሕግ ድንጋጌዎችንና አስገዳጅ የፍርድ ውሳኔዎችን ማሳወቅና በተወሰነ መልኩም ቢሆን ለአከራካሪ ጉዳዮች የጸሐፊውን እይታ ማንፀባረቅ ነው፡፡

ቼክ ምንድ ነው?

በንግድ ሕጉ ላይ የቼክ ዓይነቶች፡ የስርዝ ምልክት ያለበት ቼክ (crossed cheque)፣ ከሂሳብ ውስጥ የሚገባ ቼክ (cheques payable in account) እንዲሁም የመንገድ ቼክ(travellers cheque) የሚባሉ ሲኖሩ የዚህ ጽሑፍ ትኩረት ግን እነዚህን ወደ ጎን በመተው በንግድ ሕጉ ቁጥር 827 ጀምሮ የተቀመጠውን መደበኛ የቼክ ዓይነት ላይ ያተኩራል፡፡

ቼክ በንግድ ሕጉ መሠረት በሰፊው ጥቅም ላይ ከሚውሉ የንግድ ወረቀቶች (commercial instruments) አንዱ ሲሆን የንድግ ወረቀት ማለት ደግሞ በገንዘብ መከፈል የሚሆነውን ግዴታ የሚናገሩ የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶች ናቸው፡፡ የሚተላለፍ የገንዘብ ሰነድ (negotiable instruments) ማለት ደግሞ መብቱ ከሰነዱ ተለይቶ ሊሰራበት ወይም ሊተላለፍ የማይችል መብት ያለበት ሰነድ ሁሉ ማለት ነው (የንግድ ሕግ ቁጥር 715)፡፡ በዚህም መሠረት እንግዲህ ቼክ በቼኩ ላይ ያለን መብት ከቼኩ ተለይቶ ሊሰራበት ወይም ሊተላለፍ አይችልም ማለት ነው፡፡ ቼኩ አብሮ ካልተሰጠ በስተቀር ሌላኛው ወገን ያለበትን ግዴታ እንዲፈፅም አይገደድም ግዴታው ወይም መብቱ  ከቼኩ ጋር ተነጣጥሎ መተላለፍ አይችልም፡፡ የገንዘብ ሰነድ የሆነውን ቼክ ከፋይ ሊሆን የሚችለው ባንክ ወይም በሕግ እንደ ባንክ በታወቀ ባንድ ሥራ ማስኬጃ ብቻ ነው (የንግድ ሕጉ ቁጥር 829)፡፡ ስለዚህ ለምሳሌ ግለሰብ ባለኃብቶች ቼክን የመክፈል ሥራ ሊሰሩ አይችሉም ወይም በቼክ ላይ ከፋይ የሚለው ቦታ ላይ ስማቸው ሊሰፍር አይችሉም ማለት ነው፡፡ የገንዘብ ሰነድ የሆነው ቼክ ደግሞ ቼክ ነው ተብሎ ስለ ቼክ በተደነገገው የንግድ ሕግ ስር መብትና ግዴታ እንዲጥል ቼኩ ሊያሟላ የሚገባው መግለጫዎች ይኖራሉ፡፡

ቼክ ሊያሟላ የሚገባቸው አስፈላጊ መግለጫዎች ምንድ ናቸው?

አንድ ቼክ ሊያሟላ ይገባዋል ተብሎ በንድግ ሕጉ ላይ የተቀመጡ መግለጫዎች አሉ፡፡ እነዚህም

   1.የተወሰነ ገንዘብ ለመክፈል ሀተታ የሌለበት ትዕዛዝ፣

   2.መክፈል የሚገባው ከፋይ ስም (ባንክ ወይም በሕግ እንደ ባንክ የታወቀ ሌላ አካል ብቻ)

   3.ገንዘብ የሚከፈልበት ቦታ

   4.ቼኩ የወጣበት ቦታና ግዜ

   5.ቼኩን ያወጣው ሰው ፊርማ መሆናቸውን የንግድ ሕጉ ቁጥር 827 በግልፅ አስቀምጧል፡፡

በዚህም መሠረት አንድ ቼክ በቼኩ አማካይነት የሚከፈለውን ገንዘብ መጠን እንዲከፈል የሚል ትዕዛዝ ሊኖር ይገባል፡፡ የተወሰነ ገንዘብ ለመክፈል በዚህ መልኩ ትዕዛዝ የሌለው እንደሆነ ቼክ ሊባል አይችልም ማለት ነው፡፡ መክፈል የሚገባውን ከፋይ በተመለከተ ከፋይ ተብለው በቼክ ላይ ሊፃፉ የሚባገው ባንኮች ወይም በሕግ እንደ ባንክ የሚቆጠሩ የፋይናንስ ተቋማት ብቻ ናቸው (የንግድ ሕጉ ቁጥር 829)፡፡ ከነዚህ ውጭ የቼክ ከፋይ ሊኖር አይችልም፡፡ ገንዘብ የሚከፈልበት ቦታ በዚሁ መሠረት ሊቀመጥ ይገባዋል፡፡ ቼኩ የወጣበት ቦታና ግዜን በሚመለከት ቼኩ የወጣበት ቦታና ግዜን ያስቀምጣል፡፡ ቼኩ የሚወጣበት ቀንና ለክፍያ የሚቀርብበት ቀን አንድ ነው ወይስ ልዩነት አለው በሚለው ላይ ይህ ንዑስ አንቀፅ የሚጠቁመው ነገር ባይኖርም የንግድ ሕጉ ቁጥር 855 ግን ልዩነት ያላቸው ቀናት ሊሆኑ እንደሚችሉ ይጠቁማል፡፡ እዚህ ላይ ቼኩ ለክፍያ የሚቀርብበትን ቀን እንደ ዋና መግለጫ አለመወሰዱ ተገቢና ትክክል አይመስልም፡፡ ምክንያቱም ለክፍያ የሚቀርብበት ቀን የሌለው ቼክ ባዶ የሆነ ነገር ማለት ነው፤ ሕጉም እንዳስቀመጠው ቼኩ የወጣበት ቀን ከግምት ውስጥ ሳይገባ ነው ቼኩ ላይ ከተፃፈው ቀን ጀምሮ ለስድስት ወራት ተከፋይ የሚሆነው፡፡ ስለዚህ ቼኩ የወጣበት ቀን ከአከፋፈል ጋር በተያያዘ አስፈላጊ ጉዳይ አይደለም፡፡ ምናልባትም መሻሻል ካለባቸው የንግድ ሕጉ ድንጋጌዎች መኃል አንደኛው ይህ ሊሆን ይገባል፡፡ በተግባር እየተሰራበት ያለው ግን በቼኩ ላይ የሚፃፈው ቼኩ የወጣበት ቀን ሳይሆን ለክፍያ መቅረብ ያለበትን ቀን ነው፡፡ ሲጀመር በቼክ ላይ ሁለት ቀን መፃፊያ ቦታም የለውም (ለምሳሌ በወንጀል ጉዳይ ላይ ማስረጃ ሲቀርብ ቼኩ ለክፍያ መቅረብ ያለበትን ቀን በተመለከተ ከሌሎች ማስረጃዎች በተጨማሪ በዋናነት ቼኩ እራሱ ማስረጃ ሲሆን ቼኩ የወጣበትን ቀን በተመለከተ ግን የግል ተበዳይ (የሰው ምስክር) እና ሌሎች የሰው ምስክሮች ናቸው በዋናነት ይህንን ጉዳይ የሚያስረዱት ምክንያቱም ይህ ሁኔታ በቼኩ ላይ ስለማይፃፍ)፡፡ ሌላው ጉዳይ ቼኩን ያወጣው ሰው ፊርማ መኖር ይኖርበታል፡፡ ፊርማው ቼኩን ያወጣው ሰው ይሁን እንጂ ሌሎቹ ነገሮች ከላይ የቀረቡት በአውጪው እንዲፃፉ አያስገድድም፡፡ ሌላ ሰው ፅፎት አውጪው ከፈረመበት ቼኩ የተሟላ ነው ለማለት ይቻላል፡፡ ነገር ግን ፊርማው ከጽሑፎቹ በኋላ መሆን ይጠበቅበታል፡፡ ምክንያቱም በጽሑፎቹ፣ በገንዘብ መጠኑ ተስማምቻለሁ የሚል ኃሳብ ያዘለም ስለሚሆን፡፡ ነገር ግን ቼኩ ላይ ፊርማ ካረፈ በኃላ በቼኩ የሚፃፉ ጉዳዮች ፈራሚው ተስማምቷል ፋቅዳል ለማለት የማያስችል እና በቼክ ዙሪያ የሚደረግ ስምምነቶችም የውል ሕግ መሰረታዊ መርሆዎችን መጠበቅ ያለባቸው ስለሚሆንና በዚህ ሁኔታ ግን አውጪው ለዝርዝር የስምንምነቱ ሁኔታ ሙሉ ፈቃዱን ሰጥቷል ለማለት ስለማያስችል (የሰበር መዝገብ ቁጥር 20232 ቅፅ 7 ቼክ መሰረታዊ የውል ሕግ መርሆዎችን ሊያሟላ እንደሚገባ ያስቀምጣል) በሰነዱ ላይ በተቀመጡት ጉዳዮች ፈራሚው ይገደዳል ለማለት አያስችልም፡፡ ምንም እንኳን የተለየ ባህሪ ያለው ቢሆንም ይህንን በተመለከተ ሌሎች የውል ስምምነቶችንም ቢሆን ተዋዋዩ ወገን በራሱ ፃፋቸውም አልፃፋቸውም በውል ስምምነቱ ላይ በሙሉ ፈቃዱ የተፃፈውን ነገር አንብቦ ፊርማውን እስካኖረና ሌሎች ዝርዝር ሁኔታዎች እሰከተሟሉ ድረስ ውሎች የሕግ ያክል በተዋወዮቹ ላይ ገዢነት ይኖራቸዋል በተለየ በሕግ ላይ እራሱ እንዲፅፋቸው እስካልተደነገገ ድረስ፡፡ ቼክንም በግልፅ በሕጉ ላይ በተቃራኒ እንዲሆን እስካልተደነገገ ድረስ ይህንኑ አካሄድ መከተል የሚያስኬድ ይሆናል፡፡ ብዙ ግዜ ከሚነሱ መከራከሪያዎች አንዱም ይኸው ጉዳይ ነው፡፡ ስለሆንም ፅሁፉን ሌላ አካል (ለምሳሌ የተከፋዩን ስም) ፅፎት አውጪውም ፅሁፉን ተመልከቶ የፈረመ እንደሆነ አውጪው ፅሁፉን ስላልፃፈው አይገደድም ሊባል አይችልም፡፡

አስፈላጊ የሆኑ የቼክ መግለጫዎች ጉድለት የሚያስከትለው ውጤት ምንድ ነው?

በመርህ ደረጃ በንግድ ሕጉ ቁጥር 827 ላይ የተመለከቱት መግለጫዎች (አምስት መግለጫዎች) አንዱ እንኳን የሌለበት (የጎደለው) ሰነድ እንጂ እንደ ቼክ አይቆጠርም ይላል የንግድ ሕጉ ቁጥር 828፡፡ ነገር ግን ሁለት ልዩ ሁኔታዎች ደግሞ መኖራቸውን ሕጉ ያስቀምጣል፡፡ እነዚህም

  1. በልዩ የተመለከተ ቦታ ከሌለ በከፋዩ ስም አጠገብ የተጠቀሰው ቦታ የመክፈያ ቦታ ሆኖ ይቆጠራል፡፡ በከፋዩ ስም አጠገብ ብዙ ቦታዎች ተመልክተው እንደሆነ መጀመሪያ በተመለከተው ቦታ ቼኩ ተከፋይ ይሆናል፡፡
  2. እነዚህ ማመልከቻዎች ወይም ማናቸውም ሌላ ማመልከቻዎች ከሌሉ የከፋዩ ዋና ሥራ ማካሄጃ በሆነው ቦታ ቼኩ ተከፋይ ይሆናል፡፡ ስለዚህም በእነዚህ ሁለት ሁኔታዎች ካልሆነ በስተቀር አንድን ሰነድ ቼክ የሚያደርገው በንግድ ሕጉ ቁጥር 827 ስር የተዘረዘሩት አስፈላጊ ሁኔታዎች መሟላታቸው ነው፡፡ በዚህ አንቀፅ ስር  ከተቀመጡት አንዱ እንኳን ቢጎድል ሰነድ እንጂ ቼክ እንደማይባል ይህንንም ተከትሎ ቼክን በተመለከተ የተሰጠን መብትና ግዴታ ለመጠቀም የማያስችልና በሌሎች የሕግ ክፍሎች በተቀመጡት ድንጋጌዎች ብቻ መብትና ግዴታ ሊገኝ እንደሚችል ያመላክታል፡፡ ስለዚህም የቼክ ተከፋይ (payee) በቼክ ሲገበያይ ማድረግ ከሚገባው መሰረታዊ ነገሮች አንዱና ዋነኛው ካለይ የጠቀስናቸውን ዋና ዋና መግለጫዎች መሟላታቸውን ማረጋገጥ ይጠይቃል፡፡ የአንዱ መግለጫ ጉድለት ቼኩን እንደ ቼክ ዋጋ ሊያሳጣውና ሰነድ ብቻ ሊያደርገው ይችላል፡፡ ሰነድ ከተባለ ሌሎች ችግሮች እንደተጠበቁ ሆነው ከፋዩ እንዲከፍል አይገገድም፡፡ ከፋዩ እንዲከፍል የሚገደደው ቼክ ከሆነ ብቻ ነው፡፡ የቼክ ሁኔታዎችን አሟልቶ ከፋዩ ክፍያ እንዳይፈፅም የሚያስገድድ ምክንያት በሌለበት አልከፍልም ቢል ባለመክፈሉ ለሚደርሰው ጉዳት ኪሳራ እንዲከፍል ይገደዳል፡፡ በቅን ልቦና፣ አስፈላጊውን ጥንቃቄ አድርጎ፣ የተለመደውን አሰራር ተከትሎ እና ተቃራኒ መረጃ ሳይደርሰው ለሚፈፅመው የቼክ ክፍያ በሚደርስ ጉዳት ከፋዩ ከተጠያቂነት ነፃ ነው(የንግድ ሕግ ቁጥር 861)፡፡

የቼክ አውጪው ዋና ዋና ሃላፊነቶች ምንድ ናቸው?

የቼክ አውጪው ዋናው ግዴታው ለቼኩ አከፋፈል የሚሆን የገንዘብ ስንቅ አስቀድሞ በሂሳቡ ውስጥ እንዲኖር ሲሆን ይህም ማለት አውጪው(the drawer) ለራሱ ተቀማጭ በከፋዩ ዘንድ(payer) ያለውና በግልፅ ወይም በዝምታ ባንድ ስምምነት መሠረት አውጪው ገንዘቡን በቼክ እንዲያዝበት መብት ያለው መሆኑን ማረጋገጥ ይጠበቅበታል(የንግድ ሕጉ ቁጥር 830)፡፡ በቂ ስንቅ መኖሩን ማረጋገጥ ያለበት ቼኩ ከወጣበት ጀምሮ ለክፍያ እስከሚቀርብ ድረስ ነው፡፡ ይህን መተላለፍም በወንጀል ጭምር የሚያስቀጣ ነው(የወንጀል ሕግ 693)፡፡ ነገር ግን በቼኩ ውስጥ ሂሳብ አለመኖሩ የቼኩን ዋጋ የሚያሳጣ አይሆንም ይልቁንም በፍትሐብሔርም በወንጀልም ተጠያቂነትን ያስከተላል፡፡ ባጠቃላይም አውጪው ለቼኩ አከፋፈል ዋስ ነው፤ከዚህ ዋስትና ኃላፊነት የሚያድነው ስምምነት መፈፀም በሕግ የተከለከለ ነው ቼኩ ላይ የዛን ዓይነት ነገር ሰፍሮም ከሆነ እንዳልተፃፈ ይቆጠራል(የንግድ ሕግ ቁጥር 840)፡፡ የመዋዋል ነፃነት(freedom of contract) የቼክ ዋስትና ግዴታን በተመለከተ የማይሰራ ጉዳይ ይሆናል፡፡ በዚህ ዙሪያ ስምምነት ቢደረግም በሕግ ተቀባይነት የለውም የሚል ሀሳብ ያለው ነው፡፡

ቼክ ወጪ የተደረገበትና ለክፍያ የሚቀርብበት ቀናት ሊለያዩ ይችላሉ ወይ?

አስፈላጊ ስለሆኑት የቼክ መግለጫዎች የሚያትተው የንግድ ሕጉ ቁጥር 827 ይህንን በተመለከተ ምንም ያለው ነገር ባይኖርም የንግድ ሕጉ ቁጥር 855 ግን ጠቋሚ ነገር ያስቀምጣል፡፡ ቼኩ የወጣበት ቀን ከግምት ውስጥ ሳይገባ በቼኩ ላይ ከተፃፈው ቀን አንስቶ በሚከተሉት ስድስት ወራት ውሰጥ እንዲከፈልበት መቅረብ አለበት የሚለው የሕጉ ድንጋጌ ቼኩ ወጪ የሚደረግበትና ለክፍያ እንዲቀርብ የሚፃፈው ቀን ሊለያዩ እንደሚችሉ የሚጠቁም አንቀፅ ነው፡፡ ስለዚህም አውጪው ከቅን ልቦና ውጪ የተከፋዩን ጥቅም ለመጉዳት አስቦ ለክፍያ የሚቀርብበት ግዜው እንዲያልፍበት (ማለትም ለክፍያ መቅረብ ያለበትን ግዜ ከ 6 ወር ወደኃላ በማድረግ) አስቦ ካልተደረገ በስተቀር የክፍያ ቀኑን ከሚወጣበት(date of issuance) የመከፈያ ቀኑን ወደኃላ ማድረግም(pre-date) ወይም ወደ ፊት(post-date) ማድረግ ይቻላል ይህን በመደረጉ ምክንያት ቼኩም ዋጋ አያጣም ማለት ነው፡፡ ቼኩ እንደ ቼክ  ዋጋ የሚያጣው አውጪው ቼኩ ከወጣበት  6 ወር ለበለጠ ግዜ ወደ ኃላ እንዲከፈል አድርጎ ቼኩ ላይ ከተፃፈ ሊከፈል ከሚገባው ቀን አንስቶ 6 ወር ያለፈው ቼክ ስለማይከፈል ቼኩ ዋጋ አይኖረውም ማለት ነው፡፡ እንዲህ ዐይነት ሁኔታ የሚጋጥመው ተከፋይ በሌሎች የሕግ ክፍሎች በተቀመጡት መብት ማስከበሪያ መንገዶች መብቱን ሊያስከብር ይገደዳል፡፡ የንግድ ሕጉ ቁጥር 789 እንደሚያስቀምጠውም የቼኩ ተከፋይ በፍትሐብሔር ሕጉ ላይ በተደነገገው አላግባብ ስለመበልፀግ የተቀመጠውን ድንጋጌ ተከትሎ የፍትሐብሔር መብቱን ሊያስከብር ይችላል፡፡ በወንጀል ሆን ተብሎ ከቅን ልቦና ውጭ የተደረጉ እስከሆኑ ድረስ የቼክ ወንጀልን(የወንጀል ሕግ 693/1) ባያያቋቁሙም በወንጀል ሕግ አንቀፅ 692 ስር በተደነነገገው የማታለል ወንጀል ሊያስጠይቅ የሚችል ስለሆነ ይህንኑ ወደ ፖሊስ ጣቢያ በመሄድ ማመልከት ያስፈልጋል፡፡ ሆነ ተብሎ ተደርጓል አልተደረገም የሚለው ከአጠቃላይ ድርጊት አፈፃፀሙ ጋር ተስተያይቶ የሚረጋገት(infer የሚደረግ) ጉዳይ ነው፡፡

የሌሎች ሀገራት የቼክ ሕግጋትና አሠራር ከኢትዮጰያ ሕግና አሠራር ጋር በንፅፅር

ካናዳ

ካናዳ በዓለማችን ላይ ካሉ ውጤታማ ቼክ የማጥራት ሥርዓት (efficient cheque clearing system) ካላቸው ሀገራ መካከል አንዷ ናት፡፡ ምንም እንኳን የኤሌክትሮኒክስና የካርድ ክፍያዎች ሥርዓት መስፋፋት የቼክ አጠቃቀሟን እየቀነሰ ቢመጣም አሁንም ድረስ ግን እሰከ 1 ቢሊዮን ቼክ በዓመት የማዘዋወርና የመገበያየት ሥራ ይሰራበታል፡፡ በካናዳ ቼክ አውጪው ላወጣው ቼክ በቂ ስንቅ ሳይኖረው ሲቀር ባንኩ ለተፋዩ ክፍያ ሊፈፅም ይችላል፡፡ ከዛ በኃላ ግን ያንን ላደረገበት ተጨማሪ ክፍያ ወይም (non sufficient fund fee(nsff)) ከአውጪው ያስከፍላል፡፡ አውጪው በቂ ሂሳብ እንዲኖረው ማረጋገጥ ያለበት ተጨማሪ ክፍያዋን(nsf fee) ላለመክፈልም ሲል ጭምር  ነው፡፡ የዚህን ዐይነት አሰራር በኢትዮጵያ ባንኮች አይሰራበትም የሕግ ድጋፍም የለውም፡፡ ሌላው በካናዳ ወደ ፊት ለክፍያ እንዲቀርቡ(post-dated cheques) ቀድሞ ሊከፈል የሚችልበት አሰራርም አለ፡፡ ይህም ኢትዮጵያ ውስጥ እንዲከፈል ከተፃፈበት ቀን በፊት የመክፈል በሕግ የተቀመጠም ነገር የለም የዚህን ዓይነት አሰራርም ባንኮች አይከተሉም፡፡ ምናልባትም የንግድ ሕጉ ቁጥር 899 ካለው በላይ ማውጣት ስለመከልከሉ በሚለው አንቀፅ ስር “ገንዘቡን በአደራ የማስቀመጥ ውል ካለው ከተቀማጭ ገንዘብ በላይ የማውጣት መብትን አይሰጥም” በማለት አውጪው በሂሳብ ውስጥ ካለው በላይ ገንዘብን ቢያዝ ሊያወጣ እንደማይችል ጠቋሚ ይመስላል፡፡ የሁለቱ ጉዳዮች ልዩነት የመጣው በካናዳ ካለው ጠንካራ የፋይናስ ሥርዓት እና ኢትዮጵያ ውስጥ ደግሞ ገና በማደግ ላይ የሚገኝ የፋይናነስ ሥራዓት መኖሩ አንደኛው ምክንያት ሊሆን ይችላል፡፡

ታይላንድ

በታይላንድ በቂ ሂሳብ ሳይኖር ቼክ ማውጣት በወንጀል የሚያስጠይቅ ሲሆን የቅጣት መጠኑ ግን ኢትዮጵያ ውስጥ ካለው ያነሰ ነው፡፡ በዚህም የወንጀል ድርጊት አውጪው ሊቀጣ የሚቸለው 1 አመት ባልበለጠ እሥራት እና አስከ 60 ሺህ የታይላንድ ባህትሰ (bahts) ባልበለጠ የገንዘብ መቀጮ ያስቀጣል ይላል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ታስቦ የሚፈፀም በቂ ሂሳብ ሳይኖር ቼክ ማውጣት በቀላል እሥራት ወይም እንደነገሩ ከባድነት እስከ 10 አመት በሚደርስ ፅኑ እሥራትና በመቀጮ ሊያስቀጣ ይችላል፤ በቸልተኝነት ሲሆን ደግሞ በመቀጮ ወይም 1 አመት በማይበልጥ ቀላል እሥራት ያስቀጣል፡፡ የቅጣት ሁኔታ  በዛች ሀገር ላይ ያለውን የወንጀሉን ተፅዕኖ እንዲሁም የቅጣቱ አስተማሪነት እንደ ሀገሪቱ ሁኔታ ግምት ውስጥ ገብቶ ስለሚጣል ልዩነቱ መኖሩ አስገራሚ ላይሆን ይችላል፡፡ ሌላው ልዩነት የወንጀል ህጋችን ቼኩ በሚወጣበት ወይም ለክፍያ በሚቀርብበት ግዜ የሚያዝበት በቂ ገንዘብ ከሌለው የወንጀል ተጠያቂነት እንዳለ ሲያስቀምጥ ታይላንድ ለክፍያ በሚቀርብበት ብቻ የሚለውን ነው የሚያስቀምጠው፡፡ በዚህ ረገድ የእኛ የወንጀል ሕግ ክፍተቶችን በመዝጋት ረገድ የተሻለ ነው ለማለት ይቻላል፡፡ ምክንያቱም አንድ አንድ ግዜ ሂሳቡ ወጪ በሚሆንበት ሰዓት ሂሳብ ላስገባ ስል ሂሳቤ ተዘግቷል ተባልኩኝ የሚል መከራከሪያን ዝግ ያደርጋል፡፡ ይህን ማድረጉም የቼክ ክፍያ የግብይት ደህንነትን(security of transaction) ያጠናክረዋል፡፡ ቼክ አውጪዎችም የሕግ ቀዳዳ በመፈለግ ለማምለጥ የሚያደርጉትን ጥረት ዝግ በማድረግ ስለ ቼኩ አከፋፈል በቂ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ያደርጋቸዋል፡፡

ቼክ ከወንጀል ጋር በተያያዘ

ከወንጀል ጋር በተያያዘ በቼክ ወንጀል ስለመፈፀም የሚደነግገው የሕግ አንቀፅ  ማታለልን ያካተቱ ወንጀሎች ከሚለው ክፍል ስር ሲሆን የወንጀል ሕግ አንቀፅ 693/1 “ማንም ሰው ቼክ በሚወጣበት ወይም ቼኩ ለባንክ  በሚቀርብበት ጊዜ የሚያዝበት በቂ ገንዘብ አለመኖሩን እያወቀ ቼክ ያወጣ/የሰጠ/ እንደሆነ በቀላል እሥራት ወይም እንደነገሩ ከባድነት ከ10 አመት በማይበልጥ  ፅኑ እሥራትና  በመቀጮ  ይቀጣል” በማለት ያስቀምጣል፡፡ ሁለት ዋና ዋና ጉዳዮች በዚህ አንቀፅ ውስጥ ማውጣት እንችላለን፡፡ የመጀመሪያው ቼኩ ለክፍያ ሊቀርብ ከሚችልበት ግዜ(ምክያቱም ከዛ በፊት ወደ ፊት እንዲከፈል የተሰጠን ቼክ በተመለከተ ክፍያ መጠየቅ የሚያስችል ሕግም አሰራርም ስለሌለ ማለት ነው) ጀምሮ ለባንክ ለክፍያ እስከሚቀርብበት ግዜ ድረስ በባንክ ሂሳብ ውሰጥ በቼኩ ላይ ለተፃፈው ገንዘብ ክፍያ የሚሆን በቂ ሂሳብ መኖሩን ማረጋገጥ አለበት፡፡ ስለዚህ ለምሳሌ ተከፋዩ ቼኩ ለክፍያ መቅረብ ካለበት ግዜ 5 ወር እንኳን ዘግይቶ ቢሄድ በዚህ የወንጀል ሕግ ድንጋጌ መሠረት አምስተኛው ወር ቢሆንም አውጪው ሂሳብ ውሰጥ ለቼኩ ክፍያ የሚሆን በቂ ሂሳብ ሊኖረው ይገባል፡፡ ይህ ሳይሆን የቀረ እንደሆነ ግን የወንጀል ሕጉ ደንጋጌ ተፈፃሚ ይሆናል ማለት ነው፡፡ ሁለተኛው ጉዳይ ፍርድ ቤት ቅጣቱን በመወሰን ረገድ ሁለት አመራጭ ያለው መሆኑ ነው፡፡ በዚህም መሠረት ጉዳዩ ከባድ አይደለም በማለት የሚወስድ እንደሆነ በቀላል እሥራት  ማለትም ከ10 ቀን አስከ 3 ዓመት ሊደርስ በሚችል እሥራት ቅጣት ሊጥል ይችላል ማለት ሲሆን ነገሩን ከባድ ነው ብሎ የወሰደው እንደሆነ ግን ከ 10 አመት በማይበልጥ ፅኑ እሥራት ብቻ ሳይሆን በመቀጮም ጭምር የሚያስቀጣ ይሆናል፡፡ ዝርዝር የቅጣት ሁኔታውም ተሻሽሎ በወጣው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ 2/2006 መሠረት የሚወሰን ይሆናል፡፡ አንድ አንድ ግዜ ፍርድ ቤቱ የቀላል እሥራት አማራጭ ይወስድና የቅጣት አወሳሰን መመሪያው ላይ ግን የገንዘብ መጠኑ ግምት ውስጥ ገብቶ ሲታይ ቅጣቱ በገንዘብም ጭምር እንዲሆን የሚያስመስል ቢሆንም መመሪያ ሕግን ሊጥስ አይችልምና ቀላል እሥራት አማራጭ ከገንዘብ መቀጮ ጋር አብሮ ሊወሰን ስለማይችል መመሪያው የሚያስቀምጠውን የገንዘብ መቀጮ ወደ ጎን መተው ተገቢ ይሆናል፡፡ ባጭሩም ቀላል እሥራት ከሆነ እሥራቱ ብቻውን ነው የፅኑ እሥራት አማራጭ ከሆነ ግን እሥራቱ ከመቀጮ ጋር ነው ማለት ነው፡፡

ከወንጀል ጋር በተገናኘ መነሳት ካለባቸው መሰረታዊ ነጥቦች መካከል በወንጀል ሕጉ አንቀፅ 693 ስር ተጠያቂ ለመሆን በመጀመሪያ ቼኩ በንግድ ሕጉ ላይ የተቀመጠውን አስፈላጊ የሆኑ የቼክ መግለጫዎች ያሟላ መሆን ይጠበቅበታል፡፡ ለምሳሌ የገንዘብ መጠኑ ባልተጠቀሰ፣አውጪው የራሱ የሆነ ፊርማውን ካላሳረፈበትና የመሳሰሉትን ያላሟላ ከሆነ ቼክ ነው ተብሎ በቂ ሂሳብ አለው የለውም ወደሚል ሁኔታ ውስጥ ሊገባበት አይችልም፣አይገባምም፡፡ የወንጀል ሕጉም ከቼክ ጋር በተገናኘ ተጠያቂነትን በቂ ሂሳብ ከመኖርና ካለመኖር ጋር ነው ያያዘው፡፡ በዚህ ሁኔታ የሚፈፀም ወንጀልም ካለ በንግድ ሕጉ ድንጋጌ መሠረት በሰነድ የተፈፀመ ወንጀል እንጂ በቼክ ላይ የተፈፀመ ሊባል አይችልም(የንግድ ሕጉን ቁጥር 828 መመልከት ይቻላል)፡፡ ይልቁንም በዚህን ግዜ ሌሎች የወንጀል ሕግ ድንጋጌዎችን ለምሳሌ የማታለል ወንጀልን የሚያቋቁሙበት አጋጣሚ ሊፈጠር ይችላል፡፡

ሌላው ትልቁ ጉዳይ የወንጀል ሕጉን አንቀፅ 693ን ለማቋቋም ድርጊቱ የማታለል ሁኔታን ያካተተ መሆን ይኖርበታል ወይ?ይህንን ጥያቄ እንድናነሳ የሚያደርገን አንቀፅ 693 ማታለልን ያካተቱ ወንጀሎች ከሚል ክፍል ስር መካከተቱ ነው፡፡ በእኔ በኩል የማታለል ጉዳይ ግን መኖር የለበትም የሚል አቋም አለኝ፡፡ ምክንያት በዚሁ የማታለል ወንጀሎችን የሚመለከቱ ወንጀሎች ከሚለው ክፍል ስር ከሚገኙ የወንጀል ድንጋጌዎች መካከል የማታለል ይዘት የሌላቸው ወንጀሎች መኖራቸው ለምሳሌም በአንቀፅ 702(1) እና (2) ላይ የተደነገገው በሌላ ሰው ጥቅም የሥራ አመራር ላይ የተፈፀመ ጉዳት የሚለው የወንጀል ድርጊት በውስጣቸው የማታለል ድርጊት የሚይዙ አንቀፆች አይደሉም፡፡ ሌላኛው ምክንያት ወደኃላ ላይ በዝርዝር የምናነሳው የሰበር ውሳኔ መዝገብ ቁጥር 67947 ቅፅ 12 የቼክ ወንጀልን ለማቋቋም ምንም ዓይነት ቅድመ ሁኔታ የማያስፈልግ መሆኑን የወሰነበት መዝገብ መኖሩ ነው፡፡ በዚህም አጋጣሚ የወንጀል ሕጉ ድራፍት የተደረገበት መንገድ ላይም ጥያቄ የሚያስነሳ ነው፡፡ የማታለል ጉዳይን ያልያዙ ወንጀሎችን ማታለልን ያካተቱ ወንጀሎች በሚል የሕግ ክፍል ስር ማካተት የድራፍቲንግ(poor draftsmanship) ችግር ነው፡፡ በቼክ የሚፈፀም ወንጀል የማታለል ይዘት ሊኖረው ይገባል ከተባለ ብዙ ልዩነቶችን ያመጣል፡፡ ለምሳሌ አንድ ቼክ ወጪ በሚደረግበት ወይም ለክፍያ በሚቀርብበት ቀን አውጪው ለተካፋዩ በሂሳብ ውስጥ በቂ ሂሳብ እንደማይኖረው ነገር ግን ለመተማመኛ ብቻ ብሎ የሰጠው እንደሆነ በዚህ ሁኔታ የማታለል ጉዳይ ስለሌለው በሂሳብ ውስጥ በቂ ስንቅ የለውም እንኳን ቢባል በአንቀፅ 693 ስር የወንጀል ተጠያቂ ለማድረግ አያስችልም ማለት ነው፡፡ የሕጉ ዓላማ ደግሞ የቼክ ዝውውር አስተማማኝ ሆኖ ዝውውሩ የተቀላጠፈ እንዲሆን  ከማሰብ  አንፃር ስለሆነ ከላይ ባቀረብነው መከራከሪያ ነጥብም ምክንያት የግድ የማታለል ጉዳይ ሊኖረው አይገባም፡፡ የንግድ ሕጉም በዚህ ረገድ የሚያስቀምጠው ነገር ወደ ፊት እንዲከፈል ከወጣ ቼክ ውጪ ቼክ እንደ ቀረበ የሚከፈልበት ነው(የንግድ ሕጉ ቁጥር 854 እና 855)(other than post dated cheques, cheques are always payable at sight)፡፡ ስለዚህ ቼክ እንዲከፈል በተፃፈበት ቀን ጀምሮ እንደቀረበ እንዲከል(payable at sight) የሚያስፈልገው የገንዘብ ሰነድ ነው፡፡ የወንጀል ሕጉም ዓላማ በዚሁ አተያይ ስር መተርጎምና መታየት ይኖርበታል፡፡

የሚስተዋሉ ዋና ዋና ችግሮች ምንድ ናቸው?

ከቼክ ጋር በተገናኘ የሚነሱ አንድ አንድ ችግሮች አሉ፡፡ ከሚነሱት የሕግ እና የአሰራር ችግሮች መኃል ከላይ የተነካኩና የጸሐፊው ሀሳቦችም ጭምር ተገልጧል፡፡ የቀሩትን በችግርነት ሊጠቀሱ የሚችሉ ነጥቦች ደግሞ አሁን እናነሳለን፡፡

1.     ቼክን ለክፍያ እንዲቀርብ ሳይሆን ለዋስትና ወይም እንደመተማመኛ ነው የሰጠሁት የሚል መከራከሪያ ይነሳል በተለይም በወንጀል ጉዳይ ተጠያቂ ላለመሆን የሚነሳ ጥያቄ ነው፡፡ ከላይ ባነሳነው መከራከሪያ ነጥብ መሠረት የወንጀል ሕጉ አንቀፅ 693 የማታለል ይዘት በድርጊት ውስጥ መኖሩ መረጋገጥ አስፈላጊ አይሆንም ባልነው መሠረት ቼኩ ለተከፋዩ የተሰጠው እንደዋስትና እንኳን ቢሆን በሂሳብ ውሰጥ በቂ ሂሳብ እስከሌለው ድረስ የወንጀል ተጠያቂነት ማስቀረት አይችልም፡፡ የማታለል ጉዳይ በዚህ ግንኙነት መኖሩ ግድ ነው የሚባል ከሆነ ግን የዚህን ዓይነት መከራከሪያዎች ሚዛን የሚደፉ ይሆናሉ፡፡ ነገር ግን የሰበር መዝገብ ቁጥር 67947 ያለምንም ቅድመ ሁኔታ በሂሳብ ውስጥ በቂ ሂሳብ ከሌለ የወንጀል ተጠያቂነት እንደሚያስከትል አስቀጧል፡፡ ዝርዝር ጉዳዩን ወደታች እንመለከተዋለን፡፡

2.    ሌላው መከራከሪያ ጉዳይ በቂ ሂሳብ ሳይኖር ቼክ ወጪ ከተደረገ በኃላ ባንኩ የአውጪውን የቼኩ ሂሳብ መዝጋት፡፡ በብሔራዊ ባንክ መመሪያ መሠረት ለ 3 ግዜ በቂ ሂሳብ ሳይኖረው ቼክ የፃፈ ግለሰብ በባንኩ ሂሳቡ እንደሚዘጋበት ያስቀምጣል፡፡ ሁለት መሰረታዊ ልዩነቶችን ግልፅ እናድርግ፡፡ የመጀመሪያው ሂሳቡ በባንኩ የተዘጋው ቼኩን አውጪው ከመስጠቱ በፊት እና ሂሳቡ ከመዘጋቱ በፊት የተሠጠ ቼክ ብለን ለሁለት ከፍለን ማየት እንችላለን፡፡ የመጀመሪያውን ሁኔታ ለሁለት በድጋሜ ከፋፍሎ ማየት ነገሩን የበለጠ ግልፅ ያደርገዋል፡፡ በዚህም መሠረት ቼኩ ቀድሞ ስለመዘጋቱ በባንኩ ለአውጪው የተነገረና በባንኩ ያልተነገረበት ሁኔታዎች ይኖራሉ፡፡ ሁለተኛውን ሁኔታም በድጋሜ ለሁለት ከፍለን ማየት እንችላለን፡፡ በዚህም መሠረት ለክፍያ ቼኩ በሚቀርብበት ግዜ በቂ ሂሳብ በአካውንቱ የነበረውና ያልነበረው ተብሎ ለሁለት ከፍሎ ማየት ይቻላል፡፡ የመጀመሪያውን ሁኔታ ማለትም ቼኩ ወጪ የሆነው ቼኩ ከተዘጋ በኃላ ሲሆንና ባንኩም ለአውጪው ቼኩ መዘጋቱን የገለፀለት እንደሆነ ክፍያ ሊፈፀም የማይችልበት ሰነድ ነው የሰጠው ማለት ይቻላል፡፡ በዚህ ሁኔታም በድርጊቱ ውስጥ የወንጀል ተግባር መፈፀሙም ግልፅ ይሆናል፡፡ የተፈፀመው ወንጀል ግን አንቀፅ 692 የመታለል ወንጀል ነው፡፡ ምክያቱም ክፍያ ሊፈፀም እንደማይችልና ችኩ መዘጋቱን በመደበቅ ነው ቼኩን ፅፎ የሰጠው፡፡ ከባንኩ ጋር ያለው ስምምነት የተቋረጠ ስለሆነ ክፍያ መጠየቅ አይቻልም፡፡ ለሌላኛው እና አከራካሪው ጉዳይ ቼኩ መዘጋቱ ሳይገለፅለት ሂሳቡ ከተዘጋ በኃላ ቼክ ፅፎ የሰጠ እንደሆነ ምን ይከሰታል?በወንጀልስ ተጠያቂነት አለበት ወይ?የሚሉት ጥያቄዎች መመለስ በተወሰነ መልኩም ቢሆን አስቸጋሪነት አለው፡፡ የወንጀል ተጠያቂነትን ለማስከተል እውቀት ወይም የጥንቃቄ ጉድለት(ቸልተኝነት)ይጠይቃል፡፡ ገንዘብ እንዳያስገባ ሂሳቡ ተዘግቷል በዚህ ሁኔታ አከራካሪና አጠራጣሪ ሁኔታ መፈጠሩን ማየት ይቻላል፡፡ በዚህ ሁኔታ ደግሞ ወደ ተከሳሽ ማድላት እንደሚኖርብን የወንጀል ሕግ አንደኛው መርህ ስለሆነ በወንጀል ጥፋተኛ ወዳለማድረጉ ማድላት ይኖርብናል ማለት ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ነው ባንኮች የቼክ ሂሳብ ሲዘጉ የማሳወቅ አሰራርን የሚከተሉት፡፡ የማያሳውቁ ከሆነ ግን እራሱን የቻለ መከራከሪያ ነጥብ ሊሆን ይችላል ማለት ነው፡፡ በሁለተኛው ሁኔታ ግን ሂሳቡ የተዘጋው ቼኩ ወጪ ከሆነ በኃላ ከሆነ የማታለል ጉዳይ ለማቋቋም ያስቸግራል፡፡ በዚህ ሁኔታ መሆን የሚኖርበት ሂሳቡ በሚዘጋ ወቅት በቂ ሂሳብ ነበረው ወይስ አልነበረውም የሚለው ነጥብ ነው፡፡ በሂሳቡ ውስጥ በቂ ሂሳብ ካልነበረው አንቀፅ 693 ስር የወንጀል ተጠያቂነት ሊኖር ይገባል፡፡ ምክንያቱም ቼኩ በቂ ሂሳብ እንዲኖረው የሚያስፈልገው ቼኩ ወጪ በሆነበት ወይም ለክፍያ በሚቀርብበት ግዜ ስለሆነ ወጪ ከተደረገ በኃላ በቂ ሂሳብ እንደሌለው የሚያሳይ ስለሚሆን የወንጀል ተጠያቂነት ሊኖር ይገባል፡፡ ነገር ግን በሂሳቡ ውስጥ ሂሳቡ ሲዘጋ የነበረው ገንዘብ መጠን በቼኩ ላይ የተፃፈውን ለመሸፈን የሚያስችል ከሆነ ይህንን ቼክ በተመለከተ አውጪው በወንጀል ሊጠየቅ አይገባም፡፡ ምክያቱም የማታለል ጉዳይ የሌለበትና(አንቀፅ 692)የወንጀል ተጠያቂነትን የሚያስከትለው በቂ ሂሳብ በሂሳብ ውስጥ ያለመኖር ስለሆነ(አንቀፅ 693/1/ን በተመለከተ)፡፡ በዚህም አጋጣሚ ቼክ የፃፈና ሂሳቡ ግን ከባንክ ባለመከፈሉ ምክንያት የወንጀል ተጠያቂነት ያለ ቢሆንም ሁልግዜም ያለመሆኑን ያስገነዝባል፡፡ ይህ ማለት ግን የፍትሐብሔር ተጠያቂነትን በምንም መንገድ አያስቀርም(ያላግባብ ስለመበልፀግ በተደነገጉት የሕግ አንቀፆች መሠረት)፡፡

3.    በቂ ሂሳብ እያለ ቼኩ ከተሰጠ በኃላ ለክፍያ ከመቅረቡ በፊት ቼኩን ማሳገድ፡፡ የንግድ ሕጉ አንቀፅ 857 ቼኩ ከመከፈሉ አስቀድሞ አውጪው እንዳትከፍል ብሎ የነገረው እንደሆነ ባንኩ የቼኩን ዋጋ አልከፍልም ለማለት ይችላል ብሎ በማስቀመጥ ይህንን መብት አድርጎ አስቀምጦታል፡፡ ከንግድ ሕጉ መረዳት እንደሚቻለው እንዳትከፍል ብሎ ለማዘዝ የተቀመጠ ቅድመ ሁኔታ እንኳን የለም፡፡ ይህንን በማድረጉ የወንጀል ተጠያቂነት ሊኖር ይችላል ብሎ መከራከር አይቻልም፡፡ በቂ ሂሳብ ሳይኖር ቼኩን ያሳገደው እንደሆነ ግን ቼኩ ለክፍያ በሚቀርብ ግዜ ብቻ ሳይሆን ወጪ ሲሆንም ጭምር በቂ ሂሳብ እንዲኖረው ስለሚያስፈልግ ይህ እንዳልነበረ የተረጋገጠ እንደሆነ ግን በወንጀል ሕጉ አንቀፅ 693 መሠረት ተጠያቂ ሊሆን ይገባል ማለት ነው፡፡

4.    ቅጣትን በተመለከተ በባንክ ሂሳቤ ውስጥ ያለኝ ገንዘብ ቼኩ ላይ ከተፃፈው ገንዘብ ጋር ሲነፃፀር  በጣም አነስተኛ ጉድለት ስለሆነ በልዩነቱ ልክ ነው መቀጣት ያለብኝ የሚል መከራከሪያ(ቅጣት ሲጣል በቅጣት አወሳሰን መመሪያው መሠረት የገንዘብ መጠንን ግምት ውስጥ አስገብቶ መጣል ስላለበት)፡፡ ይህንን በተመለከተ የገንዘብ መጠንን መሠረት በማድረግ ቅጣት እርከን እንደሚወሰን የቅጣት አወሳሰን መመሪያ ቁጥር 2/2006 ያመላክታል፡፡ ይህን ጥያቄ ለመፍታት በዋናነት መመሪያውን መጠቀም ይኖርብናል፡፡ በዚህም መሠረት መመሪያው በየትኛውም ድንጋጌው ላይ በቼኩ ላይ ስለተጠቀሰው ሂሳብ እንጂ ስለልዩነቱ የሚናገረው ነገር የለም፡፡ ሕጉንና መመሪያውን መሠረት በማድረግ ስለሚሰራና በሕጉም ላይ ሆነ መመሪያው ላይ ይህን የሚፈቅድ አሰራር ስለሌለ የዚህን ዓይነት ጥያቄ የሕግ መሠረት የለውም ተብሎ ሊታለፍ ይችላል፡፡

5.    አጠቃላይ ቼኩ ላይ ያለው እና የተፃፈው ነገር ከፊርማው ውጭ የእኔ ስላልሆነ ቼኩ አያስገድደኝም በወንጀልም አልጠየቅም የሚል መከራከሪያ፡፡ የንግድ ሕጉ አንቀፅ 827 ላይ ከተዘረዘሩት ውስጥ ቼኩን ያወጣው ሰው ፊርማ ከሚለው በስተቀር ሌሎቹን አውጪው እራሱ እንዲፅፋቸው የሚያስገድድ አይደለም፡፡ ስለዚህ ሌላ ሰው ሌሎቹን ነገሮች ፅፎለት ከተመለከተ በኃላ ፊርማውን ካኖረ በተፃፈው ነገር ተስማምቷል ሕጉም ሌሎቹን ፅሁፎች እራሱ እንዲፅፍ ስለማያስገድዱ በቼኩ በፍትሐብሔርም ሆነ በወንጀል ተጠያቂነት ሊኖርበት ይገባል፡፡ ነገር ግን ማስተዋል ያለብን በሌላ በኩል አውጪው በቼኩ ላይ ፊርማ ብቻ አኑሮ ለሌላ ሰው ከሰጠው ሰነድ እንጂ እንደ ቼክ እንደማይቆጠር ሕጉ ያስቀምጣል፡፡ ስለዚህ በዚህ ሁኔታ ቼክ ተብሎ ለመጠየቅ ያስቸግራል፡፡ ስለዚህ ፅሁፉን ማንም ይፃው ማን ዋናው ነገር አውጪው የተፃፈውን ነገር ተመልክቶ ፊርማውን ማኖሩ ነው፡፡ ፊርማ ብቻ ያለበት ቼክ ለተከፋዩ ቢሰጥና ተከፋዩ የመሰለውን ነገር ቢሞላበት የተሟላ ቼክ ነው ለማለት አይቻልም፡፡ ከዚሁ ጋር በተገናኛ ፊርማው የእኔ አይደለም የሚል መከራከሪያም ይነሳል፡፡ በዚህ ሁኔታ ምንም አያከራክርም አውጪው ፊርማው ከሌለበት ወይም የእሱ ካልሆነ ሰነድ እንዲ ቼክ አይባልም፡፡ ነገር ግን መርሳት የሌለብን አውጪው ለተከፋዩ ፊርማው የእኔ ነው ብሎ አሳሳች ነገር ተናግሮ ቼኩን ሰጥቶት እንደሆነ በወንጀል ሕጉ አንቀፅ 692 ስር በተገነነገገው የማታለል ወንጀል ተጠያቂ መሆኑ አይቀርለትም ምንም እንኳን አንቀፅ 693 ስር ተጠያቂ ባይሆንም ማለት ነው(ከፍትሐበሔር ተጠያቂነት ጎን ለጎን አላግባብ ስለመበልፀግ በተደነገገው መሠረት)

ከቼክ ጋር በተገናኘ በሰበር ችሎት የተሰጡ አስገዳጅ ውሳኔዎች

ከቼክ ጋር በተገናኘ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከሰጣቸው ውሳኔዎች መኃል የተወሰኑትን ማንሳቱ ጠቃሚ መሆኑን በማመን የተወሰኑትን እንመለከታለን፡፡

የሰበር መዝገብ ቁጥር 67947 ቅፅ 12 ላይ እንደተወሰነው የሚያዝበት ገንዘብ ሳይኖር ቼክ ማውጣት በሚል በወንጀል ሕጉ ውስጥ የተመለከተውን የወንጀል ድርጊት ለማቋቋም ቼኩ ለክፍያ ባንክ በቀረበበት ጊዜ በቂ ስንቅ የሌለው መሆኑን/አለመሆኑን / ማረጋገጥ ብቻ በቂ መሆኑን አስገዳጅ በሆነው ውሳኔው ላይ አስቀምጦታል፡፡ በዚህ ውሳኔ መሠረትም ለዋስትና ነው ቼኩን የሰጠሁት፤ቼኩ ለክፍያ ሲቀርብ በቂ ሂሳብ እንደማይኖረው ለተከፋዩ ስላሳወኩት የማታለል ጉዳይ የሌለ ስለሆነ በቼክ ማታለል ልጠየቅ አይገባም የሚሉ መከራከሪያዎች ተቀባይነት እንደሌለው ብቻም ሳይሆን ከላይ የጠቀስነውን የድራፍቲንግ ችግር ይህም ውሳኔ ያረጋገጠው ጉዳይ ሆኗል ማለት ነው፡፡

የሰበር መዝገብ ቁጥር 20232 ቅፅ 7 ላይ እንደተወሰነው የሚተላለፉ የገንዘብ ሰነዶች (ቼክን ጨምሮ ማለት ነው) የተዋዋይ ወገኖች መብትና ግዴታ የሚረጋገጥባቸው በመሆናቸው የውል ሕግ መሰረታዊ ድንጋጌዎች መሟላታቸው አስፈላጊ ስለመሆኑ አስገዳጅ ውሳኔውን አስተላልፏል፡፡ ይህም ማለት ውልን ለመመስረት አስፈላጊ የሆኑት መግለጫዎች መኖር ይኖርባቸዋል ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ በኃይልና ማስገደድ የተገኘ ቼክ ይህ እስከተረጋገጠ ድረስ መብትሀና ግዴታ እንዳይጥል በፍርድ ቤት ማስወሰን ይቻላል ማለት ነው፡፡ ምክንያት በቼክ ዝውውር ግንኙነቱ ውስጥ የውል ሕግ መሰረታዊ ድንጋጌዎች አለመሟላታቸው፡፡

እንግዲህ በዚህ ጽሑፍ ላይ የተነሱት ሀሳቦች አጠቃላይ የሕግ ይዘትና በአከራካሪ ጉዳዮቹ ዙሪያ የግል አስተያየትም ጭምር ያለባቸው ስለሆኑ አንባቢው በበኩሉ የሚመስለውን ወይም መሆን አለበት የሚለውን ሊያካፍል ይችላል፡፡