ዛሬ ጥቅምት 5 ቀን 2008 ዓ.ም በዋለው ችሎት የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ድረ ገፅ ተጠቅመው የተለያዩ ጽሑፎችን በማውጣት ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በኃይል ለመናድ ተንቀሳቅሰዋል በሚል የተከሰሱ አራት የዞን9 ጦማርያን ከክሱ ነፃ በማድረግ ውሳኔ አስተላለፈ፡፡ ወሳኔ የተላለፈው በጦማርያን ሶልያና ሽመልስ፣ አቤል ዋበላ ሱጌቦ፣ ናትናኤል ፈለቀ፣ በፍቃዱ ሃይሉ እና አጥናፉ ብርሃኔ ላይ ነው፡፡
በውሳኔው መሠረት አንደኛ ተከሳሽ ሶልያና ሽመልስ መከላከል ሳያስፈልጋት ከክሱ ነፃ፣ ሦስተኛ ተከሳሽ ናትናኤል ፈለቀ መከላከል ሳያስፈልገው ከክሱ ነጻ፣ አምስተኛ ተከሳሽ አጥናፍ ብርሃኔ መከላከል ሳያስፈልገው ከክሱ ነፃ፣ ስድስተኛ ተከሳሽ አቤል ዋበላ መከላከል ሳያስፈልገው ከክስ ነፃ የተባሉ ሲሆን፤ ሁለተኛ ተከሳሽ ጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉ ከሽብር ክስ ነፃ የተባለ ሲሆን መአከላዊ ምርመራ በሃይል እና በማሰቃየት የሰጠው ቃል ላይ አመፅ እንዳነሳሳ አምኗል በሚል በወንጀል ሕጉ 257 መሠረት እንዲከላከል ግን ዋስትና መጠየቅ እንደሚችል ተገልጿል።
የጦማርያኑ ጠበቃ በፍቃዱ ተከላከል የተባለበት አንቀጽ የዋስትና መብቱን የማይከለክል ስለሆነ (ተከላከል የተባለበት የወንጀለኛ መቅጫ ሕግ አንቀጽ 257-ሀ ሲሆን በቀላል እስራት (በቅጣት ማኑዋሉ ስሌት ከስድስት ወር ስለማይበልጥ) በዋስ ከእሥር እንዲፈታ ይግባኝ የጠየቁ ሲሆን ዓቃቤ ሕግ ተቃውሞ በማሰማቱ ይግባኙን ለማየትና ውሳኔ ለመስጠት ለጥቅምት 10 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ ተሰጥቷል።
ሰኔ 30 ቀን 2007 ዓ.ም ፍትሕ ሚኒስቴር በአዋጅ በተሰጠው ሥልጣን መሠረት ከተከሰሱት ጦማርያን መካከል ኤዶም ካሳዬ፣ ዘላለም ክብረት፣ አስማማው ሃይለጊዮርጊስ፣ ተስፋለም ወልደየስ አራጌ እና ማህሌት ፋንታሁን ክስ ማንሳቱና ጦማርያኑ ከእስር መለቀቃቸው አይዘነጋም፡፡