የሰው ልጅ ወደዚች ምድር ከመጣበት /ከተወለደበት/ እለት አንስቶ እስከ ሕይወቱ ፍፃሜ ድረስ በዚች ምድር ላይ የሚኖረው ለተወሰነ ጊዜ ነው፡፡ የሰው ልጅ በዚች ምድር ላይ ዘላለማዊ አይደለም፡፡ ለያንዳንዱ ሰው በፈጣሪው የተጠው የምድር ቆይታ ጊዜ አለው፡፡ ይህ የምድር ላይ ቆይታው በአይቀሪው ሞት ይጠናቀቃል፡፡ የሰው ልጅ ወደዚች ምድር ከተቀላቀለበት እለት አንስቶ እስከ እለተ ሞቱ ድረስ የሕግ መብት አለው፡፡

በዚች ምድር ላይ በቆይታው ጊዜው የሰው ልጅ የተለያዩ መብቶች እና ግዴታወች አሉ፡፡ ለምሳሌ ያህል ንብረት የማፍራት መብት የሚጠቀስ ነው፡፡ በእለት ተእለት ኑሮው የተለያዩ ሥራዎችን እየሠራ የራሱን ብሎም የቤተሰቡን ጉርስ ለመሸፈን ጥረት ያደርጋል፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ የራሱ የሆነ ጥሪት ማፍራቱ አይቀሬ ነው፡፡ ይህን ጥሪት በምድር ላይ እስካለ ብቻ ነው የሚጠቀምበት፡፡ ሕይወቱ ካለፈች በኋላ ይህን ያፈራውን ንብረት በሕይወት ያሉ የሱ የቅርብ ሰዎች ናቸው የሚጠቀሙበት፡፡ እነዚህ በሕይወት ያሉ የሟችን ንብረት ሕይወቱ ካለፈ እለት በኋላ የሚጠቀሙበት በውርስ በመውረስ ነው፡፡ ውርስ የአንድ የሞተን ሰው ኃብትና ንብረት እንዲሁም ሊተላለፉ የሚችሉ መብትና ግዴታዎች ለአንድ ወይም ከአንድ በላይ ለሆኑ በሕይወት ላሉ ሰዎች የሚላለፋበት ሕጋዊ ሰርዓት ነው፡፡ ይህ ሰርዓት ደግሞ ሊያስከትል የሚችለው ሕጋዊ ውጤት ስለሚኖረው ራሱን የቻለ ሕግ ሊኖረው ይገባል፡፡

የሟችን ንብረት የሚወርሱት እንማንናቸው፣ ወራሽነትን የሚያሳጡ ነገሮች ምንድን ናቸው፣ ንብረቱ እንዴት ይከፋፈላል፣ ሟች ኑዛዜ ከተወ ኑዛዜው ሕጋዊ ውጤት እንዲኖረው ምን ምን መሟላት አለበት እና የመሳሰሉትን ነገሮች የሚመራው የሕግ ክፍል የወርስ ሕግ ይባላል፡፡ በዚህ ጽሑፍ የሃገራችን የውርስ መሠረታዊ ጉዳዩች እንቃኛለን፡፡

የውርስ ምንነት እና ስለ ውርስ አስተላለፍ

ውርስ ምንድን ነው?

ውርስ ምንድን ነው የሚለውን ትርጉም በሃገራችን የውርስ ሕግ ውስጥ በቀጥታ ተተርጉሞ ባናገኘም ከሕጉ ጠቅላላ መንፈስ ግን ትርጉሙን መረዳት እንችላለን፡፡ ይህም ውርስ ማለት የአንድ በሞት የተለየን ሰው ንብረት እና ኃብት እንዲሁም ሊተላለፍ የሚችሉ መብት እና ግዴታዎች በሕይወት ላሉ አንድ እና ከዚያ በላይ ለሆኑ ሰዎች የሚተላለፍበት መንገድ ነው፡፡ እውቁ የሕግ መዝገበ ቃላት Black’s Law “succession is the transmission of the rights and obligations of the deseased to the heirs, also the estates, right and charges which a person leaves after his death” በማለት ትርጉም ይሰጠዋል፡፡

የቃሉ ትርጉም በግርድፉ “ውርስ ማለት የሟች መብትና ግዴታዎች እንዲሁም ኃብት ፣በሃብቱ ላይ ያለው መብትና ግዴታ በሕይወት ላሉት ወራሾቹ የሚተላለፍበት መንገድ ነው”በማለት ይገልፀዋል፡፡

የውርስ ሕግ ምነድነው?

የውርስ ሕግ ጠቅለል ባለ አገላለፅ የሟች (አውራሽ) መብቶች እና ግዴታዎች በሕይወት ወዳሉት ወራሾቹ የሚተላለፍበት ሕግ ነው፡፡ የሟች ውርስ መች እና እንዴት ይከፈታል፣ ወራሾች እነማን ናቸው፣ ወራሽነትን የሚያሣጡ ነገሮች ምንድን ናቸው፣ የሟች ኑዛዜ ምን ማሟላት አለበት፣ ውርሱ እንዴት እና በማን ይጣራል፣ የውርስ ክፍያ እንዴት እና በማን ይፈፀማል እና የመሳሰሉትን የሚመራ ሕግ የውርስ ሕግ ነው፡፡ በሃገራችን ኢትዮጵያ ይህ የውርስ ሕግ  በ1952ዓ/ም በወጣው የፍታብሄር ህጋችን በሁለተኛ መጽሃፍ በአንቀፅ አምስት ውስጥ ከአንቀፅ 826 እስከ 1125 ድረስ ተቀምጦ ይገኛል፡፡

ከላይ እንደተገለጸው ውርስ ማለት የሟችን መብቶችን እና ግዴታዎች ወደ ሕይወት ያሉ ወራሾች ማስተላለፍ መሆኑን ገልፀናል ፡፡ የማስተላለፍ ሂደት የተሟላ እንዲሆን የሚከተሉት ቅደም ተከተሎች መከተል ተገኒ ነው፤

ሀ/ ውራሾችን ማጣራት ( መውረስ የሚችሉ እነማን እነደሆኑ ማወቅ )፣

ለ/ ውርስ ማጣራት እና

ሐ /ውርስ ክፍፍል

ሀ/ ወራሾችን ማጣራት

ስለ ውርስ መክፈት

የሟች ኃብትና ንብረት እንዲሁም ወራሾች በተለያየ ቦታ ሊገኙ ስለሚችሉ ሁሉንም በአንድ ቦታ አጠቃሎ ለማየት እንዲያመችና በውርስ ላይ ክርክር ቢነሳ ጉዳዩን የመዳኘት ሥልጣን ያለውን ፍርድ ቤት ለይቶ ለመወሰን እንዲቻል ውርስ የሚከፈተው ቦታ ተለይቶ መታወቅና በሕግም መገለፅ አለበት፡፡ በፍትሐብሔር ሕግ አንቀጽ 862/1/ ላይ እንደተገለፀው የሟች ውርስ የሚከፈተው ሟች በሞተበት ጊዜ ዋና መኖሪያው ስፍራ በሆነበት ቦታ ነው ይላል፡፡ በመሆኑም ሟች ከመሞቱ በፊት ከአንድ በላይ የመኖሪያ ስፍራ የነበረው ቢሆን እንኳን ውርሱ የሚከፈተው ሟች በሞተበት ጊዜ ዋና መኖሪያው በነበረው  ስፍራ ነው፡፡

በውርስ መተላለፍ የሚችሉ መብትና ግዴታዎች

የሟች ንብረት እንዲሁም መብትና ግዴታዎቹ በውርስ ሕግ መሠረት ለወራሾች የሚተላለፉ ናቸው፡፡ ይህ አጠቃላይ ደንብ ነው፡፡ ነገር ግን ሁሉም መብትና ግዴታዎች ሊወረሱ ወይም ለወራሾች ሊተላለፉ አይችሉም፡፡ በባሕሪያቸው አንዳንድ መብቶች እና ግዴታዎች ግለሰባዊ ናቸው፡፡ በመሆኑም በውርስ የሚተላለፉት መብትና ግዴታዎች ከሟች መሞት ጋር አብረው ቀሪ የማይሆኑ እና መተላለፍ የሚችሉት ብቻ ናቸው፡፡ ለምሳሌ ያህል ሟች የህክምና ዶክተር ቢሆን ይህን ዶክተርነቱን ለወራሾች ማውረስ አይችለም ምክንያቱም ይህ እውቀት የግለሰቡ ብቻ በመሆኑ፡፡ እዚህ ጋር መነሳት ያለት ሌላኛው ነገር ሟች በሕይወት እያለ ይጠቀምባቸው ወይም ያገኛቸው የነበሩ ጥቅሟች በሙሉ የውርስ አካል መሆን አይችሉም፡፡ በዚህ ሁኔታ ሊተላለፉ ከማይችሉ ጥቅሟች ውስጥ በፍ/ብ/ሕ/ቁ 827 እና 828 ላይ የተገለፁት የሕይወት ዋስትና መድህን፣ ጡረታ እና ካሳ ናቸው፡፡ የሕይወት ዋስትና በመድን ሰጭው እና በመድን ተቀባዩ መካከል የሚደረግ ውል ነው፡፡ በመሆኑም የሕይወት ዋስትና መድህን ለወራሾቹ በግልጽ እነእገሌ ይጠቀሙ ወይም ለወራሾች ጥቅም የተደገ መሆኑን በግልጽ በመድን ውሉ ውስጥ ካልተቀመጠ በስተቀር የውርስ ኃብት አካል አይሆንም፡፡ እንዲሁም በሞት ምክንያት ለሟች ዘመዶች ወይም ለባል ወይም ለሚስት የሚሰጥ ጡረታ ወይ ካሳ የውርስ ኃብት አካል አይሆንም፡፡

ወራሽ ለመሆን የሚያስፈልጉ ችሎታ

ለወራሽነት ብቁ የሚያደርጉ በሕጉ የተቀመጡትን ቅድመ ሁኔታዎችን ሳያሟሉ እንዲሁም በስመ ወላጅት ወይም ተወላጅነት ብቻ ወራሽ መሆን አይቻልም፡፡ ይልቁንም በሕጉ የተቀመጡትን ወራሽ ለመሆን መሟላት ያለትን/ያለባትን/ ቅድመ ሁኔታዎች ሟሟላት አለባቸው፡፡ እነዚህም ሁኔታዎች ያላሟላ ወራሽ በኑዛዜ ስሙ ቢጠቀስም ወይም በሕግ ወራሽነቱ ቢገለፅም ከውርሱ ተጠቃሚ ሊሆን አይችልም፡፡ ለወራሽ ብቁ ለመሆን የሚያስፈልጉት ቅድመ ሁኔታዎች፡-

        ሀ/ በሕይወት መኖር እና                  

        ለ/ ለወራሽነት የማይገባ አለመሆን ናቸው፡፡

ሀ/ በሕይወት መኖር

በፍ/ብ/ሕ/ቁ 830 ላይ እንደተገለፀው አንድ ሰው ወራሽ ለመሆን አውራሹ በሚሞትበት ወቅት በሕይወት ያለ መሆን አለበት፡፡ በሌላ አገላለፅ ሟች ሲሞት ያልነበሩ ወይም ሟችን /አውራሽን / ቀድሞ የሞተ መውረስ አይችሉም፡፡ ነገር ግን በልዩ ሁኔታ በፍ/ብ/ሕ/ቁ 834 ላይ እንደተገልፀው ሟች በሚሞትበት ወቅት በእናቱ ፅንስ ውስጥ ያለ ህፃን ተወልዶ 48 ሰዓት በሕይወት ከቆየ ውርስ ሲከፈት እንደነበረ ተቆጥሮ የመውረስ መብቱ ይጠበቅለታል፡፡

እዚህ ነጥብ ላይ ሌላኛው አጨቃጫቂ ጉዳይ አብሮ በአንድ ጊዜ የሞቱ ሰዎች ጉዳይ ነው፡፡ አብሮ ሟቾቹ አንዱ አንዱን የሚወርስ ከሆነ የአንደኛው ውርስ ሲከፈት ሌላኛው በሕይወት መኖር አለት የሚለውን ቅድመ ሁኔታ ለማሟላት የትኛው ቅድሚያ እንደሞተ ማረጋገጥ አዳጋች የሚሆንበት ጊዜ ያጋጥማል፡፡ በፍ/ብ/ሕ/ቁ 832 ላይ ለዚህ ጉዳይ መፍትሄ አስቀምጧል፡፡ ይህም ሁለት ወይም ከዚያ በላይ ሰዎች አብረው የሞቱ እንደሆነ እና የትኛው በኋላ የሞተው የሚለውን ማረጋገጥ ካልተቻለ ከአብሮ ሟቾቹ ሰዎች ኃብት ወራሽነት ምንም ሳያገኝ የነዚህ ሰዎች የያንዳንዳቸው ውርስ በመጨረሻ እንደ ሞተ ዓይነት ተቆጥር ይወሰናል፡፡

ለ/ ለወራሽነት የማይገባ አለመሆን

ወራሽ ለመሆን ከሚያስፈልጉት ቅድመ ሁኔታዎች ሌላኛው ለወራሽነት የማይገባ አለመሆን ነው፡፡ አንድ ወራሽ ለወራሽነት የማይገባ የሚሆነው በፍ/ብ/ሕ/ቁ 838 ላይ እንደተጠቀሰው በአውራሹ ወይም ወደ ታች የሚቆጠሩ ተወላጅ/ዎች/ ወይም ወደ ላይ የሚቀጠሩ ወላጆች ወይም ባል ወይም ሚስት አስቦ በመግደል የተፈረደበት ወይ ለመግደል ሙከራ የተቀጣ ወይም በሀሰት በመወንጀል ወይም በመመስከር አንደኛውን የሞት ፍርድ ወይም ከአስር ዓመት በበለጠ የፅኑ እሥራት ቅጣትን ለማስከተል የሚያሰጋ ሆኖ የተቀጣ ከሆነ ነው፡፡ እነዚህን ከላይ የተገለፁትን ድርጊቶች የፈፀመ እና የተቀጣ ሰው ወራሽ መሆን አይችሉም፡፡ ነገር ግን ወራሽ የሆነው ሰው በነዚህ በተጠቀሱ ሰዎች ላይ ወንጀሉን ወይም የወንጀሉን ሙከራ ያደረገው አውራሹ ከሞተ በኃላ ከሆነ የወራሽነት መብቱን ማጣት አይፈፀምበትም፡፡

ሌላው ለወራሽነት የማይገባ የሚያደርገው ምክንያት ሟች በነፃነት እንዳይናዘዝ ተጽእኖ ማሳደር ነው፡፡ ይህም አውራሽ ከመሞቱ በፊት ባሉት ሶስት ወር ውስጥ የአውራሽን ሁኔታ ከግምት አስገብቶ ኑዛዜ እንዲይደርግ፣ እንዳይለውጥ ወይም እንዳይሽር የከለከለ እንደሆነ ወይም አስቦ ያለ ሟች ፍቃድ የመጨረሻውን ኑዛዜ ያበላሸ፣ እንዳይገኝ ያደረገ፣ ያጠፋ ወይም ጉዳየን በማወቅ በሐሰት ኑዛዜ የተጠቀመ እንደሆነ ነው፡፡ ይህም የሆነበት ምክንያት አንድ ሰው ከጥፋቱ መጠቀም የለበትም ከሚለውን የሕግ መርህ በመነሳት  ነው፡፡

ሆኖም ለወራሽነት የማይገባ የሆነ ሰው በአውራሹ (ሟች) ይቅርታ ከተደረገለት የመውረስ መብቱን ያገኛል፡፡ ይቅርታውን ማድረግ የሚችለው አውራሽ ብቻ ነው፡፡ ይቅርታውንም የሚያደርገው ግልጽ በሆነ ጽሑፍ ይቅርታ ማድረጉን ሲገልፅ ወይም በኑዛዜ የሚደረግ ውርስ ከሆነ በኑዛዜው ወራሽ ለውርስ እንደማይገባ እያወቁ ስጦታ ካደረገለት ይቅርታ እንዳደረገለት ይቆጠራል፡፡ (የፍ/ብ/ሐ/ቁ 841)፡፡

ከጋብቻ ውጭ መወለድ ወይም የጉዲፈቻ ልጅ መሆን ለወራሸነት የማይገባ አያደርጉም፡፡ እንዲሀም የወራሽ ፆታ፣ዕድሜና ዜግነት ለወራሸነት የማይገባ አያደርጉም፡፡ ከሕጋዊ ጋብቻ የተወለደ ልጅ ሆነ የጉዲፈቻ ልጅ እድሜው፣ ፆታው እና ዜግነቱ የቱንም ይሁን የመውረስ መብት አለው፡፡

የውርስ ሥርዓቶች

በሃገራችን የውርስ ሕግ ውስጥ ሁለት አይነት የውርስ ማስተላለፊያ መንገዶች አሉ፡፡ እነርሱም፡-

              ሀ/ ያለኑዛዜ ውርስ (INTESTATE succession) እና

              ለ/ በኑዛዜ ውርስ (Testate succession)

ሀ /ያለ ኑዛዜ ውርስ (Intestate succession)

አውራሽ (ሟች) ኑዛዜ ሳያደርግ ሲሞት ወይም ያደረገው ኑዛዜ ፈራሽ በሚሆንበት ጊዜ የአውራሽ ንብረት ለወራሾች የሚከፋፈለው በሕጉ በተቀመጠው መሠረት ያለ ኑዛዜ ውርስ መሠረት ነው፡፡በዚህ ዓይነቱ ውርስ የሚካሄደው በአውራሽ ፍላጎት ሣይሆን በሕጉ መሠረት ነው፡፡ ሕጉ ደግሞ መሠረት ያደረገው የዘር ሐረግን ነው፡፡ ይህም የሆነበት ምክንያት ሟች ኑዛዜ ቢያደርግ ኖሮ ለነዚህ ዘመዶቹ ስጦታ ያደርጋል ተብሎ ስለሚገመት ነው፡፡

ያለ ኑዛዜ ውርስ ላይ የሟችን ንብረት  በመጀመረያ ደረጃ የሚወርሱት የሟች ልጆች ናቸው ፡፡የሟች ልጆች ለመውረስ ብቁ የሚያደርጓቸውን በሕይወት ያሉ መሆን እና ለወራሽነት የማይገባ አለመሆን ቅድመ ሁኔታዎችን እስካሟሉ ድረስ የመጀመሪያ ደረጃ ወራሾች ናቸው፡፡በፍ/ብ/ሕ/ቁ 842(3) ላይ የሟች ልጆች ወይም ከልጆቹ አንዱ የሞተ እንደሆነ ወደታች የሚቆጠሩ ተወላጆች ትተው እንደሆነ በነሱ ምትክ ሆነው ይወርሳሉ በማለት ተገልጾአል ፡፡የሟች ልጀች ውርሱን እያንዳንዳቸው እኩል ይካፈላሉ፡፡

የመጀመረያ ደረጃ ወራሾች ወይም የእነሱ ተወላጆች በሕይወት ከሌሉ ያለ ኑዛዜ ውርስ ወራሾች የሚሆኑት በሁለተኛ ደረጃ ዝምድና በሕጉ የተቀመጡት የሟች አባትና እናት ናቸው፡፡ በፍ/ብ/ሕ/ቁ 844(1) ላይ እንደተገለፀው የሟች አባትና እናት ውርሱን ንብረት አኩል በእኩል ይካፈላሉ፡፡ አናት ወይም እናት ወይም ሁለቱም ቀድመው የሞቱ እንደሆነ የነሱን ፋንታ ወደታች የሚቆጠሩ ተወላጆቻቸው ተተክተው ይወርሳሉ፡፡ በአባት ወይም በእናት መስመር /አንዱ መስመር/ የሚወርስ ከሌላ ወደ ሌላኛው መስመር ሙሉ ውርስ ይተላለፋል፡፡

ያለኑዛዜ የሚደረግ ውርስ የሟች ልጆች እና ወላጆቹ የሟች ውርስ ሲከፈት በሕይወት ከሌሉ እና እነርሱን ተክቶ ውርሱን የሚወርስ ሰው ከሌለ ውርሱ ወደ ሶስተኛ ደረጃ ዝምድና ላይ ለተቀመጡ አያቶቹ ይሄዳል፡፡ ይህ በሚሆንበት ግዜ የውርስ እኩሌታው በአባት መስመር ላሉት አያቶች እኩሌታው ደግሞ በእናት መስመር ላይ ላሉት አያቶች እንደሚሆን የፍ/ብ/ሐ/ቁ  845 (2) ይገልፃል፡፡ አያቶቹ ውርስ ሲከፈት በሕይወት ከሌሉ ወደታች የሚቆጠሩ ተወላጆቻቸው ተክተዋቸው ይወርሳሉ፡፡ በአባት ወይም በእናት የትውልድ መስመር የዘር ተከታይ ሳይኖረው የሞተ አያት ድርሻው ለዚህ መስመር ወራሾች ይተላለፋል፡፡ አንድ የትውልድ መሥመር (የአባት ወይም የእናት) የዘር ተከታይ ሳይኖራቸው የሞቱ አያቶች ማናቸውም የውርስ ኃብት ሁሉ ለሌላኛው ወገን የዝምድና መሥመር ወራሾች ይተላለፋል ፡፡ (የፍ/ብ/ሐ/ቀ/846)

የሟች ቅድመ አያቶች በአራተኛ ደረጃ የዝምድና የሟች ሶስተኛ ደረጃ ዝምድና ላይ የሚገኙት አያቶች ከሌሉ እና እነርሱን ተክቶ የሚወርስ ከሌለ ወራሽ እንደሚሆኑ በፍ/ሐ/ቁ 847 ላይ ተገልፆአል፡፡ የውርስ እኩሌታው የአባት መስመር ለሆኑት ቅድመ አያቶች ወይም ተወላጆቻቸው.፤ እኩሌታውን የእናት መስመር ለሆኑ ቅድመ አያቶች ወይም ትወላጆቻቸው ይሰጣል፡፡ ዘመዶች እስከ አራትኛ ደረጃ ተለይቶ ያልተገኘ እንደሆን የሟችን ንብረት ለመንግስት እንደሚተላለፍ የ/ፍ/ሕ/ቁ 852 ላይ ተገልፆኣል፡፡

ያለ ኑዛዜ ውርስ ላይ ከላይ ለመግለፅ እንደተሞከረው የአባት ንብረት ወደ እናት ሐረግ እንዲሁም የእናት ንብረት ወደ አባት ሐረግ ሊተላለፍ የሚችልበትን አጋጣሚዎች እንዳሉ አይተናል፡፡ ነገር ግን በልዩ ሀኔታ ከአባት ወገን ወደ እናት ወገን ንብረት እንደማይተላለፍ በውርስ ሕጎችን ተገልፆ ይገኛል፡፡ ይህም በፍ/ብ/ሕ/ቁ 849 ላይ የጠቀመጠው የአባትን ለአባት ወገን የእናትን ለእናት ወገን መስጠት የሚል ደንብ ነው፡፡ ይህ ደንብ ተግባራዊ  እንዲሆን የሚከተሉት ቅድመሁኔታዎች መሟላት ይኖርባቸዋል ፡-

1ኛ ንብረቱ ከመጣበት መሥመር ሕጋዊ ወራሽ መኖር አለበት፣

    2ኛ ሟች ሳይናዘዝ የሞተ መሆን አለበት ፣

   3ኛ ንብረቱ የማይንቀሳቀስ መሆን አለበት፣

   4ኛ ንብረቱ ከአባቱ ወይም ከእናት መሥመር በውርስ ወይም በስጦታ የመጣ መሆን አለበት

   5ኛ የሟች ተወላጆች በሕይወት የሌሉ መሆን አለባቸው፡፡

ይህም ማለት ከአባት ወገን አያቱ በስጦታ ወይም በውርስ የተገኘው የማይንቀሳቀስ ንብረት የእናት ወገን ለሆነ ተወላጅ እንዳይተላለፍ እንዲሁም ከእናት በኩል የገኘው ለአባት በኩል እንዳይተላለፍ የሚያደርግ ነው፡፡ ይህም የሆነው የቤተሰብ ቅርስ የሆነ ንብረት በቤተሰብ እጅ እንዲቀር ነው፡፡ ነገር ግን ይህን ንብረት እንዳይወርስ የተደረገው ሰው ከንብረቱ የአላባ (usufruct) መብት አለው፡፡

ምትክነት

ከላይ እንደተገለፀው የወራሽነት መብት የተሰጠው ወራሽ ከሌለ የሱን የውርስ ድርሻ የሱ ወራሽ በምትክነት ገብቶ እንደሚወርስ አይተናል፡፡ ይህ የምትክነት መርህ የሚተገበረው፡፡

        1ኛ. ተተኪው ሰው ውርሱ በተከፈተበት ጊዜ ይህ የሚተካው ሰው (ወራሽ) በሕይወት የነበር መሆን አለበት

        2ኛ. ምትክ ባስፈለገበት ጊዜ ይህ የሚተካው ሰው በሕይወት የሌለ መሆን አለበት

        3ኛ. የሚተካው ሰው በሕይወት በነበረ ጊዜ ውርሱን ለመቀበል ፍቃደኛ የነበረ መሆን አለበት እና

        4ኛ. ተተኪው ሰው ለወራሽነት ብቁ የሆነ (ለወራሽነት የማይገባ ያልሆነ) መሆን አለበት፡፡

ወራሽነትን አልፈልግም ባለ ወራሽ ምትክ ገብቶ መውረስ አይችልም፡፡ ነገር ግን ውርሱን አልፈልገውም በተባለው ሰው ምትክ ለመግባት እና ለመውረስ የሚቻል መሆኑን በፍ/ብ/ሐ/ቁ 854 ላይ ተገልፆል፡፡ ለምሳሌ፡- “ሐ” የአባቱን የ”ለ”ን ንብረት አልወርስም ብሎ የወራሽነት መብቱን ቢተው አባቱን አልወርስም ማለቱ በአባቱን ምትክ ገብቶ አያቱን “ሀ”ን እንዳይወርስ አያደርገውም፡፡ ነገር ግን ልጁ “መ” እሱን ተክቶ “ለ”ን መውረስ አይችልም፡፡

በፍ/ብ/ሕ/ቁ 856 ላይ እንደተገለፀው ከሟች ጋር የስጋ ዝምድና የሌለው ሰው በምትክነት ገብቶ ለመውረስ አይችልም፡፡ በሕጉ መሠረት ከሟች ጋር የዝምድና ትስስር የሌለው ማናኛው ሰው ተተክቶ መውረስ አይችል፡፡

ለ/ በኑዛዜ ውርስ (Testate succession)

ሁለተኛው ውርስ ማስተላለፍያ መንገድ ኑዛዜ ነው፡፡ ኑዛዜ ማለት ሟች ከመሞቱ በፊት ንብረቱን በፍላጎቱ መሠረት ለተተኪዎቹ የሚያስተላልፍበት ሕጋዊ መንገድ ነው፡፡ ሟች በኑዛዜው ከሞተ በኋላ ስለ ንብረት ክፍፍል፣ የልጆቹ ሞግዚት ማን እንደሚሆን፣ ንብረቱን ማን እንደሚያስተዳድር፣ ስለ ቀብር ስነስርዓቱ ሊገልፅ ይችላል፡፡ ኑዛዜ በወኪል ወይም በእንደራሴ የማይከናወን የተናዛዡ የግል ድርጊት ነው (ፍ/ብ/ሕ/ቁ/857)፡፡ ስለዚህም ለመናዘዝ፣ ለማሻሻል ወይም ቀሪ ለማድረግ በውክልና ለሌላ አካል መስጠት ኑዛዜውን ዋጋቢስ ያደርገዋል፡፡

ኑዛዜ የሚደረገው በተናዛዡ ብቻ እንደሆነ ከላይ በተገለፀው መልኩ ተረድተናል፡፡ ይሁን እንጂ ማንኛውም ሰው የሚያደርገው ኑዛዜ ሁሉ የሚፀና አይደለም፡፡ አንድ ኑዛዜ በሕግ በኩል ተቀባይነት የሚኖረው ተናዛዡ በሕግ የመናዘዝ ችሎታ ያለው ሰው ሲሆን ብቻ ነው፡፡ በሕጉ ችሎታ የላቸውም የተባሉት ሰዎች፡-    

                   1ኛ. እድሜያቸው ከ16 ዓመት በታች የሆኑ

                   2ኛ. በፍርድ የተከለከሉ ሰዎች

                   3ኛ. የአእምሮ ሕመም ያለባቸው ሰዎች ናቸው፡፡

አንድ እድሜው አሥራ ስድስት ያልሞላ ልጅ ኑዛዜ ማድረግ እንደማይችል በተሻሻለው የቤተሰብ ሕግ አንቀፅ 295 ላይ ተገልፆል፡፡ በፍርድ የተከለከለ ሰው ከተከለከለበት እለት ጀምሮ ኑዛዜ ማድግ አይችልም፡፡ ነገር ግን ከመከልከሉ በፊት ያደረገው ኑዛዜ ተቀባይነት አለው፡፡ ይህም ሆኖ ዳኞች እንደነገሩ ሁኔታ ኑዛዜውን በሙሉ ወይም በከፊል እንዲፈርስ የማድረግ ሥልጣን በፍ/ብ/ሐ/ቁ 368 ላይ ተሰጥቶቸዋል፡፡ የአእምሮ ሕመም ያለበት ሰው ያደረገው ኑዛዜም አይፀናም፡፡ ኑዛዜው የማይፀናው ግን  ኑዛዜውን ባደረገበት ጊዜ የታወቀ ዕብድ መሆኑ ሲረጋገጥ ብቻ ነው፡፡

 

ኑዛዜ ( Will )

ከላይ እንደተገለፀው ኑዛዜ ማለት ሟች ከመሞቱ በፊት ንብረቱን በፍላጐቱ መሠረት ለተተኪዎቹ የሚያስተላልፍበት ሕጋዊ መንገድ ነው፡፡ እንዲሁም ኑዛዜ የሚደረገው ኑዛዜውን ለማድረግ በሕግ  ችሎታ ባለው ሰው ብቻ በግሉ (በራሱ) የሚያደርገው ሕጋዊ ድርጊት ነው፡፡ ኑዛዜው የሚፀና  እንዲሆን ኑዛዜውን በተመለተ መሙላት ያለባቸው ሁኔታዎች አሉ፡፡ እነዚህም፡፡

        1ኛ. ኑዛዜው መፈፀም የሚችል መሆን አለበት፣

        2ኛ. የኑዛዜው ቃል ሕገ ወጥ መሆን የለበትም፣

        3ኛ. ኑዛዜ በሃይል የተደረገ መሆን የለበትም፣

        4ኛ. ኑዛዜው በመንፈስ ጫና ምክንያት የተደረገ መሆን የለበትም

 

አንድ የኑዛዜ ቃል በማያሻማ መልኩ ተጠቃሚውን ወይም ጉዳዩን ካላመላከተ ፈራሽ ነው፡፡ በማንኛውም የኑዛዜ ቃል ላይ “ይህ ንብረት ለእገሌ” ተብሎ በግልጽ መቀመጥ አለበት፡፡(ፍ/ብ/ሕ/ቁ 865)፡፡ እንዲሁም አፈፃፀሙ የማይቻል ኑዛዜ ፈራሽ ነው፡፡ ለምሳሌ ሟቹ በሕይወት እያለ ሸጦ ገንዘቡን የተገለገለበትን መኪናውን አበበ የተባለ ልጄ ይውሰድ ቢል ይህ የኑዛዜ ቃል ሊፈፀም የማይችል ነው፡፡ በመሆኑም ተቀባይነት የለውም፡፡

 

የኑዛዜ ቃል ሕግን ወይም መልካም ጠባይን ተቃራኒ የሆነ እንደሆነ ፈራሽ ነው፡፡ ሁልጊዜም ቢሆን የኑዛዜ ቃል ሕግን እና መልካም ጠባይን ያከበረ መሆን አለበት፡፡ ለምሳሌ ለምለም የተባለችው ልጅ አዲስ አበባ ያለውን ቤቴን የምትወስደው ጫላ የተባለውን ወዳጄን ስታገባ ነው በማለት በኑዛዜ ቃሉ አባቷ ቢገልፅ ይህ ኑዛዜ ከቤተሰብ ሕጉ ጋብቻ ተጋቢዎች ሲፈቅዱ ብቻ ነው የሚለው ስለሚቃረን ተቀባይነት የለውም፡፡

በኃይል ተገዶ የተናዘዘ ተናዛዥ በትክክል ለሚፈልገው ሰው በፍላጐቱ መሠረት ሊናዘዝ ይችላል ተብሎ አይገመትም፡፡ ስለዚህም በኃይል ተገዶ ወይም በፍርሃት የተደረገ ኑዛዜ ፈራሽ ነው፡፡(ፍ/ብ/ሕ/ቁ 867)

ሟች ያደረገው ኑዛዜ በከፊል ወይም በሙሉ ፈራሽ የሚሆንበት ጊዜ አለ፡፡ ይህ ሁኔታ አለ የሚባለው  የመንፈስ መጫን (undue influence) ሲኖር ነው፡፡ በመሠረቱ አንድን ኑዛዜ በኑዛዜው ተጠቃሚ የሆነ ሰው ባደረገው የመንፈስ ተፅዕኖ የተደረገ ነው ብሎ ውድቅ ለማድረግ አይቻልም፡፡ በአንፃሩ ግን የሥራ ወይም የሞያ ጠባያቸው ከሟች ጋር የቀረበ ግንኙነት እንዲኖራቸው የሚያደርጋቸው ሰዎች አሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች በተለይም ሟች ጋር ዝምድና ከሌላቸው በሥራ ወይም በሞያ ግዴታቸው ሟችን ጣዕሩ በበረታበት ጊዜ ስላገለገሉት ብቻ አለአግባብ ንብረት እንዳያገኙ ቢናዘዝላቸው ሕግ ጣልቃ ይገባል፡፡ ዕድሜው ከሀያ ዓመት በታች የሆነ ሰው ለአሳዳሪው ወይም ለሞግዚቱ ጥቅም ያደረገው ኑዛዜ ሊቀነስ ወይም ሙሉ በሙሉ ሊሻር ይችላል፡፡ ነገር ግን ሞግዚት ወይም አሳዳሪው ወደ ላይ የሚቆጠሩ ወላጆቹ ከሆኑ ግን ኑዛዜው ተፈፃሚ ይሆናል፡፡ (ፍ/ብ/ሕ/ቁ 869)፡፡

ሟችን ከመሞቱ በፊት ባሉት ስድስት ወራት ውስጥ የሕክምና እርዳታ ሲሰጡት የነበሩ ሀኪሟች ወይም በመንፈሳዊ አገልግሎት ሲሰጡት የነበሩ የእምነት አባቶች በአገልግሎታቸው ወቅት በሟች ላይ ከፍተኛ የመንፈስ ጫናን ሊያሳድሩ ይችላሉ ተብሎ ይገመታል፡፡ በመሆኑም ሟች በኑዛዜው ለነሱ የሰጠው ስጦታ እንደነገሩ ሁኔታ ሊቀነስ ወይ ሊሻር ይችላል፡፡ ነግር ግን እነዚህ ግለሰቦች ከሟች ጋር በትዳር የተሳሰሩ ወይም የስጋ ወይም የጋብቻ ዝምድና ካላቸው ይህ ደንብ ተፈፃሚ አይሆንም በማለት በፍ/ብ/ሕ/ቁ 870 ተገልጿል፡፡ በኑዛዜው ላይ ምስክሮች ወይም አዋዋዮች ለነበሩ ሰዎች የተደረገ ኑዛዜም በተመሳሳይ ሊቀነስ ወይም ሊሻር ይችላል፡፡ 

ከላይ በተገለፀው መልኩ ኑዛዜውን ለመቀነስ ወይም ለመሻር ሥልጣን የተሰጣቸው ለዳኞች ብቻ ነው፡፡ ዳኞች በዚህ ስልጣናቸው ለመሥራት በኑዛዜው ተጠቃሚ የሆነው ሰው ኑዛዜው እንዲፈፀምለት ጥያቄ ካቀረበበት ቀን አንስቶ በሶስት ወራት ውስጥ በሕጉ መብት የተሰጣቸው ሰዎች ጥያቄ ሲቀርቡ ብቻ ነው፡፡ ዳኞች በዚህ በተሰጣቸው ሥልጣን መሠረት ኑዛዜውን በከፊል ወይም በሙሉ ሲሽሩ ከልቦና ፍርድና ከርትዕ ጋር የተስማማ ነው የሚባሉትን ምክንያት መግለጽ አለባቸው፡፡

ሟች የኑዛዜውን አንዳንድ ክፍሎች ሊናዘዝ የቻለው የኑዛዜው ተጠቃሚ በፈፀመው የተንኰል ወይም የማታለል ሥራ ነው በማለት የኑዛዜውን ቃል መሻር አይቻልም፡፡ ነገር ግን የኑዛዜው ቃል ላይ ስህተት ካለ ኑዛዜው ይሻራል፡፡ ይህም የሚሆነው ተናዛዡ የፈፀመው ስህተት ሀሳቡን ወደ አንድ አቅጣጫ እንዲያዘነብል ወሳኝ በሆነ መልኩ ተፅዕኖ ያደረገበት ለመሆኑ በኑዛዜው አነጋገር ላይ በግልጽ ሲታይ ወይም ኑዛዜውን በሚጠቅስ በአንድ ሰነድ ላይ በማያሳጣ መልኩ ተገልፆ ሲገኝ ብቻ እንደሆነ በፍ/ብ/ሕ/ቁ 877 ተደንግጓል፡፡ አንድ የኑዛዜ ቃል ፈራሽ በሚሆንበት ጊዜ በፈራሹ ቃልና በሌሎቹ ቃላት አፈፃፀም መካከል የሚያስተሳስር ነገር አለ ተብሎ ካልታሰበ በስተቀር በመርሕ ደረጃ ኑዛዜውን ሙሉ በሙሉ ፈራሽ የማድረግ ውጤት አይኖረውም፡፡

በተወሰኑ አጋጣሚዎች አንዳንድ ግለሰቦች ኑዛዜአቸውን ከአንድ መሟላት ካለት ሁኔታ ጋር አያይዘውት ይገኛሉ፡፡ ይህ ቅድመ ሁኔታ የማይቻል ወይም ለሕግ ወይም ለመልካም ፀባይ ተቃራኒ ከሆነ ግን በሕግ ፊት ተቀባይነት የለውም፡፡ (የፍ/ብ/ሕ/ቁ 879)

 

የኑዛዜዎች ፎረም

ኑዛዜ ሟች በሕይወት እያለ ንብረቶቹን እሱ ከሞተ በሆላ የሚጠቀሙባቸውን ሰዎች በፍላጎቱ የሚሰጥበት መሆኑን ከላጥ ተመልክተናል፡፡ ኑዛዜ የሚፈፀመው ሟች ከሞተ በሆላ በመሆኑ የሟች ፍላጎት በተገቢው እንዲፈፀም አስቀድሞ በማያሻማና ግልጽ በሆነ ፎርም መደረግ አለበት፡፡ በፍ//ብ/ህ/ቁ 880 ላይ የውርስ ህጋችን ሶሶት ለአይነት ኑዛዜ ፎርሟችን አስቀምጧል፡፡እነሱም ፡-      

             ሀ/ በግልጽ የሚደረግ ኑዛዜ (public will)

             ለ/ በተናዛዡ ፁሁፍ የሚደረግ ኑዛዜ (holograph will) 

             ሐ/ በቃል የሚደረግ ኑዛዜ (Oral will)

  

ሀ/ በግልጽ የሚደረግ ኑዛዜ (public will)

 

ይህ ዓይነቱ ኑዛዜ በጽሑፍ ሆኖ ኑዛዜው ተናዛዡ እራሱ የሚፅፈው ወይም እሱ እየተናዘዘ ሌላ ሰው የሚፅፍለት ነው፡፡ ኑዛዜው ከተፃፈ በኋላ በተናዛዡና አራት ምስክሮች ፊት ተነቦ ስለመነበቡም በኑዛዜው ውስጥ ሰፍሮ ቀኑ ተጠቅሶ ወዲያው በተናዛዡ እና በምስክሮች መፈረም አለባቸው፡፡ ይህ ካልሆነ ኑዛዜው ፈራሽ ይሆናል፡፡ በግልጽ የሚደረግ ኑዛዜ የተደረገው ለማዋዋል ሥልጣን የተሰጠው ሰው ወይም ፍርድ ቤት ፊት ከሆነ አንድ ተጨማሪ ምስክር ብቻ ነው የሚያስፈልገው፡፡ ይህ ማለት ሁለት ምስክር ብቻ ነው የሚያስፈልገው ማለት ነው፡፡ በዚህ መልኩ በመንግስት ባለስልጣናት ፊት የሚፈፀም ኑዛዜ በዕርግጥም የሟችን ነፃ ፍላጐት የሚገልጽና በትክከለኛ አዕምሮ የተሰጡ ስለመሆናቸው በገለልተኛ አካል ለማረጋገጥ ከሚከፍቱት ልዩ ዕድል አንፃር ነው፡፡ ምክኛቱም ለማዋዋል ሥልጣን የተሰጠው ሰው የሶስት ምስክሮችን ያክል ነው ተብሎ ሕጉ ግምት ስለሚዎስድ ነው፡፡ በኑዛዜ ላይ ምስክር ሆነው የሚርቡ ምስክሮች ኑዛዜው የተፃፈበትን ቋንቋ ለመስማት ወይም ለማንበብ የሚችሉ መሆን አለባቸው፡፡ በግልጽ የሚደረግ ኑዛዜ ሊያሟላቸው የሚገቡት ዋና ዋና ሥርዓቶች በፍትሃብሄር ሕጉ አንቀፅ 881 ስር ተመልክተው የሚገኙ ሲሆን ኑዛዜው በምስክሮቹ ፊት መነበብ ያለበት መሆኑና ይሕ ሥርዓት ስለመፈፀሙና የተፈፀመበትን ጊዜ የሚገልፅ ቃል በኑዛዜው ውስጥ መካተቱ በሕጉ አስገዳጅ ተደርገው የተቀመጡ ነጥቦች ናቸው፡፡

 

ለ/ በተናዛዡ ጽሑፍ የሚደረግ ኑዛዜ (holo groph will)

 

የዚህ ዓይነቱ ኑዛዜ በጽሑፍ ሆኖ ሙሉ በሙሉ በተናዛዡ መፃፍ አለበት፡፡ በተጨማሪም ፅሁፉ ኑዛዜ መሆኑ በግልጽ “ኑዛዜ ነው” ተብሎ መፃፍ አለበት፡፡ እንዲሁም በያንዳንዱ ገፅ ላይ ተናዛዡ ቀን ጽፎ መፈረም አለበት፡፡ ተናዛዡ ኑዛዜውን በኮፒውተር ወይም በታይኘ ሊፅፈው ይችላል፡፡ ነገር ግን የራሱ ኑዛዜ መሆኑን በእጅ ጽሑፍ በያንዳንዱ ገፅ ላይ መግለፅ አለት፡፡ ይህ ሁሉ ያስፈለገው ኑዛዜው የተናዛዡ መሆኑን በእርግጠኝነት ለማረጋገጥ ስለሚጠቅም ነው፡፡ ይህ ካልሀነ ኑዛዜው ፈራሽ ነው፡፡ በተናዛዡ የእጅ ጽሑፍ የሆነውን ኑዛዜ ተናዛዡ ያልተማረ መሃይም በመሆኑ ኑዛዜው የተፃፈበት ቋንቋ እና ፍችውን ማያውቀው እንደሆነ ኑዛዜው ፈራሽ ነው፡፡

ከላይ በተገለፁት ሁለቱ አይነት የኑዛዜ ፎርሟች በጋራ የሚጋሯቸው ነጥቦች አሉ፡፡ እነዚህም ሁለቱም ላይ ቀን፣ ወር እና አመተ ምህረት መፃፍ አለበት፡፡ በእለቱ በተለያዩ ምክንያቶች ይህ ተረስቶ ሳይፃፍ ቢቀር ወይም በሌላ ጊዜ ትክክለኛ ያልሆነው ሰፍሮ ቢገኝ በኑዛዜው ወይም በሌላ ሰነድ ላይ ትክክለኛውን የሚያረጋግጥ ከሆነ ኑዛዜው የፀና ኑዛዜ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ካልተረገጠ ኑዛዜ ፈራሽ ይሆናል (ፍ/ብ/ሕ/ቁ 887)፡፡

አንዳንዱ ጊዜ ኑዝዜው ላይ የሰፈረው ቃል ለመረዳት አስቸጋሪ ይሆናል፡፡ ይህ በሚሆንበት ጊዜ ቃሉን ለመረዳት ከሌላ በሟች በራሱ የተፃፈና የተፈረመ ሰነድ ላይ አይተን እናረጋግጣለን፡፡ በኑዛዜው ቃል ላይ የሚገኘውንና መጀመሪያ የተፃፈውን ቃል የሚለውጥ ስርዝ፣ መፋቅና ድልዝ ኑዛዜውን ፈራሽ ያደርገዋል፡፡ ምክንያቱም የተናዛዡን ፈቃድ መለወይ ስለሚሆን ነው (ፍ/ብ/ሕ/ቁ 889)፡፡ በሌላ በኩል ስርዝ ወይም ድልዝ በመኖሩና በመፋቁ ምክንያት የኑዛዜ ቃል ፈራሽ የማይሆንበት ጊዜ አለ፡፡ ይህም እንደ ኑዛዜው ፎርም አይነት ኑዛዜው በግልጽ የተደረገ ኑዛዜ ከሆነ ምስክሮቹ ስርዝ ድልዙን በፊርማ ያፀደቁት፤ ኑዛዜው በተናዛዡ ጽሑፍ የተደረገ ከሆነ ግለሰብ በራሱ ማስታወሻ ላይ ከገለፀ የኑዛዜው ቃል ፈራሽ አይሆንም፡፡ (ፍ/ብ/ሕ/ቁ 889)፡፡

በተወሰኑ አጋጣሚዎች ኑዛዜዎች ከአንድ በላይ በሆኑ በተለያዩ ፅሁፎች ውስጥ ሊገኙ ይችላሉ፡፡ ይህ ሲሆን በፍ/ሕ/ቁ 895 ላይ እንደተገለፀው ተቀራራቢነት ኖሯቸው በአንድነት ሊፈፀሙ የሚችሉ ሆነው ሲገኙ በአንድነት ይፈፀማሉ፡፡ ነገር ግን በአንድ ላይ ሊፈፀሙ የማይችሉ ሲሆን በመጨረሻ የተደረገው ኑዛዜ ዋጋ ያለው ሆኖ ይፈፀማል፡፡

 

ሐ/ የቃል ኑዛዜ (Oral will)

 

የቃል ኑዛዜ በጽሑፍ ሳይሆን ተናዛዡ በቃሉ የሚደረገው ኑዛዜ ነው፡፡ የቃል ኑዛዜ አንድ ሰው የሞቱ መቃረብ ተሰምቶት የመጨረሻ ፈቃድ ቃሎቹን ለሁለት ምስክሮች የሚሰጥበት ነው፡፡ ምስክሮቹ አካለ መጠን የደረሱና በፍርድ ወይም በሕግ ያልተከለከሉ መሆን አለባቸው፡፡ በቃል በሚደረግ ኑዛዜ ተናዛዡ መናዘዝ የሚችለው ስለቀብር ሥነ-ሥርዓት በተመለከተ ትዕዛዞች መስጠት፣ ከአምስት መቶ የኢትዩጵያ ብር ያልበለጠ የንብረት ስጦታ እና ለአካለ መጠን ላልደረሱ ልጆች አስተዳዳሪ ወይም ሞግዚት መሾምን ብቻ ነው፡፡ በፍ/ብ/ሕ/ቁ 894 ላይ እንደተገለፀው በቃል ኑዛዜ ውስጥ ከላይ በተገለፁት ሌላ ማንኛውም የኑዛዜ ቃል ፈራሽ ነው፡፡ በአንድ የቃል ኑዛዜ ውስጥ ከአምስት መቶ ብር በላይ የኑዛዜ ስጦት የተደረገ እንደሆነ ከአምስት መቶ ብር በላይ የሆነው ስጦታ ተቀናሽ ይሆናል፡፡

 

የኑዛዜ መሻር

የኑዛዜ ተፈፃሚነት በተዛዡ ፍላጐት ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ ኑዛዜ አድራጊው ሰው በፈለገው ጊዜ ኑዛዜ የማድረግ፣ የመሻር ወይም የመለወጥ መብት አለው፡፡ አንድ ተናዛዥ የተናዘዘውን ኑዛዜ ምንም አይነት ምክንያት ሳያስፈልገው መሻር ይችላል፡፡ ተናዛዡ ይህን የሚያደርገው ኑዛዜውን ባደረገው ፎርም ነው፡፡ ይህ ማለት ኑዛዜውን ያደረገው በራሱ በተናዛዡ ጽሁፍ ከሆነ በዚያው ፎርም፤ በግልጽ በሚደረግ ኑዛዜ ከሆነ በዚያው ፎርም ኑዛዜውን መሻር ይችላል፡፡ ይህም የመሻር ሙሉ የኑዛዜ ቃሉን ወይም ደግሞ የኑዛዜውን የተወሰነ ቃል ብቻ ሊሆን ይችላል፡፡

ተናዛዡ ኑዛዜውን ለመሻር ወይም ለመለወጥ ያለውን ሀሳብ በግልጽ በሚያሳይ መልክ ኑዛዜውን በማንኛውም ጊዜ በማጥፋት፣ በመቅደድ ወይም አነጋገሩን በመሰረዝ የኑዛዜውን ቃል ለመለወጥ ይችላል፡፡ እንዲ በሚሆንበት ጊዜ ተቃራኒ የሆነ ማስረጃ ካልቀረበ በቀር ኑዛዜውን ራሱ ፈልጐ እንደሻረው ይቆጠራል፡፡ (ፍ/ሕ/ቁ 900)

የኑዛዜ መሻር ውጤት

ኑዛዜውን ተናዛዡ በራሱ ፍላጐት ከሻረው የተናዘዘው ቃል ቀሪ ይሆናል፡፡ ይህም ማለት ተናዛዡ ኑዛዜውን በሙሉ ከሻረ ኑዛዜው ቀሪ ሆነ ማለት ነው፡፡ በከፊል የኑዛዜውን ቃል የሻረው ከሆነ ይህ የተሻረው ቃል ቀሪ ሆኖ የተቀበረው የኑዛዜ ቃል ተፈፃሚ ይሆናል፡፡ በፍ/ብ/ሕ/ቁ 901/1/ እንደተገለፀው ተቃራኒ ቃል ከሌለ በቀር ያንዱ ኑዛዜ መሻር አስቀድሞ ተደርጐ የነበረውን ኑዛዜውን ቃል አያፀድቀውም፡፡

 

የኑዛዜ ውድቅ መሆን (Lapse of will)

የኑዛዜ ውድቅ መሆን ማለት የኑዛዜውን መፈፀም አቅም ከተናዡ ፍቃድ ውጭ በሕግ ኑዛዜው ቀሪ የሚሆንበት ሁኔታ ነው፡፡ የኑዛዜው ውድቅ መሆን ምክንያቶች እንደየ ኑዛዜ ፎርሟች ይለያያል፡፡ በቃል የተደረገ ኑዛዜው ኑዛዜው ከተደረገ ከሶስት ወር በኋላ ተናዛዡ በሕይወት ካለ ኑዛዜው ውድቅ ይሆናል፡፡ ኑዛዜው በተናዛዡ ጽሑፍ የተደረገ ከሆነ ኑዛዜው በተደረገ በሰባት አመት ጊዜ ውስጥ ለማዋዋል ሥልጣን በተሰጠው ሰው ወይም በፍርድ ቤት መዝገብ ቤት ዘንድ ያልተቀመጠ እንደሆነ ውድቅ ይሆናል፡፡

ኑዛዜው ከተደረገ በኋላ ልጅ መውለድ ኑዛዜውን ውድቅ ያደርገዋል፡፡ የተናዛዡ ባለቤት ወይም በምትክነት ፈቅዶ ለወራሽነት የቀረበ ወደታች የሚቆጠር ተወላጅ ከተወለደ ኑዛዜው ውድቅ ይሆናል፡፡ ከኑዛዜ በኋላ የተወለደን ልጅ ፈቃድ ለማግኘት በተሻሻለው የቤተሰብ ሕግ አንቀጽ 216 መሠረት በሞግዚቱ ወይም በንብረት አስተዳዳሪ ተወካይነት መሆኑ ተገልጿል፡፡ ተናዛዡ ልጅ የተፀነሰ መሆኑን እያወቀ ኑዛዜውን ያደረገ እንደሆነ ወይም ተናዛዡ ጉዳዩን ቢያውቅ ኑሮ ስጦታውን አያሰቀርም ነበር ተብሎ የሚገመት የሆነ እንደሆነ ዳኞች የኑዛዜ ስጦታዎች በሙሉ ወይም በከፊል  እንደፅኑ ለማድረግ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ተናዛዡ የወለደው ልጅ ወይም ወደታች የሚቆጠር ተወላጅ ቢያንስ የውርሱን ሁለት ሶሶተኛ ሁሌም (በማንኛውም ሁኔታ) ማግኘት አለበት (በፍ/ብ/ሕ/ቁ 905) ፡፡

ሌላው ኑዛዜን ውድቅ የሚያደርገው ባል ለሚስት በኑዛዜ ስጦታ ሰጥቶ ወይም ሚስት ለባሏ በኑዛዜ ሰጦታ ስጥታ እያለ ጋብቻው ከሞተ ውጭ በሆነ ምክንያት የፈረሰ እንዲሆን ነው፡፡

በኑዛዜ ስጦታ የተደረገለት ሰው ከሰጭው አስቀድሞ ከሞተ፣ ስጦታውን ለመቀበል ካልቻለ ወይም ደግሞ ለመቀበል ፈቃዱን ካልገለፅ የኑዛዜው ስጦታም እንደውርስ ሁሉ ውድቅ ይሆናል፡፡ ይህ ማት የኑዛዜ ስጦታ የተደረገለት ሰው ተናዛዡን ቀድሞ ከሞተ (በሕይወት ያለመሆን)፣ ለወራሽነት የማይገባ መሆን እና ኑዛዜውን ለመቀበል ፍቃደኛ አለመሆን የስጦታ ኑዛዜውን ውድቅ ያደርገዋል፡፡

የኑዛዜ ስጦታ የተደረገለት ሰው ከተናዛዡ በፊት ከሞተ የሱ ምትክ ሊወርስ (ስጦታውን ሊቀበል) የሚችልበት አጋጣሚ አለ፡፡ይህም፡-

               1ኛ. ተናዛዡ ጠቅላላ ሀቡቱን የሰጠው እንደሆነ ወይም

              2ኛ. ልዩ ስጦታ በሆነ ጊዜ ተቀባዩ ባለመኖሩ ሀብቱ ለመንግስት የሚተላለፍ ሲሆን ነው፡፡

የልዩ ስጦታ ዘመዶች የሚገቡት የናዛዡ እስከ አራተኛ ደረጃ የሚቆጠር ዘመዶች ከሌሉ ብቻ ነው፡፡

የኑዛዜ ትርጓሜ

አንዳንድ ጊዜ ኑዛዜው ግልጽ ባለመሆኑ ኑዛዜውን መረዳት በማይቻልበትና ትርጉም የሚያስፈልግበት ጊዜ አለ፡፡ እንዲህ ያለ አጋጣሚ ሲከሰት ኑዛዜው የሚተረጐመው የኑዛዜውን ዝርዝር ይዘቱን በመመርመርና ሌሎች የአካባቢ ሁኔታዎችንም በማመዛዘን የተናዛዡን ፍላጐት በመፈለግ ይሆናል፡፡ ኑዛዜ የግለሰቡ ፍላጐት ነፃ መግለጫ በመሆኑ የኑዛዜው ቃል ግልጽ ሆኖ እያለ በትርጉም አመካኝኝቶ የተናዛዡን ቃል ማዛባት ወይም ማሻሻል እንደማይቻል በሕጉ ፍ/ብ/ሕ/ቁ 910/2/ ላይ ተደንግጓል፡፡

ይህን ጉዳይ በተመለከተ የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በቅፅ 10 በመዝገብ ቁጥር 47487 በአመልካች አቶ ሀ/ራጉኤል ደበላ እና ተጠሪ እነ ወ/ሪት አለምፀሃይ ፈለገ መካከል በነበረው ክርክር ፟፟፟፟“ . . . በመሠረቱ ኑዛዜ ሊተረጎም የሚገባው ቃላቶቹ እና መልእክቱ ግልጽ ሳይሆን ሲቀር ነው፡፡ በሌላ አገላለፅ ኑዛዜው ግልጽ ቃላቶችንና መልዕክትን የያዘ ከሆነ ትርጓሜ መስጠት አያስፈሌግም፡፡ ይህንን መሠረታዊ መርህን መከተል ያለብን መሆኑን ደግሞ የፍ/ብ/ሔ/ቁጥር 910(2) ዴንጋጌ በግልጽ ያስገነዝባል፡፡ በመሆኑም የኑዛዜው ቃል መተርጎም ያለበት የኑዛዜው መልእክት ጥርጣሬ በሚፈጥርበት ጊዜ አሻሚ ወይም ግልጽ ያልሆነ እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ ይህን ደንብ ተፈጻሚ የሚሆንበትን መንገድም የፍ/ብ/ሔ/ቁጥር 910(1)፣ 911፣ 925 እና ሌሎች ድንጋጌዎች ያሳዩናል፡፡ ስለሆነም የኑዛዜው ቃልት ግልጽ የሆኑ እንደሆነ የተናዛዡ እውነተኛ፣ ትክክለኛ ፈቃድ የትኛው ነው ብሎ ትርጓሜ መስጠትና ከኑዛዜው ቃል መራቅ የማይፈቀድ ስለመሆኑ ከላይ የተጠቀሱት የውርስ ሕግ ድንጋጌዎች ያሳያሉ” ማለት ውሳኔ ሰጥቶል፡፡

በኑዛዜ ውስጥ የተናዛዡ የተጠቀመባቸው ቃላት አጠቃላይ ትርጉም ያላቸው ሆነው ሊገኙ ይችላሉ፡፡ ለምሳሌ “ሀብቴን”፣ “ወራሾቼን”፣ “የማይንቀሳቀስ ንብረቴን” የመሳሰሉ ቃላትን በኑዛዜው ውስጥ ተጠቅሞ ሊሆን ይችላል፡፡ በእንደዚህ ያለ ጊዜ እነዚህ ቃላት የሚረጐሙት ተዛዡ በሞተበት ወቅት የነበሩ ንብረቶች ወይም ወራሾችን ብቻ ለመግለፅ እንደተጠቀመባቸው ይቆጠራል፡፡ ነገር ግን ለዚህ ግምት ተቃራኒ የሆነ ማስረጃ በማቅረብ ማስረዳት ይቻላል (ፍ/ብ/ሕ/ቁ 911)፡፡

 

የኑዛዜ ስጦታዎች

በኑዛዜ  ተናዛዡ ለስጦታ ተቀባዮቹ ጠቅላላ የኑዛዜ ስጦታ ወይም ልዩ የኑዛዜ ስጦታ ወይም ሁለቱንም በአንድ ጊዜ ሊሰጥ ይችላል፡፡

ሀ/ ጠቅላላ የኑዛዜ ስጦታ (Legalies by universal title)

ተናዛዡ ሀብቱን በጠቅላላ ወይም ከመላው ንብረቱ አንድን ክፍል በመሉ ኃብትነት ወይም በሌጣ ርስትነት ለአንድ ወይም ለብዙ ሰዎች የሚያወርስበት የኑዛዜ ቃል ጠቅላላ ስጦታ ይባላል፡፡ ጠቅላላ ኃብት ስጦታ የሚቀበለውን ሰው ሟች የሚመርጥበት የተለየ ፎርም በሕግ አልተሰጠም፡፡

ለ/ ልዩ የኑዛዜ ስጦታ (Legalies by Singulat title)

ልዩ የኑዛዜ ስጦታ ማለት የሚሰጡ ንብረቶችን መጠን በግልጽ የሚመለከት ጉዳይ ነው፡፡ ለምሳሌ አቶ ባርናባስ ሚኒባስ ታክሲዋን ለወንድሜ ከሁሉም ይሰጥልኝ ወይም መርካቶ ያለው ሱቄ ለእህቴ ባል ለዮናስ ይሰጥልኝ ብሎ በኑዛዜ ሲያስቀምጥ ይህ ልዩ የኑዛዜ ስጦታ ነው፡፡

የጠቅላላ ኑዛዜ ስጦታ ውጤት

ተናዛዡ በኑዛዜው ላይ በግልጽ ካላስቀመጠ በቀር የሟችን ጠቅላላ ኃብት በስጦታ መልክ እንዲቀበል የተመረጠ ሰው ያለ ኑዛዜ ወራሽ (intestate succession) እንደሆነ ይቆጠራል፡፡ ይህ ሲባል የጠቅላላ ኑዛዜ ስጦታ የተደረገለት ሰው ያሉ ኑዛዜ ወራሽ ያለውን መብትና ግዴታ ይኖረዋል፡፡ ነገር ግን ተናዛዡ በግልጽ ጠቅላላ ኃብት በኑዛዜ ስጦታ ያገኘ ሰው ያለ ኑዛዜ ወራሽ እንደሆነ ሰው አይቆጠርም ሊል ይችላል፡፡ እንዲህ ከሆነ ደግሞ ያለኑዛዜ ወራሾች ያላቸውን መብት እና ግዴታ አይኖረውም፡፡

ገደብ ያለበት ኑዛዜ (conditional will)

በጠቅላላም ሆነ ልዩ የኑዛዜ ስጦታውን በኑዛዜው ሟች ይህ ሲደርስ ስጦታው ይፅናል፣ ይህ ሁኔታ ሲደርስ ደግሞ ስጦታው ይቀራል በማለት ገደብ ወይም ቅድመ ሁኔታ ሊጥል ይችላል፡፡ ለምሳሌ አቶ “ሀ” ሲሞት መኖሪያ ቤቱን አጐቱ “ለ” ሕይወቱ እስካለ ድስ ሊኖርበት ይችላል በማለት ሊናዘዝ ይችላል፡፡ እዚህ ላይ ግን “ለ” ሲሞት ስጦታው ቀሪ ይሆናል፡፡

አንድ የኑዛዜ ስጦታ አድራጊ ተናዥ የኑዛዜ ስጦታ የተደረገለት ሰው በተለይ እከሌን ወይም እከሊትን አግባ ወይም አታግባ ብሎ የሚያደርገው የኑዛዜ ገደብ ዋጋ አለው በማለት የፍ/ብ/ሕ/ቁ 917 አስቀምጧል፡፡ ነገር ግን በጠቅላላ ሁኔታ ወራሽ እንዳይገባ ወይም እንደገና እንዳያገባ የሚያሰገድደው የኑዛዜ ገደብ ፈራሽ ነው፡፡ ምክንያቱም ከኢ.ፌ.ዴ.ሪ ሕገ መንግስት አንቀፅ 34/1/ ጋር ስለሚቃረን፡፡

ሟች ያደረገው የኑዛዜ ስጦታ አንድ ሁኔታ ሲደርስ ስጦታው ይቀራል በሚል ገደብ አድርጐበት እንደሆነ ይህ ስጦታው የሚያስቀረው ሁኔታ የደረሰ እንደሆነ የተሰጠውን ኃብት ሊመልስ ማረጋገጫ የሚሆን ዋስ ወይም ሌላ ዋስትና እንዲሰጥ ባለ ጥቅም የሆነው ሰው በሚያቀርበው ጥያቄ መሠረት ዳኞች በኑዛዜ ስጦታ የተደረገለትን ሰው ሊያስገድዱ ይችላሉ፡፡

ተናዛዡ ወራሾቹን ወይም በኑዛዜ ስጦታ የተሰጣቸውን ሰዎች ከሚደርሳቸው ሐብት ላይ በተለይ ለአንድ ወይም ለብዙ ሰዎች አንድ አገልግሎት እንዲሰጡ ግድ (ግዴታ) እንዲሆንባቸው በኑዛዜው ለመወሰን ይችላሉ በማለት በፍ/ሕ/አ 920 ላይ ተገልጿል፡፡ ነገር ግን አንድ ግዴታ የተጣለበት ወራሽ ወይም በኑዛዜ ስጦታ የተሰጠው ሰው ስለዚህ ግዴታ አፈፃፀም በደረሰው ውርስ ወይም የኑዛዜ ስጦታ መሠረት ካልሆነ በቀር እንደማይገደድ በፍ/ብ/ሕ/ቁ 921 ላይ ተገልጿል፡፡ በፍ/ብ/ሕ/ቁ 922 ላይ ደግሞ በኑዛዜው ወይም ውርሱ የግዴታው ተጠቃሚ የሆነው ሰው የታዘዘለት እንዲፈፀምለት ለማስገደድ ይችላል፡፡ እንዲሁም ለግዴታው አፈፃፀም ዋስ ወይም ሌላ ማረጋገጫ እንዲያቀርብ አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ይህኑ እንዲያደርግ ይገደዳል፡፡ ተናዛዡ ግልጽ በሆነ ሁኔታ ግዳጁን ያልፈፀመ ግለሰብ ስጦታውን ማግኘት አይችልም የሚል ቃል በኑዛዜው ውስጥ ካላሰፈረ በስተቀር ግዳጁን አለመፈፀሙ ስጦታውን ውደቅ እንደሚያደርገው በፍ/ብ/ሕ/ቁ 923/1/ ተጠቅሷል፡፡ ተናዛዡ እንዲህ ያለ ቃል ቢያስፈርም ግን ስጦታን በቅን ልቦና ያገኙ ሰዎች መብት አይነካም፡፡

ወራሹ ወይም የኑዛዜ ባለስጦታው ለሌላው እንዲያስተላልፍ ስለመታዘዝ (Entails)

በአንድ ኑዛዜ ላይ ተናዛዡ በውርስ ወይም በስጦታ የተሰጠውን ሐብት ወይም ከዚሁ ወስጥ የተወሰነውን ክፍል ወራሹ ወይም የኑዛዜ ባለስጦታው ለሌለ ሰው እንዲያስተላልፍ ሊያዝ ይችላል፡፡ ይህ ግን መቼና በምን ሁንታ መፈፀም እንዳለበት ተናዛዡ በግልጽ መጥቀስ አለት (ፍ/ብ/ሕ/ቁ 929)፡፡ ሀብቱን በመጀመሪያ የሚቀበል ወራሽ ወይም የኑዛዜ ስጦታ ተቀባይ የሆነ ሰው ባለግዴታ ይባላል፡፡ የምትክነቱ ሥራ በሚፈፀምበት ጊዜ ከወራሽ ወይም ከኑዛዜ ስጦታ ከተደገለት ሰው ላይ ንብረቱን የሚያኘው ሰው ዋና ወራሽ ይባላል፡፡

ዋናው ወራሹ ተናዡ በሞተበት ጊዜ ውርሱን ወይም ስጦታውን የመቀበል ችሎታ ይኑረው አይኑረው አስፈላጊ አይደለም፡፡ ነገር ግን ውርሱን ወይም ስጦታውን ተተክቶ በሚረከብበት ጊዜ የመቀበል ችሎታ ያለው መሆን አለበት፡፡ ባለ ግዴታው በኑዛዜ ቃል እንዲያስተላልፍ የተሰጠው ኃብት ወይም ንብረቱን በኑዛዜው ላይ የተጠቀሰው ሁኔታ ሲያጋጥም፣ የመተላለፊያው ጊዜ ሲደርስ ወይ በኑዛዜው የተጠሰው ሁኔታ ሲፈፀም የሚያስተላልፈው በመሆኑ ሊሸጠው ለሌላ 3ኛወገን ሊያስተላልፈው ወይም በእዳ ሊያስይዘው እንዳማይችል በፍ/ብ/ሐ/ቁ 931 ላይ ተገልጿል፡፡ ዳኞች ፍታሀዊ ሆነው ሲያገኙት አንድን ንብረት እንዲሸጥ፣ እንዲተላለፍ የማዘዝ ሥልጣን አላቸው፡፡ ነግር ግን ወራሹ ወይም የኑዛዜ ባለስጦታው ለሌላ ሰው እንዲያስተላልፍ የታዘዘውን የማይንቀሳቀስ ንብረት ዳኞች ከላይ በተሰጠው ሁኔታ እንዲሸጥ፣ እንዲለወጥ ወይም ለሌላ ሰው እንዳያስተላልፍ ማዘዘ እንደማይችል በፍ/ብ/ሐ/ቁ 932 ላይ ተገልጿል፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያቱ ንብረቱ የዋና ወራሹ ስለሆነ ነው፡፡ ይህ ንብረት መብት ተጥሶ ከተገኘ በሕገ ወጥ መንገድ የተወሰደው ንብረት እንዲመለስ ጥያቄ ማቅረብ አለበት፡፡ ዋናው ተጠቃሚ ወይም ወኪሉ ወይም ተናዛዡ የመተካቱን ሥርዓት ለማስፈፀም የመረጠው ሰው በማይገባ የተደረገ መሸጥ፣ መለወጥ ወይም መያዝ እንዲፈርስ በማንኛውም ጊዜ ለመጠየቅ ይችላል፡፡ የመተካቱ ሥርዓት ከተደረገ በኋላ በሚከተለው ሁለት አመት ውስጥ ክሳቸውን ማቅረብ ይችላሉ (በፍ/ብ/ሐ/ቁ 933)፡፡

ባለግዴታው ስጦታውን ለመቀበል ካልቻለ ወይም ፈቃደኛ ካልሆነ ምንም መደረግ እንዳለበት ተናዛዡ በኑዛዜው ላይ ካልገለፀ በስተቀር የኑዛዜ ስጦታ የሚደርሰው ሰው ወዲያውኑ እንዲቀበል እንደሚደረግ በፍ/ብ/ሕ/ቁ 935 ላይ ተገልጿል፡፡ ይህም ማለት ዋና ወራሹ እንዲወስድ ይደረጋል፡፡ በዋና ወራሸነት መብት ያለው ሰው ቢሞትና የሚተኩትም ሰዎች ባይኖሩ ባለግዴታው ባደራ መልክ በያዘው መብትና ንብረት ያለምንም ገደቡ ሊጠቀም ይችላል፡፡ የሚተካው ሰው ባለመቅረብ ወይም እምቢ ማለት ወይም በማንኛውም ሌላ ምክንኛት በተናዛዡ ፈቃድ ካልተፈፀመ የተሰጡትን ንብረቶች ለዋናው ወራሽ ወራሾች ይተላለፋሉ፡፡ ተቃራኒ ቃል ከሌላ በቀር የተናዛዡ ወራሾች ለዋናው ወራሽ የተሰጡ ንብረቶች ላይ አንድም መብት አይኖራቸውም ሲል የፍ/ብ/ለ/ቁ 936 ይገልፃል፡፡

ከወራሽነት መንቀል (Dihersion)

አንድ ተናዛዥ ያለውን ንብረት በኑዛዜ ለማስተላለፍ ሙሉ መብት እንዳለው ያህል ንብረቱን ላለማውረስም ሙሉ መብት አለው፡፡ በዚህ ጊዜ ተናዛዡ ወራሽ ሳያደርግ በሕግ ሊወርሱት ይችሉ የነበሩትን ግለሰቦች ወይም ከእነሱ አንድን በግልጽ ከውርስ ውጪ ሊያደርግ ይችላላ (በፍ/ብ/ሐ/ቁ 937/1/)፡፡ ይህም ሲሆን ከውርስ ውጪ የሆነው ወራሽ ከተናዡ በፊት እንደሞተ ተቆጥሮ ውርሱ በሕጉ መሠረት ይፈፀማል (ፍ/ብ/ለ/ቁ 937/2/)፡፡

አንድ ተናዛዥ ወራሾችን የመንቀል መብት ቢኖረውም ወደታች የሚቆጠሩ ተወላጆችን ጥቅም የሚጠብቅ የሕግ ድንጋጌ በውርስ ሕጋችን ውስጥ አለ፡፡ በፍ/ብ/ሕ/ቁ 938/1/ ተናዛዡ በኑዛዜው ውስጥ ከውርስ ወራሹን ለመንቀል የደረሰበትን ምክንያት ካልገለፅ በቀር ልጅን ወይም ወደታች የሚቆጠር ተወላጅን ከውርስ ቢነቅል ውኔው በሕግ እንደማይፀና ይገለፃል፡፡ ይህም ማለት ተናዛዡ ልጆቹን ወይም ወደታች የሚቆጠሩ ተወላጆችን በዝምታ መንቀል አይችልም፡፡ ነገር ግን ተቃራኒ የኑዛዜ ቃል ከሌለ በቀር የሁለተኛ፣ የሶስተኛ እና አራተኛ ደረጃ ዘመዶች እያሉ በኑዛዜው ሌላ ሰው ንብረቱን ከሰጠ እነዚህን የተጠቀሱ ዘመዶቹን ከኑዛዜው ውጭ እንዳደረጋቸው ይቆጠራል (በፍ/ብ/ሕ/ቁ 939)፡፡ ወደታች የሚቆጠሩ ተወላጆችን ተናነዛዡ በግልጽ ከኑዛዜ ውጭ ካላደረጋቸው በስተቀር የጠቅላላ ኑዛዜ ባለ ስጦታዎች ካገኙት ንብረት ላይ እኩል ይካፈላሉ፡፡(በፍ/ብ/ሕ/ቁ 939/1/)

ተናዛዡ ከወራሾቹ አንዱን ወይም ሁሉንም የኑዛዜውን ሙሉ ወይም አንድ ቃል ከተቃወሙ ውርሱን እንዳያገኙ ብሎ ቢናዘዝ ይህ ኑዛዜ በሕግ ፊት ተቀባይነት እንደሌላው (በፍ/ብ/ሕ/ቁ 940) ላይ ተደንግጐ ይገኛል፡፡

ማጠቃለያ                          

አንድ ሰው በምድር ላይ የተወሰነ ጊዜ ከኖረ በሆላ ማለፉ የማይቀር ነው፡፡ በምድር ላይ ቆይታው ከተወለደበት ሰዓት አንስቶ እከሞተበት ጊዜ ድረስ የተለያዩ መብቶች እና ግዴታዎች አሉት፡፡ ከነዚህ መብቶቹ ውስጥ የተወሰኑት ከሞተ በሆላ ወደ ሌላ ሰው መተላለፍ የሚችሉ ናቸው፡፡ ሟች ከሞተ በሆላ ሊተላለፉ የሚችሉት መብቶቹ ለሌሎች በሕይወት ላሉ ወራሾቹ ወይም ሟች በኑዛዜ ስጦታ ለሰጣቸው ሰዎች ይተላለፋሉ፡፡ ይህም የሚሆነው በውርስ ሕግ መሠረት ነው፡፡

የሟችን ንብረት የሚወርሱት እንማን ናቸው፣ ወራሽነትን የሚያሳጡ ነገሮች ምንድን ናቸው፣ የሟች ንብረቶች በምን መልኩ ነው ለወራሾቹ የሚተላለፉት፣ ሟች ኑዛዜ ከተወ ኑዛዜው ሕጋዊ ውጤት እንዲኖረው ምን ምን መሟላት አለበት እና የመሳሰሉትን ነገሮች ከላይ በጽሑፍ ውስጥ ያየናቸው ናቸው፡፡